“መልስህ ምንድን ነው?”
1. አብዛኞቻችን ምን ነገር ያስቸግረናል?
1 መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ ብትወድም እንኳ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የሚገኙት ታሪኮች ዝርዝር ሁኔታ ወይም አንዳንድ አነጋገሮች በቅዱሳን ጽሑፎች ውስጥ የት ቦታ እንደሚገኙ ማስታወስ ይከብድሃል? ልጆችህ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስለሚገኙት መሠረታዊ ትምህርቶች ትክክለኛ እውቀት እንዲኖራቸው ትፈልጋለህ? በንቁ! መጽሔት ገጽ 31 ላይ የሚወጣው “መልስህ ምንድን ነው?” የሚለው አምድ ልጆችም ሆኑ አዋቂዎች ስለ አምላክ ቃል የተሻለ እውቀት እንዲኖራቸው ይረዳል።—ሥራ 17:11
2. “መልስህ ምንድን ነው?” የሚለው የንቁ! መጽሔት አምድ ያሉትን በርካታ ገጽታዎች እንዴት ልንጠቀምባቸው እንችላለን?
2 ይህንን የንቁ! መጽሔት አምድ በጥሩ ሁኔታ መጠቀም የምትችለው እንዴት ነው? የጥር 2006 ንቁ! የሚከተለውን ሐሳብ ሰጥቶ ነበር:- “የዚህን እትም ገጽ 31 እስቲ ተመልከት። በዚያ ላይ የሚገኙት አንዳንዶቹ ክፍሎች የወጣቶችን ትኩረት የሚስቡ ናቸው፤ ሌሎቹ ደግሞ የቆዩ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎችን የማስታወስ ችሎታ የሚፈትኑ ይሆናሉ። ‘ዘመኑ መቼ ነበር?’ የሚለው ክፍል መጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተጠቀሱ ሰዎች መቼ እንደኖሩና ዓበይት ክንውኖች የተፈጸሙት መቼ እንደሆነ የጊዜ ቅደም ተከተሉን እንድታውቁ ይረዳችኋል። የአብዛኞቹ ጥያቄዎች መልሶች በዚያው እትም በተወሰነ ገጽ ላይ ተገልብጠው የሚጻፉ ሲሆን ‘ከዚህ እትም’ በሚለው ሥር ያሉት ጥያቄዎች መልሶች ደግሞ መጽሔቱ ውስጥ በተለያዩ ገጾች ላይ ይገኛሉ። መልሶቹን ከማንበባችሁ በፊት ለምን ጥቂት ምርምር አታደርጉም? ከዚያም ያገኛችሁትን እውቀት ለሌሎች ማካፈል ትችላላችሁ። በተጨማሪም ‘መልስህ ምንድን ነው?’ የሚለውን ይህን አዲስ ገጽታ ከቤተሰባችሁ ወይም ከሌሎች ሰዎች ጋር የመጽሐፍ ቅዱስ ውይይት ለማድረግ ልትጠቀሙበት ትችላላችሁ።”
3. አንዳንድ ቤተሰቦች ከዚህ አምድ ጥቅም ማግኘት የቻሉት እንዴት ነው? አንተስ በጣም የወደድከው የትኛውን ገጽታ ነው?
3 በእርግጥም በርካታ ቤተሰቦች ይህንን ክፍል በቤተሰብ ጥናታቸው ላይ ውይይት ለማድረግ ተጠቅመውበታል። አንዲት እናት እንዲህ በማለት ጽፋለች:- “እኔና ባለቤቴ የቤተሰብ ጥናታችን ለሦስት ዓመት ሴት ልጃችን ሕያውና ማራኪ እንዲሆን ለማድረግ ስንል ‘ለልጆች የቀረበ የሥዕል ጥያቄ’ የሚለውን ክፍል ማካተታችን ጥሩ እንደሆነ ተሰምቶናል። ልጃችን የራሷን የንቁ! መጽሔት እትም ወስዳ ይህንን ክፍል እስክታገኝ ድረስ እያንዳንዱን ገጽ እየገለጠች በጉጉት ስትመለከት ማየት የሚያስደስት ነው።” በብራዚል የሚኖር አንድ አባት ደግሞ “እኔና የሰባት ዓመት ልጄ በንቁ! ላይ የሚወጣውን ይህንን አምድ በጣም ወደነዋል። ልጄ ሞይዚዝ በትኩረት እንዲከታተለው፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶችን እንዲያወጣ፣ የሥዕሎቹን ትርጉም እንዲያስተውልና የተፈጸሙበትን ዘመን እንዲያውቅ ረድቶታል” ብሏል። የስምንት ዓመቷ አሽሊ እንዲህ ስትል ጽፋለች:- “በንቁ! መጽሔት መጨረሻ ገጽ አካባቢ ለምታወጡት ‘መልስህ ምንድን ነው?’ ለሚለው አምድ በጣም አመሰግናችኋለሁ። ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ብዙ እውቀት አግኝቼበታለሁ።”
4. ቤተሰቦች “መልስህ ምንድን ነው?” የሚለውን አምድ በቤተሰብ ጥናታቸው ላይ እንዴት ሊጠቀሙበት ይችላሉ?
4 “መልስህ ምንድን ነው?” የሚለውን አምድ አልፎ አልፎ በቤተሰብ ጥናታችሁ ላይ ለምን አታካትቱትም? ይበልጥ አስቸጋሪ ለሆኑ አንዳንድ ጥያቄዎች መልስ ለማግኘት የመጠበቂያ ግንብ ማኅበር ጽሑፎች ማውጫን ወይም በሲዲ የተዘጋጀውን ዎች ታወር ላይብረሪ መጠቀም ትችላላችሁ። በዚህ መንገድ ልጆቻችሁን እንዴት ምርምር ማድረግ እንደሚችሉ ልታስተምሯቸው ትችላላችሁ። ትልልቅ ልጆች ካሏችሁ “እኔ ማን ነኝ?” ወይም “ዘመኑ መቼ ነበር?” በሚሉት ክፍሎች ውስጥ በሚገኙት ጥያቄዎች ላይ ምርምር አድርገው እንዲመጡ ለምን አታደርጉም? ከዚያም በጥናቱ ወቅት በምርምር ያገኙትን ውጤት ለቤተሰቡ ማካፈል ይችላሉ። ይህ የንቁ! መጽሔት አምድ ወላጆች በልጆቻቸው ልብ ውስጥ የአምላክን ቃል ለመቅረጽ ከሚያስችሏቸው መንገዶች መካከል አንዱ ነው። ወላጆች ይህን አምድ ውጤታማ በሆነ መንገድ መጠቀማቸው ልጆቻቸው ከሕፃንነታቸው ጀምሮ “ቅዱሳት መጻሕፍትን” እንዲያውቁ ለመርዳት ያስችላቸዋል።—2 ጢሞ. 3:15፤ ዘዳ. 6:7