የጥያቄ ሣጥን
◼ በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ ለመማር አመቺ ሁኔታ እንዲኖር ሁሉም አስተዋጽኦ ማበርከት የሚችሉት እንዴት ነው? (ዘዳ. 31:12)
ለይሖዋና ለጉባኤ ስብሰባዎች ካለን ጥልቅ አክብሮት የተነሳ ሁላችንም ቀደም ብለን መንግሥት አዳራሽ እንድንደርስና ከይሖዋ ለመማር ራሳችንን እንድናዘጋጅ ማበረታቻ ይሰጠናል። የኋለኞቹን መቀመጫዎች ትንንሽ ልጆች ላሏቸው ወንድሞችና አልፎ አልፎ ዘግይተው ለሚመጡ ሰዎች በመተው ከፊት ያሉትን መቀመጫዎች መያዝ ጥሩ ነው። እንደ ሞባይል ስልክ ያሉ የኤሌክትሮኒክ መሣሪያዎች ተሰብሳቢዎችን እንዳይረብሹ ስብሰባው ከመጀመሩ በፊት አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል። በስብሰባ ላይ የተገኙ ሁሉ ፕሮግራሙ ተጀምሮ እስኪጠናቀቅ ድረስ ለስብሰባዎች ጥልቅ አክብሮት የሚያሳዩ ከሆነ የሚረብሹ ነገሮች ብዛትና ዓይነት ይቀንሳሉ።—መክ. 5:1፤ ፊልጵ. 2:4
አዳዲስ ሰዎች በስብሰባዎች ላይ መገኘት ሲጀምሩ እነሱን የሚያውቅ ወንድም ወይም እህት አብሯቸው ቢቀመጥ ጥሩ ነው። በተለይ ደግሞ እንግዶቹ ሥልጠና የሚያስፈልጋቸው ትንንሽ ልጆች ይዘው የሚመጡ ከሆነ እንዲህ ማድረጉ በጣም ጠቃሚ ነው። ለዚህ ቤተሰብ በስብሰባዎች ላይ መገኘት አዲስ ነገር ሊሆን ይችላል። በመሆኑም ወላጆች ለሕፃናት ልጆቻቸው የሚያስፈልገውን ነገር ለማድረግ ከአዳራሹ መውጣት ቢያስፈልጋቸው ሌሎችን እንዳይረብሹ ከኋላ መቀመጥን ሊመርጡ ይችላሉ። (ምሳሌ 22:6, 15) ልጆች እንደልባቸው መረበሽ እንደሚችሉ ሊሰማቸው ስለሚችል ትንንሽ ልጆች ያላቸው ቤተሰቦች ሁለተኛው አዳራሽ ወይም ሌላ ክፍል ውስጥ መቀመጥ የለባቸውም። ልጆችን ለመቅጣትም ሆነ ሌላ አስፈላጊ ነገር ለማድረግ ወላጅ ልጁን ከአዳራሹ ይዞ መውጣቱ የተሻለ ነው፤ የሚፈልጉትን ነገር አድርገው ከጨረሱ በኋላ ወደ አዳራሹ ሊመለሱ ይችላሉ።
አስተናጋጆች በይሖዋ አምልኮ ቤት ውስጥ ተገቢ የሆነ መንፈስ እንዲንጸባረቅ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ያደርጋሉ። ቤተሰቦች ወይም አልፎ አልፎ ዘግይተው የሚመጡ ሰዎች መቀመጫ እንዲያገኙ ይረዳሉ። አስተናጋጆች፣ ሌሎች መቀመጫ እንዲያገኙ ሲረዱ ተሰብሳቢዎችን እንዳይረበሹ ተጠንቅቀው በዘዴ ሥራቸውን ያከናውናሉ። ያልተጠበቀ ሁኔታ በሚያጋጥምበት ጊዜ የማመዛዘን ችሎታቸውን ተጠቅመው ሁኔታውን ለማስተካከል ይሞክራሉ። አንድ ልጅ ሌሎችን እየረበሸ ካስቸገረ አስተናጋጆች ወላጆቹን ለመርዳት ፈቃደኞች መሆናቸውን ሊገልጹ ይችላሉ።
በመንግሥት አዳራሽ ለአምልኮ የሚሰበሰቡ ሁሉ ስለ ይሖዋ እንዲሁም ሰላምና ጽድቅ የሰፈነበት አዲስ ዓለም ለማምጣት ስላለው ዓላማ ለመማር የሚያመች ሁኔታ እንዲኖር የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ማበርከት ይችላሉ።—ዕብ. 10:24, 25