‘የእምነትን ቃል መመገብ’
1 ለአምላክ ያደሩ ሆኖ መኖር ብርቱ ጥረት ይጠይቃል። (1 ጢሞ. 4:7-10) በመሆኑም በራሳችን ኃይል ይህን የሕይወት ጎዳና ለመከተል ጥረት የምናደርግ ከሆነ ዝለን ልንወድቅ እንችላለን። (ኢሳ. 40:29-31) ከይሖዋ ዘንድ ኃይል የምናገኝበት አንዱ መንገድ ‘የእምነትን ቃል በመመገብ’ ነው።—1 ጢሞ. 4:6 የ1954 ትርጉም
2 የተትረፈረፈ መንፈሳዊ ምግብ:- ይሖዋ በቃሉ እንዲሁም ‘በታማኝና ልባም ባሪያ’ በኩል የተትረፈረፈ መንፈሳዊ ምግብ ያቀርብልናል። (ማቴ. 24:45 የ1954 ትርጉም) ከዚህ ዝግጅት ለመጠቀም የበኩላችንን እያደረግን ነው? መጽሐፍ ቅዱስን በየዕለቱ እናነባለን? የግል ጥናት ለማድረግና ለማሰላሰል የሚያስችል ጊዜስ መድበናል? (መዝ. 1:2, 3) እንደዚህ ያለው ጤናማ መንፈሳዊ ምግብ ብርታት የሚሰጠን ከመሆኑም በላይ የሰይጣን ዓለም በሚያደርስብን ተጽዕኖ እንዳንዳከም ይረዳናል። (1 ዮሐ. 5:19) አእምሯችንን ጤናማ የሆነ ትምህርት የምንመግብና የተማርነውን በሕይወታችን ውስጥ ተግባራዊ የምናደርግ ከሆነ ይሖዋ ከእኛ ጋር ይሆናል።—ፊልጵ. 4:8, 9
3 ይሖዋ በጉባኤ ስብሰባዎችም ያበረታታናል። (ዕብ. 10:24, 25) በእነዚህ ስብሰባዎች ላይ የምናገኘው መንፈሳዊ ትምህርትና ከወንድሞቻችን ጋር የምንመሠርተው ጥሩ ወዳጅነት በፈተና ጊዜ ጸንተን እንድንቆም ያደርገናል። (1 ጴጥ. 5:9, 10) አንዲት ወጣት ክርስቲያን “ሙሉ ቀን ትምህርት ቤት ውዬ ስመጣ እዝላለሁ። ስብሰባዎች ግን ልክ በበረሃ መካከል እንዳለ ገነት ለሚቀጥለው ቀን የትምህርት ቤት ውሎዬ መንፈሴን ያድሱልኛል” በማለት ተናግራለች። በስብሰባዎች ላይ ለመገኘት በምናደርገው ጥረት በእጅጉ ተባርከናል!
4 እውነትን ማወጅ:- ለሌሎች መስበክ ለኢየሱስ ልክ እንደ ምግብ የብርታት ምንጭ ሆኖለት ነበር። (ዮሐ. 4:32-34) እኛም በተመሳሳይ ለሰዎች ስለ አስደናቂው የአምላክ ተስፋ በምንናገርበት ጊዜ ኃይላችን ይታደሳል። በተጨማሪም በአገልግሎት የምንጠመድ ከሆነ ልባችንም ሆነ አእምሯችን በመንግሥቱና በቅርቡ በሚመጡት በረከቶች ላይ ያተኮረ ይሆናል። በእውነትም የስብከቱ ሥራ እንድንታደስ ያደርገናል።—ማቴ. 11:28-30
5 በዛሬው ጊዜ ይሖዋ ለሕዝቦቹ ከሚያቀርበው የተትረፈረፈ መንፈሳዊ ምግብ መቋደስ በመቻላችን በእርግጥም ተባርከናል! እንግዲያው ይሖዋን በደስታ ማወደሳችንን እንቀጥል።—ኢሳ. 65:13, 14