ቅድሚያ ልንሰጠው የሚገባ ነገር
1. ኢየሱስ ለአገልግሎት ትልቅ ቦታ እንደሚሰጥ ያሳየው እንዴት ነበር?
1 ኢየሱስ ለአገልግሎት ቅድሚያ ይሰጥ ነበር። በፓለስቲና ምድር በመቶ የሚቆጠሩ ኪሎ ሜትሮች በእግሩ በመጓዝ በተቻለው መጠን ለብዙ ሰዎች ለመስበክ ከፍተኛ ጥረት አድርጓል። ቀለል ያለ ሕይወት ይመራ የነበረ መሆኑ ለአገልግሎቱ ተጨማሪ ጊዜና ትኩረት ለመስጠት አስችሎታል። (ማቴ. 8:20) ሕዝቡ ከእነሱ ጋር ቆይቶ የታመሙ ሰዎችን እንዲፈውስላቸው ለማድረግ በሞከሩ ጊዜ “ለሌሎች ከተሞችም የአምላክን መንግሥት ምሥራች ማወጅ አለብኝ፤ ምክንያቱም የተላክሁት ለዚህ ዓላማ ነው” ብሏቸዋል።—ሉቃስ 4:43
2. ኢየሱስ ለአገልግሎት ትልቅ ቦታ ይሰጥ የነበረው ለምንድን ነው?
2 ኢየሱስ ለአገልግሎት ትልቅ ቦታ ይሰጥ የነበረው ለምንድን ነው? የይሖዋ ስም መቀደስ ከምንም በላይ ያሳስበው ስለነበረ ነው። (ማቴ. 6:9) ኢየሱስ በሰማይ ያለውን አባቱን ይወድ ነበር፤ ይህ ደግሞ የአባቱን ፈቃድ እንዲፈጽምና ሙሉ በሙሉ እንዲታዘዘው አነሳስቶታል። (ዮሐ. 14:31) በተጨማሪም ለሕዝቡ ከልብ ያስብ የነበረ ከመሆኑም ሌላ ሊረዳቸው ይፈልግ ነበር።—ማቴ. 9:36, 37
3. አገልግሎታችን ቅድሚያ የምንሰጠው ነገር መሆኑን እንዴት ማሳየት እንችላለን?
3 ኢየሱስን ምሰሉ፦ በዓለም ውስጥ ጊዜያችንን የሚሻሙና ትኩረታችንን የሚሰርቁ በርካታ ነገሮች መኖራቸው ኢየሱስ እንዳደረገው ለአገልግሎታችን ቅድሚያ መስጠት ተፈታታኝ እንዲሆንብን ያደርጋል። (ማቴ. 24:37-39፤ ሉቃስ 21:34) ስለዚህ ለአገልግሎት ለመዘጋጀትና በስብከቱ ሥራ አዘውትረን ለመካፈል ጊዜ በመመደብ ይበልጥ አስፈላጊ የሆኑትን ነገሮች ለይተን እንደምናውቅ ማሳየት ይኖርብናል። (ፊልጵ. 1:10) እንግዲያው ቀለል ያለ ሕይወት ለመምራት ጥረት በማድረግ ዓለምን ሙሉ በሙሉ ከመጠቀም እንራቅ።—1 ቆሮ. 7:31
4. በጣም አስፈላጊ ለሆኑ ነገሮች አሁኑኑ ቅድሚያ መስጠት ያለብን ለምንድን ነው?
4 አስተዋይ የሆነ ሰው ጊዜው ሲጣበብበት ይበልጥ አስፈላጊ የሆኑ ነገሮችን በቅድሚያ ያከናውናል። ለምሳሌ ይህ ሰው አደገኛ አውሎ ነፋስ እየመጣ መሆኑን ካወቀ ያለውን ጊዜና ጉልበት ቤተሰቡን ከአደጋ ማዳን የሚችልበትን ዝግጅት ለማድረግ ብሎም ጎረቤቶቹን ለማስጠንቀቅ ይጠቀምበታል። እምብዛም አስፈላጊ ያልሆኑ ነገሮችን በሌላ ጊዜ ማከናወን ይችላል። የአርማጌዶን ጥፋት ሊመጣ የቀረው ጊዜ በጣም አጭር ነው። (ሶፎ. 1:14-16፤ 1 ቆሮ. 7:29) የእኛንም ሆነ የሚሰሙንን ሰዎች ሕይወት ለማዳን በጉባኤ ውስጥም ሆነ ከጉባኤ ውጭ ለራሳችንና ለምናስተምረው ትምህርት ምንጊዜም ትኩረት መስጠት አለብን። (1 ጢሞ. 4:16) በእርግጥም መዳናችን የተመካው ለአገልግሎታችን ምንጊዜም ቅድሚያ በመስጠታችን ላይ ነው!