የጥያቄ ሣጥን
◼ እውቀት በተባለው መጽሐፍ ከአንድ ሰው ጋር መደበኛ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት የሚደረገው ለምን ያህል ጊዜ መሆን አለበት?
በአሁኑ ጊዜ ይሖዋ ድርጅቱን እየባረከ ነው። በየዓመቱ በሺህ የሚቆጠሩ አዲሶች ከእውነት ጎን መሰለፋቸው ለዚህ ጉልህ ማስረጃ ነው። እውቀት የተባለው መጽሐፍ በዚህ ረገድ ውጤታማ መሣሪያ ሆኖ ተገኝቷል። የጥር 15, 1996 መጠበቂያ ግንብ ይህ መጽሐፍ የተዘጋጀው የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች በአጭር ጊዜ ውስጥ ምናልባትም በጥቂት ወራት ውስጥ መንፈሳዊ እድገት እንዲያደርጉ ለመርዳት ታስቦ እንደሆነ ገልጾ ነበር።
በመሆኑም ይኸው መጠበቂያ ግንብ በገጽ 17 ላይ እንዲህ ብሎ ነበር:- “አንድ ግለሰብ ጥናቱን እውቀት በተባለው መጽሐፍ አጠናቆ ከተጠመቀ በኋላ በሌላ ሁለተኛ መጽሐፍ ለእርሱ ጥናት መምራት አያስፈልግም።”
አንድ ሰው እውቀት የተባለውን መጽሐፍ አጥንቶ ከጨረሰ በኋላ ባይጠመቅስ? የሰኔ 1996 የመንግሥት አገልግሎታችን ገጽ 6 አንቀጽ 23 ላይ በመጠበቂያ ግንቡ ላይ የተጠቀሰውን ሐሳብ በማውሳት አንድ ሰው እውቀት የተባለውን መጽሐፍ አጥንቶ ከጨረሰ በኋላ ከዚያው ሰው ጋር ሌላ መጽሐፍ ማጥናት እንደማያስፈልግ አሳስቦን ነበር። ይህ ማለት ግን ከዚህ በኋላ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪውን ቸል እንለዋለን ማለት ነውን? አይደለም። ሰዎች ስለ እውነት መሠረታዊ እውቀት እንዲኖራቸው እንፈልጋለን። ይሁንና አንድ ውጤታማ አስተማሪ መጠነኛ ችሎታ ያለውን በፍላጎት የሚያጠና ተማሪ በአንጻራዊ ሁኔታ ሲታይ በአጭር ጊዜ ውስጥ ይሖዋን ለማገልገል የጥበብ ውሳኔ እንዲያደርግ የሚያስችለውን በቂ እውቀት ሊያስታጥቀው ይችላል ተብሎ ይታመናል። እንዲያውም አንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች አመቺ ሁኔታ ስላላቸው በሳምንት ከአንድ ጊዜ በላይ ለማጥናት ሊፈልጉ ይችላሉ።
አንዳንድ ተማሪዎች ከሌሎች ይልቅ አዝጋሚ እድገት እንደሚያደርጉ አይካድም። ይሁን እንጂ ሰውዬው እውቀት የተባለውን መጽሐፍ ከሌሎቹ የበለጠ ለረጅም ጊዜ አጥንቶ ከጉባኤው ጋር ለመተባበር እንደሚፈልግ የሚያሳይ ውሳኔ ላይ ካልደረሰ አስፋፊው በአገልግሎት ኮሚቴ ውስጥ ካሉት ሽማግሌዎች አንዱን ቀርቦ ማነጋገሩ ጥሩ ይሆናል። ለዚህ ምክንያት የሆኑ ሌሎች ነገሮች ወይም ለየት ያሉ ሁኔታዎች ካሉት ሌላ ተጨማሪ እርዳታ ያስፈልገው ይሆናል። ይህም በጥር 15, 1996 መጠበቂያ ግንብ ገጽ 17 አንቀጽ 11 እና 12 ላይ ከተገለጸው መሠረታዊ ሥርዓት ጋር የሚስማማ ነው።
ተማሪው ላገኘው የእውነት መሠረታዊ እውቀት ያለው አድናቆት በክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ላይ እንዲገኝ ሊገፋፋው ይገባል። ይህም ተማሪው ይሖዋን ለማገልገል ፍላጎት እንዳለው የሚያሳዩ አንዳንድ ግልጽ እርምጃዎችን ወደ መውሰድ ሊያደርሰው ይችላል። ለረጅም ጊዜ እውቀት የተባለውን መጽሐፍ ካጠናም በኋላ እንዲህ ዓይነቱን መንፈሳዊ አድናቆት የማያሳይ ከሆነ ጥናቱን ማቆሙ ይመረጣል።