‘ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጁ መሆን’
1 በዛሬው ጊዜ የይሖዋ ሕዝቦች የተትረፈረፈ መንፈሳዊ ምግብ በማግኘታቸው ተባርከዋል። (ኢሳ. 25:6) በግልና በቤተሰብ ጥናት እንዲሁም በጉባኤና በትልልቅ ስብሰባዎች አማካኝነት ብዙ ቅዱስ ጽሑፋዊ ትምህርቶች እናገኛለን። ይሁን እንጂ ‘ፍጹምና ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጀን’ ለመሆን ከእነዚህ መንፈሳዊ ትምህርቶች ሙሉ በሙሉ እየተጠቀምን ነውን?—2 ጢሞ. 3:17
2 በዚህ ባጋመስነው ዓመት ማለትም በ1998 የቀረቡትን መንፈሳዊ ምግቦች ብቻ እስቲ ተመልከት! በሳምንታዊ የጉባኤ ስብሰባዎቻችን ላይ የክርስቲያን ግሪክኛ ቅዱሳን ጽሑፎች ክፍል በሆኑ 23 መጻሕፍት ውስጥ የተካተቱትን አንዳንድ ጎላ ያሉ ነጥቦች እንሸፍናለን፣ በመጠበቂያ ግንብ መጽሔቶች የወጡትን የተለያዩ ርዕሶች በንግግር መልክ እንወስዳለን። አንድ ሦስተኛ የሚሆነውን የእውቀት መጽሐፍ የምንሸፍን ሲሆን የውይይት አርዕስት ከተባለውም ቡክሌትም በርካታ ክፍሎች እንሸፍናለን። በተጨማሪም በዓመት ውስጥ በምናገኛቸው 12 የመንግሥት አገልግሎታችን እትሞችና 52 የመጠበቂያ ግንብ የጥናት ርዕሶች እንዲሁም የተለያየ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትምህርት ባዘሉ ብዙ የሕዝብ ንግግሮች አማካኝነት እንመገባለን። በዚህ ሁሉ ላይ ደግሞ መንፈሳዊ ቁም ነገር የሞላባቸው የአውራጃ፣ የወረዳና የልዩ ስብሰባ ፕሮግራሞች ይቀርባሉ። ያገኘናቸው መልካም መንፈሳዊ ነገሮች ምንኛ የተትረፈረፉ ናቸው!
3 የይሖዋን ዝግጅቶች አድንቁ፦ ከዝግጅቶቹ ሙሉ ጥቅም ማግኘት እንድንችል ይሖዋ የተትረፈረፈ መንፈሳዊ ምግብ የሚያቀርብበትን ምክንያት መገንዘብ ይኖርብናል። እነዚህን መልካም ነገሮች መመገባችን እምነታችንን ከመገንባቱም በላይ ከይሖዋ ጋር ያለንን ዝምድና ያጠናክርልናል። (1 ጢሞ. 4:6) ሆኖም መንፈሳዊ ምግብ የሚቀርብልን እኛ ትምህርት እንድናገኝ ብቻ አይደለም። የምናገኘው መንፈሳዊ ምግብ እውነትን ለሌሎች እንድናካፍል የሚያንቀሳቅሰን ሲሆን የምሥራቹ አገልጋዮች እንደመሆናችን መጠን በዚሁ ሥራችን ውጤታማ እንድንሆንም ያስታጥቀናል።—2 ጢሞ. 4:5
4 መንፈሳዊ ፍላጎታችንን ቸል አንበል። ከዚህ ይልቅ በይሖዋ ማዕድ ለሚቀርቡልን የተትረፈረፉና መንፈሳዊ ፍላጎታችንን የሚያረኩ ዝግጅቶች ጉጉት ማሳደራችንን እንቀጥል። (ማቴ. 5:3፤ 1 ጴጥ. 2:2) ከእነዚህ ዝግጅቶች ሙሉ በሙሉ መጠቀም እንድንችል ቋሚ የሆነ የግልና የቤተሰብ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ማድረግን እንዲሁም አዘውትሮ በስብሰባዎች ላይ መገኘትን ለመሳሰሉት በጣም አስፈላጊ ጉዳዮች በቂ ጊዜ መመደብ ይኖርብናል። (ኤፌ. 5:15, 16) እንዲህ በማድረጋችን ጳውሎስ በዕብራውያን 13:20, 21 ላይ ታማኝ ለሆኑት የዕብራውያን ክርስቲያኖች በመንፈስ አነሳሽነት ከጻፈው ማበረታቻ ጋር የሚመሳሰል አስደሳች በረከት እናገኛለን።