አዲስ የልዩ ስብሰባ ቀን ፕሮግራም
የልዩ ስብሰባ ቀን ዝግጅት የጀመረው በ1987 ነው። ይህ የአንድ ቀን ስብሰባ ለይሖዋ አገልጋዮችም ሆነ በስብሰባው ላይ ለሚገኙት ፍላጎት ያላቸው ሰዎች የሚያንጽ ሆኖ ተገኝቷል። ከመስከረም 1998 ጀምሮ ደግሞ አዲስ የልዩ ስብሰባ ቀን ፕሮግራም ይጀምራል። በስብሰባው ላይ የሚቀርቡት ዘጠኝ ንግግሮችና በርካታ ቃለ ምልልሶች እንዲሁም ተሞክሮዎች ለመንፈሳዊነታችሁ ጠቃሚዎች ሆነው ታገኟቸዋላችሁ።
የአዲሱ ፕሮግራም ጭብጥ “ለይሖዋ ማዕድ አድናቆት ይኑራችሁ” የሚል ነው። (ኢሳ. 65:14፤ 1 ቆሮ. 10:21) ስብሰባው ለይሖዋ ለምናቀርበው አምልኮ በሕይወታችን ውስጥ ቀዳሚውን ቦታ ለመስጠት ያደረግነውን ቁርጥ ውሳኔ የሚያጠናክርልን ይሆናል። (መዝ. 27:4) የወረዳ የበላይ ተመልካቹ ንግግር በስብሰባዎች ላይ ስለመገኘት “የልባችንን ዝንባሌ መመርመር” በሚል ርዕሰ ጉዳይ ላይ ያተኮረ ይሆናል። እንግዳ ተናጋሪው “ከይሖዋ ማዕድ በመመገብ መንፈሳዊነታችንን መጠበቅ” የምንችለው እንዴት እንደሆነ ያብራራል። በይሖዋ ድርጅት ውስጥ ላሉት ወጣቶች አምላክን በማገልገል እንዲጸኑ የሚያበረታታ ተግባራዊ የሆኑ ሐሳቦች ያቀርብላቸዋል። ጎብኚ ተናጋሪው የሚያቀርበው ዋናው ንግግር “ድፍረት የተሞላበት ምሥክርነት ለመስጠት በመንፈሳዊ የበረቱ መሆን” የሚል ርዕስ ያለው ሲሆን በጉባኤ በኩል የሚቀርቡልን ዝግጅቶች መንግሥቱን በድፍረት እንድናውጅ የሚያስታጥቁን እንዴት እንደሆነ ይገልጻል። ከዚህ ፕሮግራም መጠቀም የማይፈልግ ማን አለ?
በቅርቡ ራሳቸውን የወሰኑና ለመጠመቅ የሚፈልጉ ሁሉ ስማቸውን ለሰብሳቢ የበላይ ተመልካቹ ሳይዘገዩ መስጠት ይኖርባቸዋል። የልዩ ስብሰባ ቀን ዝግጅት የተጀመረበትን 12ኛውን ዓመት ስንጀምር በስብሰባው ላይ የሚገኙ ሁሉ ከፊታችን ለሚጠብቀን ሥራ መንፈሳዊ ብርታት እንደሚያገኙ እርግጠኞች ነን።