የጥያቄ ሣጥን
◼ ለረጅም ጊዜ አገልግሎት ያቆመን ሰው እንደገና የምሥራቹ አስፋፊ እንዲሆን መርዳት የሚቻለው እንዴት ነው?
አገልግሎት አቁሞ የነበረ ሰው ይሖዋን የማገልገል ልባዊ ፍላጎት እንዳለው የሚያሳይ እርምጃ ሲወስድ ማየቱ በጣም የሚያስደስት ነው። (ሉቃስ 15:4-6) ግለሰቡ የደረሰበት ተቃውሞ ወይም የኑሮ ጫና የግል ጥናት እንዳያደርግ፣ በጉባኤ እንዳይገኝና በመስክ አገልግሎት እንዳይሳተፍ እንዳደረገው ምንም ጥርጥር የለውም። መንፈሳዊ እድገት እንዲያደርግ በግል እርዳታ መስጠት የሚቻልበት የተሻለው መንገድ ምንድን ነው?
ሁላችንም ለግለሰቡ ያለንን እውነተኛ ክርስቲያናዊ ፍቅር ለመግለጽ ቀዳሚ መሆን ይገባናል። በምን በኩል መንፈሳዊ እርዳታ እንደሚያስፈልገው ለማወቅ ሽማግሌዎች ፈጥነው መንቀሳቀስ አለባቸው። (ያዕ. 5:14, 15) ግለሰቡ አገልግሎት ያቆመው ለአጭር ጊዜ ከሆነ ተሞክሮ ያለው አስፋፊ እንዲረዳው ማድረጉ ብቻ አገልግሎት እንዲጀምር ሊረዳው ይችላል። ይሁን እንጂ አገልግሎት ያቆመው ሰው ከጉባኤው ጋር የነበረውን ግንኙነት ለረጅም ጊዜ አቋርጦ ከነበረ ተጨማሪ እርዳታ ያስፈልገው ይሆናል። እምነቱን ለማጠንከርና አድናቆቱን ከፍ ለማድረግ ተስማሚ ጽሑፍ በመምረጥ የግል የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት እንዲመራለት ማድረግ ጥሩ ሊሆን ይችላል። በዚህ ጊዜ የአገልግሎት የበላይ ተመልካቹ ጥናቱን የሚመራ ብቁ አስፋፊ ይመድብለታል። (ዕብ. 5:12-14፤ በኅዳር 1998 የመንግሥት አገልግሎታችን ላይ የወጣውን የጥያቄ ሣጥን ተመልከት።) እንደዚህ ያለ እርዳታ የሚያስፈልገውን ሰው የምታውቅ ከሆነ የጉባኤህን የአገልግሎት የበላይ ተመልካች አነጋግር።
ለረጅም ጊዜ አገልግሎት አቁሞ የነበረ ሰው አብሮህ እንዲያገለግል ከመጋበዝህ በፊት የመንግሥቱ አስፋፊ ለመሆን ይበቃ እንደሆነ ለማረጋገጥ ሁለት የጉባኤ ሽማግሌዎች ቢያነጋግሩት ጥሩ ነው። እንደዚህ በሚያደርጉበት ጊዜ አስፋፊ ለመሆን ፍላጎት ያለውን አንድ አዲስ ሰው ሲያነጋግሩ የሚከተሉትን አሠራር ይከተላሉ። (22–109 መጠበቂያ ግንብ ገጽ 16-17ን ተመልከት።) አገልግሎት አቁሞ የነበረው ሰው ምሥራቹን ለሌሎች ለማካፈል ከፍተኛ ፍላጎት ሊኖረው ይገባል። እንዲሁም አገልግሎታችን በተባለው መጽሐፍ ገጽ 98-9 ላይ የሚገኙትን መሠረታዊ ብቃቶች ማሟላትና ዘወትር በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ መገኘት ይኖርበታል።
እንደገና የተነቃቃው ሰው ጥሩ መንፈሳዊ ልማዶች ማዳበሩ ከይሖዋ ጋር ያለውን ውድ ዝምድና ለማጠንከርና ጠብቆ ለማቆየት እንዲሁም ወደ ዘላለም ሕይወት በሚወስደው መንገድ ላይ የጀመረውን ጉዞ ለመቀጠል ይረዳዋል። (ማቴ. 7:14፤ ዕብ. 10:23-25) ‘ትጋትን የሚያሳይ’ ከሆነና ለመጽናት የሚያስችለውን ክርስቲያናዊ ባሕርያትን የሚያፈራ ከሆነ ክርስቲያን ደቀ መዝሙር በመሆን ረገድ ‘ሥራ ፈትና ፍሬ ቢስ’ እንዳይሆን ለመከላከል ያስችለዋል።—2 ጴጥ. 1:5-8