መንፈሳዊ ግብ አውጡ
1 ይሖዋን ለዘላለም ማወደስ ምንኛ ታላቅ መብት ነው! እዚህ ግብ ላይ ለመድረስ አሁን ልናከናውናቸው የምንችላቸው ሌሎች መንፈሳዊ ግቦች ልናወጣና እነዚህ ግቦች ላይ ለመድረስ ጥረት ልናደርግ እንችላለን። ይህም ጥረታችን መና ሆኖ እንዳይቀር ይረዳናል። (1 ቆሮ. 9:26) ምን ዓይነት ግቦች ልናወጣ እንችላለን?
2 የግል የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት:- ለሁሉም የጉባኤ ስብሰባዎች ትዘጋጃለህ? የምትዘጋጅ ከሆነ ምርምር ለማድረግና ለማሰላሰል ጊዜ ትመድባለህ? ለምሳሌ ያህል በየሳምንቱ ለሚደረገው የመጠበቂያ ግንብ ጥናት ወይም የጉባኤ የመጽሐፍ ጥናት የምትዘጋጀው መልሶቹን ሰመር ሰመር እያደረግህ ነው? ወይስ ጥቅሶቹን አውጥተህ እያነበብክ በቀረበው ማብራሪያ ላይ ታሰላስላለህ? ለቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከተመደበው የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ ፕሮግራም ላይ ጥቂት ነጥቦችን ወስደህ በየሳምንቱ ምርምር ለማድረግ ግብ ልታወጣ ትችላለህ? እንዲህ ዓይነቱን መንፈሳዊ ቁፋሮ ለማድረግ ጊዜና ጥረት የሚጠይቅ ቢሆንም የተትረፈረፈ በረከት ያስገኛል።—ምሳሌ 2:4, 5
3 የጉባኤ ስብሰባዎች:- ሌላው ልታወጣው የምትችለው ግብ በአምስቱም የጉባኤ ስብሰባዎች ላይ አዘውትሮ መገኘት ነው። ከእምነት አጋሮቻችን ጋር ለመጨዋወትና በመክፈቻው መዝሙርና ጸሎት ላይ ለመካፈል ቀደም ብሎ መምጣት የጉባኤውን መንፈስ ለማጠናከር ይረዳል። በሁሉም ስብሰባዎች ላይ ተሳትፎ ለማድረግ እንዲሁም የምንሰጠውን ሐሳብ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሻሻልን ለመሄድ ጥረት ልናደርግ እንችላለን። ምናልባትም በአንቀጹ ውስጥ የሚገኝ አንድ ጥቅስ ከውይይቱ ጋር እንዴት እንደሚዛመድ ወይም በርዕሱ ሥር የቀረበው ሐሳብ በዕለት ተዕለት ሕይወታችን ውስጥ እንዴት በሥራ ላይ ሊውል እንደሚችል ልታብራራ ትችላለህ።—ዕብ. 10:24, 25
4 የመስክ አገልግሎት:- ግብ አውጥተን የምናገለግል ከሆነ በአገልግሎታችን ትልቅ መሻሻል እናደርጋለን። በየወሩ በአገልግሎት ይሄን ያህል ሰዓት አሳልፋለሁ ብለህ በግልህ ግብ ታወጣለህ? አንዳንዶች እንዲህ ማድረጉ ጠቃሚ ሆኖ አግኝተውታል። ከቤት ወደ ቤት በሚደረገው አገልግሎት መጽሐፍ ቅዱስ መጠቀምን፣ ውጤታማ የሆኑ ተመላልሶ መጠየቆች ማድረግን፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ማስጀመርን በመሰሉ የአገልግሎት ዘርፎች እድገት ማድረግ ወይም ጥናቶችን ይበልጥ ውጤታማ በሆነ መንገድ ማስተማር ትችላለህ?
5 ወላጆች ልጆቻችሁ በይሖዋ አገልግሎት ግብ እንዲያወጡ እያበረታታችኋቸው ነው? አቅኚ ወይም የቤቴል ቤተሰብ አባል ሆኖ ማገልገል ለይሖዋ ያላቸውን ጥልቅ አድናቆት ማሳየት የሚችሉበት ግሩም መንገድ መሆኑን እንዲያስተውሉ እርዷቸው።—መክ. 12:1
6 እንቅስቃሴያችንን ስንመረምር፣ መንፈሳዊ ግቦች ስናወጣና እነዚህ ግቦች ላይ ለመድረስ ስንጥር ከአገልግሎታችን የላቀ ደስታ እናገኛለን፤ ለሌሎችም የብርታት ምንጭ እንሆናለን።—ሮሜ 1:12