አዲስ የልዩ ስብሰባ ቀን ፕሮግራም
ዛሬ ዛሬ ረዥምና አስደሳች ሕይወት ለመኖር የልባችንን ጤንነት መጠበቅ እንደሚያስፈልግ ብዙ ይነገራል። ከዚህ ይበልጥ አስፈላጊ የሆነው ግን የምሳሌያዊ ልባችንን ጤንነት መጠበቅ ነው። በመሆኑም በ2004 የሚጀምረው የልዩ ስብሰባ ቀን ፕሮግራም “ይሖዋን በሙሉ ልብ ማገልገል” የሚል ጭብጥ ያለው መሆኑ ተገቢ ነው። (1 ዜና 28:9) በዚህ ስብሰባ ላይ ምን ነገሮችን እንማራለን?
የወረዳ የበላይ ተመልካቹ “ሌሎች ይሖዋን በበጎ ፈቃድ እንዲያገለግሉት መርዳት” በሚል ጭብጥ ንግግር ያቀርባል። ሰዎች ለምሥራቹ ፍላጎት እንዲያዳብሩ መርዳትና ይሖዋን ማገልገል የሚፈልጉትን መጽሐፍ ቅዱስ ማስጠናት የሚያስገኘውን ደስታ የሚያጎሉ ቃለ ምልልሶች ይኖራሉ። “በመከራ በተሞላ ዓለም ውስጥ ልባችንን መጠበቅ” በሚል ጭብጥ የአውራጃ የበላይ ተመልካቹ የሚያቀርበው የመጀመሪያ ንግግሩ በስብሰባው ላይ የሚገኙትን ሁሉ እንደሚያጽናና እና እንደሚያበረታታ አያጠራጥርም። የጠዋቱ ክፍለ ጊዜ በጥምቀት ንግግር ይደመደማል።
ከሰዓት በኋላ “የእርዳታ እጃችንን መዘርጋት” በሚለው ንግግር ላይ ሌሎችን እንዴት መርዳት እንደምንችል ይብራራል። ወላጆች የልጆቻቸውን ልብ ከመጥፎ ተጽዕኖዎች ለመጠበቅና ወደ ይሖዋ እንዲቀርቡ ለመርዳት ምን ማድረግ ይችላሉ? “ልጆቻችሁ በይሖዋ እንዲደሰቱ እርዷቸው” በሚለው ንግግር ላይ ጠቃሚ የሆኑ ሐሳቦች የሚቀርቡ ከመሆኑም በላይ እንዴት ተግባራዊ ማድረግ እንደሚቻልም በሠርቶ ማሳያ ይታያል።
የምሳሌያዊ ልባችንን ጤንነትና ጥንካሬ ለመጠበቅ ይሖዋ በሚያደርግልን ዝግጅቶች ሁሉ እየተጠቀምን ነው? “ይሖዋን ስታገለግሉ ፍጹም ልብ ይኑራችሁ” በሚል ርዕስ በጎብኚ ተናጋሪው የሚቀርብልን የመደምደሚያ ንግግር መንፈሳዊነታችንን ለመጠበቅ በሚያስችሉን አራት ዘርፎች ላይ የሚያተኩር ይሆናል። ልባዊ ጸሎት ለማቅረብ፣ የአምላክን ቃል ለማጥናት፣ በስብከቱ ሥራ በቅንዓት ለመካፈልና ከሌሎች ክርስቲያኖች ጋር ለመሰብሰብ ምን ያህል ጊዜ እንመድባለን? ምን ያህልስ ጥረት እናደርጋለን? በእነዚህ ዘርፎች ረገድ ማሻሻያ ማድረግ እንችል ይሆን?
ይሖዋ “ልብህን ለተግሣጽ ስጥ፣ ጆሮህንም ወደ እውቀት ቃል” በማለት ግብዣ አቅርቦልናል። (ምሳሌ 23:12) መንፈሳዊ መመሪያ በሚገኝበት በዚህ ጠቃሚ ስብሰባ ላይ ለመገኘት ከወዲሁ እቅድ አውጣ። እንዲህ ካደረግህ ይሖዋን በፍጹም ልብና በበጎ ፈቃድ ማገልገልህን ለመቀጠል የሚያስችል ብርታት ታገኛለህ።