አዲስ የልዩ ስብሰባ ቀን ፕሮግራም
ዓይን የተሠራበት መንገድ በጣም የሚያስደንቅ ነው። (መዝ. 139:14) ሆኖም በአንድ ጊዜ ሊያተኩር የሚችለው አንድ ነገር ላይ ብቻ ነው። ይህ አባባል ለሥጋዊም ሆነ ለመንፈሳዊ ዓይናችን ይሠራል። ጥርት ያለ መንፈሳዊ እይታ እንዲኖረን ትኩረታችን የአምላክን ፈቃድ በማድረግ ላይ ያነጣጠረ መሆን ይኖርበታል። የሰይጣን ዓለም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመሩ የመጡ ትኩረት የሚከፋፍሉ ነገሮች ያሉት እንደመሆኑ መጠን በ2006 የአገልግሎት ዓመት የምናደርገው የልዩ ስብሰባ ቀን ፕሮግራም ጭብጥ “ጤናማ ዓይን ይኑራችሁ” የሚል መሆኑ ምንኛ የተገባ ነው!—ማቴ. 6:22
ከይሖዋ በረከት ለማግኘት በበኩላችን ማድረግ የሚኖርብን ነገር ምንድን ነው? (ምሳሌ 10:22) ይህ ጥያቄ “ጤናማ ዓይን በመያዝ በረከት እጨዱ” በሚለው ንግግር ላይ መልስ ያገኛል። የመጽሐፍ ቅዱስን መሠረታዊ ሥርዓቶች በሥራ ላይ ማዋላችን ምን ጥቅም እንደሚያስገኝ በቃለ ምልልሶቹ ላይ ይጎላል። “ክፉ በሆነ ዓለም ውስጥ ጤናማ ዓይን መያዝ” የሚለው የጎብኚ ተናጋሪው የመጀመሪያ ንግግር ሕይወታችንን ውስብስብ የሚያደርጉብንንና ቀስ በቀስ መንፈሳዊነታችንን የሚያንቁብንን ነገሮች በተመለከተ ማስጠንቀቂያ ይዟል። እንዲሁም “የሚሻለውን ድርሻ” መምረጥ ምን ነገሮችን እንደሚያካትት እንማራለን።—ሉቃስ 10:42
ወላጆችም ሆኑ ሌሎች ወንድሞች፣ ወጣት ክርስቲያኖች በመንፈሳዊ ግቦች ላይ እንዲያተኩሩ እንዴት ሊረዷቸው ይችላሉ? በዚህ ወሳኝ ጥያቄ ዙሪያ ወጣቶችም ሆኑ ወላጆች የሚሰጡት ሐሳብ “ፍላጾቻቸውን አስተካክለው የሚያነጣጥሩ ወላጆች” እና “መንፈሳዊ ግቦች ላይ ለመድረስ የሚጣጣሩ ወጣቶች” በሚሉት ክፍሎች ላይ ይቀርባል። (መዝ. 127:4) ጎብኚ ተናጋሪው በሚያቀርበው የመደምደሚያ ንግግር ላይ በግለሰብ፣ በቤተሰብና በጉባኤ ደረጃ ከይሖዋ ድርጅት ጋር እንዴት ወደፊት መጓዝ እንደምንችል ይብራራልናል።
በእውነት ውስጥ ለአሥርተ ዓመታት የቆየንም እንሁን አዲሶች ‘ጤናማ ዓይን መያዛችን’ በጣም አስፈላጊ ነገር ነው። የልዩ ስብሰባው ቀን ፕሮግራም እንዲህ እንድናደርግ ይረዳናል።