በመልካም ሥራ ይሖዋን አስከብሩ
1 ዶፍ ዝናብ በድንገት ሲጥል መጠለያ ቤት ማግኘት ምንኛ የሚያስደስት ነው! ቤቱ የሚሞቅና ከአደጋ የሚጠብቅ እንዲሁም በዚያ የሚኖሩት ሰዎች እንግዳ ተቀባዮች ከሆኑ እዚያ መቆየት ያስደስትሃል። የመንግሥቱ የስብከት ሥራ ሰዎች ከሰይጣን ሥርዓት ሸሽተው እንዲህ በመሰለ ቤት ውስጥ እንዲጠለሉ ያደርጋል። በየዕለቱ የምናሳየው ጠባይ ከአደጋ የሚጠብቀው ይህ መጠለያ ምን ያህል አስተማማኝ እንደሆነ እንዲገነዘቡ ሊረዳቸው ይችላልን? አዎን፣ ሰዎች ‘መልካሙን ሥራችንን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችንን እንደሚያከብሩ’ ኢየሱስ ተናግሯል።—ማቴ. 5:16
2 ተግባራችን ሌሎች ሰዎችን ወደ ይሖዋና ወደ ድርጅቱ መሳብ እንችል ዘንድ ምን ዓይነት ጠባይ ማሳየት ይኖርብናል? በሉቃስ 6:31 እና 10:27 ላይ ተመዝግበው የሚገኙትን የኢየሱስ ቃላት ሕይወታችንን በየዕለቱ እንዲቀርጹ በመፍቀድ ነው። ይህም ለሰዎች ፍቅራዊ አሳቢነት እንድናሳይ ያነሳሳናል እንዲሁም በዚህ ረገድ በድን ከሆነውና አሳቢነት ከጎደለው ዓለም የተለየን ያደርገናል።
3 በጀልባ ትጓዝ የነበረች አንዲት እህት አንዲት ወጣት ሴት ውኃውን ለማየት በመፍራትዋ ልጅዋን በደንብ መያዝ እንዳልቻለች ተመለከተች። እህት ልጁን ተቀብላ ያዘችላት። ሴትየዋ ውለታዋን እንዴት እንደምትመልስ ስትጠይቃት እህት:- ‘የይሖዋ ምሥክሮች ቤትሽ መጥተው ሲያነጋግሩሽ በደንብ አዳምጫቸው’ አለቻት። ሴትየዋ እንደተባለችው ያደረገች ሲሆን አሁን እሷና ባለቤትዋ የይሖዋ ምሥክሮች ናቸው። መልካም ሥራ ሰዎች ለመንግሥቱ መልእክት በሚሰጡት ምላሽ ላይ ለውጥ ያመጣል።
4 መላ ሕይወታችንን ይነካል:- በጎረቤቶቻችን ዘንድ፣ በሥራ ቦታ ወይም በትምህርት ቤት እንዲሁም በምንዝናናበት ቦታ የምናሳየው ጠባይ ሰዎች ስለ እኛና ስለ ሃይማኖታችን አስተያየታቸውን እንዲሰነዝሩ ያደርጋቸዋል። ስለሆነም እንዲህ እያልን ራሳችንን መጠየቃችን የተገባ ነው:- ‘ሰዎች እኔንም ሆነ ቤተሰቤን የሚመለከቱት እንዴት ነው? ጎረቤቶቻችን የሚያውቁን ቤታችንና ግቢያችን ንጹሕና በደንብ የተያዘ እንደሆነ አድርገው ነው? የሥራ ባልደረቦቻችንና በትምህርት ቤት አብረውን የሚማሩ ተማሪዎች የሚመለከቱን ሰዓት አክባሪዎችና ትጉህ ሠራተኞች እንደሆንን አድርገው ነው? ሌሎች ሰዎች የሰውነት አቋማችን ልከኛና የሚያስከብር እንደሆነ ይሰማቸዋልን?’ መልካም ሥራችን የይሖዋ አምልኮ በሌሎች ዘንድ ማራኪ ሆኖ እንዲታይ ሊያደርግ ይችላል።
5 ክርስቲያኖች የፌዝ ዒላማ እንደሚሆኑ ጴጥሮስ ተናግሯል። (1 ጴጥ. 4:4) ጠባያችን ለሐሜት በር የሚከፍት እንዳይሆን መጠንቀቅ አለብን። (1 ጴጥ. 2:12) የዕለት ተዕለት ሥራችን ለምናመልከው አምላክ ክብር የሚያመጣ ከሆነ በከፍታ ቦታ ላይ እንደተቀመጠ መብራት ልንሆንና ሰዎች ይሖዋ ወዳዘጋጀው ሰላማዊ መጠለያ እንዲመጡ ልንረዳቸው እንችላለን።—ማቴ. 5:14-16