“ጊዜ ማግኘት የምችለው እንዴት ነው?”
1 ሕይወታችን በተለያዩ እንቅስቃሴዎች የተሞላ ስለሆነ ብዙዎቻችን ከላይ እንዳለው በማለት ስናማርር ይሰማል። ካሉን ንብረቶች ሁሉ እጅግ ውድ የሆነውና የማይበረክተው ጊዜ እንደሆነ ይነገራል። ታዲያ የአምላክን ቃል እንደ ማንበብና ማጥናት ለመሳሰሉት በጣም አስፈላጊ የሆኑ ጉዳዮች ጊዜ ልናገኝ የምንችለው እንዴት ነው?—ፊልጵ. 1:10
2 ቁልፉ ተጨማሪ ጊዜ ለማግኘት መሞከር ሳይሆን ባለን ጊዜ ምን ማድረግ እንደምንፈልግ መወሰን ነው። ሁላችንም በሳምንት 168 ሰዓታት ሲኖሩን ከዚህ ውስጥ ወደ 100 ሰዓት ገደማ በእንቅልፍና በሥራ እናሳልፋለን። እንግዲያው የቀረውን ሰዓት ይበልጥ ውጤታማ በሆነ መንገድ ልንጠቀምበት የምንችለው እንዴት ነው? ኤፌሶን 5:15-17 ‘ጥበብ እንደሌላቸው ሳይሆን እንደ ጥበበኞች እንድንመላለስ፣ ዘመኑን እንድንዋጅና የጌታ ፈቃድ ምን እንደሆነ እንድናስተውል’ አጥብቆ ይመክረናል። ይህም ይሖዋ በጣም አስፈላጊ ናቸው ያላቸውን ነገሮች ሁሉ ለማድረግ እያንዳንዱን አጋጣሚ በሚገባ የመጠቀምን አስፈላጊነት ያሳያል።
3 ኢየሱስ ያለንበትን ጊዜ ከኖህ ዘመን ጋር አመሳስሎታል። (ሉቃስ 17:26, 27) በዚያን ዘመን የነበሩት ሰዎች በዕለት ተዕለት የኑሮ ጉዳዮች ተጠምደው ነበር። ይሁን እንጂ ኖህ ግዙፍ መርከብ ለመገንባት እንዲሁም ለመስበክ የሚያስችለውን ጊዜ መዋጀት ችሏል። (ዕብ. 11:7፤ 2 ጴጥ. 2:5) እንዴት? የአምላክን ፈቃድ በማስቀደምና እንደታዘዘው ሁሉ “እንዲሁ” በማድረግ ነው።—ዘፍ. 6:22
4 ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው ምንድን ነው? ኢየሱስ “ሰው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣ ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም” በማለት ተናግሯል። (ማቴ. 4:4) በየሳምንቱ ‘መንፈሳዊ ምግብ በጊዜው’ ይቀርብልናል። (ሉቃስ 12:42) ይህንን ምግብ ከሰውነታችን ጋር በማዋሃድ በይበልጥ ተጠቃሚ ለመሆን ቋሚ የሆነ የግል ንባብና የጥናት ፕሮግራም ሊኖረን ይገባል። ለሚቀርብልን መንፈሳዊ ምግብ የአመስጋኝነት መንፈስ ካለን በጥድፊያ ላይ ያለ ሰው ዋጥ ዋጥ እያደረገ ሊመገበው እንደሚችል ‘ፈጣን ምግብ’ አድርገን አንመለከተውም። ከዚህ ይልቅ ተገቢ የሆነ አድናቆት መንፈሳዊ የሆኑ ነገሮችን ጊዜ ወስደን እንድናጠናና በሚገባ እንድናጣጥም ይገፋፋናል።
5 መንፈሳዊ ምግብ መመገብ ዘላለማዊ ሕይወት ያስገኛል። (ዮሐ. 17:3) በዕለታዊ ፕሮግራማችን ውስጥ ቀዳሚ ስፍራ ሊሰጠው ይገባል። በየዕለቱ መጽሐፍ ቅዱስን ለማንበብና ለክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ለመዘጋጀት የሚሆን ጊዜ ማግኘት እንችላለን? አዎን፣ እንችላለን። እንዲህ ካደረግን የአምላክን ፈቃድ በማወቅና በመፈጸም ‘እጅግ እንጠቀማለን።’—መዝ. 19:7-11