እርስ በርሳችሁ መተናነጻችሁን ቀጥሉ
1 ሐዋርያው ጳውሎስ የእምነት ባልንጀሮቹን ለማበርታት የቻለውን ሁሉ አድርጎ ነበር። (ሥራ 14:19-22) እኛም በተመሳሳይ ወንድሞቻችን ችግር ላይ ሲወድቁ እናዝናለን፤ ልንረዳቸውም እንፈልጋለን። መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚጠቁመው ሽማግሌዎች ብቻ ሳይሆኑ ሁሉም ክርስቲያኖች የሌሎች ችግር ሊያሳስባቸው ይገባል። (ሮሜ 15:1, 2) “እርስ በርሳችሁ ተጽናኑ፤ አንዱም ሌላውን ያንጽ” የሚለውን ፍቅራዊ ማሳሰቢያ በተግባር ማዋል የምንችልባቸውን ሁለት መንገዶች እንመልከት።—1 ተሰ. 5:11
2 የሌሎችን ፍላጎት አስተውል:- ዶርቃ ዘወትር “በትጋት በጎ ነገር እያደረገችና ድኾችን እየረዳች ትኖር” እንደነበር የአምላክ ቃል ይናገራል። (ሥራ 9:36, 39) በችግር ላይ ያሉት እነማን እንደሆኑ ካስተዋለች በኋላ እነርሱን ለመርዳት የምትችለውን ሁሉ ታደርግ ነበር። እንዴት ያለ ግሩም ምሳሌ ትታልናለች! አንድ አዛውንት ወንድም ወደ ስብሰባ ለመሄድ እርዳታ ያስፈልጋቸው ይሆናል። አሊያም አንድ አቅኚ ወንድም በሥራ ቀናት ውስጥ ከሰዓት በኋላ ላይ አብሮት የሚያገለግል ሰው ይፈልግ ይሆናል። አንድ ሰው እንዲህ ያለ ችግር እንዳለበት አስተውለህ እርዳታ ብታደርግለት እንዴት ሊበረታታ እንደሚችል እስቲ ገምት!
3 መንፈሳዊ ጭውውት:- ከዚህ በተጨማሪ በንግግራችን ሌሎችን ማነጽ እንችላለን። (ኤፌ. 4:29) ተሞክሮ ያለው አንድ ሽማግሌ እንዲህ ብሏል:- “ሌሎችን ማበረታታት ከፈለጋችሁ መንፈሳዊ ነገሮችን አንስታችሁ ተጫወቱ። የሚያንጽ ጭውውት ለመጀመር ‘እውነትን የሰማኸው እንዴት ነው?’ እንደሚለው ያሉ ቀላል ጥያቄዎችን መጠየቅ ትችላላችሁ።” በጉባኤህ ውስጥ ላሉ ወጣቶች ልባዊ አሳቢነት ይኑርህ። ላዘኑትም ይሁን ዓይን አፋር ለሆኑት አሳቢነት አሳይ። (ምሳሌ 12:25) ስለ ዓለማዊ መዝናኛ ብቻ በማውራት ከእምነት ባልንጀሮችህ ጋር ጥሩ መንፈሳዊ ጭውውት የምታደርግበት ጊዜ እንዳታጣ ተጠንቀቅ።—ሮሜ 1:11, 12
4 ሆኖም ሌሎችን ለማነጽ ስለ ምን ጉዳይ ማንሳት ትችላለህ? ሰሞኑን መጽሐፍ ቅዱስን ስታነብ ወይም ስታጠና ለይሖዋ ያለህን አድናቆት ከፍ የሚያደርግ ግሩም መሠረታዊ ሥርዓት አላገኘህም? በሕዝብ ንግግር አሊያም በመጠበቂያ ግንብ ጥናት ላይ እንድትበረታታ ያደረገህ የሰማኸው ነጥብ የለም? ወይም በዚህ ሰሞን ልብ የሚነካና እምነት የሚያጠናክር አንድ ተሞክሮ አልሰማህም? እንዲህ ያሉትን መንፈሳዊ ሀብቶች በልብህ ብታኖር ምንጊዜም ቢሆን ለሌሎች የምታካፍለው አበረታች ሐሳብ አታጣም።—ምሳሌ 2:1፤ ሉቃስ 6:45
5 በተግባር የተደገፈ እርዳታ በመስጠት እንዲሁም አንደበታችንን በጥበብ በመጠቀም አንዳችን ሌላውን ማነጻችንን እንቀጥል።—ምሳሌ 12:18