አዲስ የሚበረከት ብሮሹር!
1. በኅዳር ወር የምናበረክተው ጽሑፍ ምንድን ነው? የተዘጋጀበት ዓላማስ ምንድን ነው?
1 “ምንጊዜም ነቅታችሁ ጠብቁ!” በተሰኘው የ2009 አውራጃ ስብሰባ ላይ መጽሐፍ ቅዱስ—የያዘው መልእክት ምንድን ነው? የሚል ርዕስ ያለው አዲስ ብሮሹር አግኝተን ነበር። በኅዳር ወር በዓለም ዙሪያ ያሉ ጉባኤዎች ይህንን ብሮሹር ለመጀመሪያ ጊዜ ያበረክታሉ። ይህ ብሮሹር በክልላችን ውስጥ ያሉ ሰዎችን የሚጠቅመው እንዴት ነው? ብዙዎች በተለይ ከክርስትና የተለየ ሃይማኖት ያላቸው ሰዎች ስለ መጽሐፍ ቅዱስ እምብዛም አያውቁም። በመሆኑም ብሮሹሩ ራሱ በገጽ 3 ላይ እንደሚገልጸው የተዘጋጀበት ዓላማ “በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኘውን መልእክት አጠቃላይ ይዘት” ማስተዋወቅ ነው።
2. ብሮሹሩን ለማበርከት ምን ማለት እንችላለን?
2 እንዴት ማበርከት እንችላለን? ብሮሹሩን ለማበርከት እንዲህ ማለት እንችላለን፦ “እዚህ ጥቅስ ላይ ስለሚገኘው ሐሳብ ምን እንደሚሰማዎት ቢነግሩን ደስ ይለናል። [2 ጢሞቴዎስ 3:16ን አንብብ።] ከዚህ በፊት ያነጋገርናቸው ብዙ ሰዎች አሁን ካነበብነው ሐሳብ ጋር ይስማማሉ፤ ሌሎች ደግሞ መጽሐፍ ቅዱስን ጥሩ መጽሐፍ እንደሆነ አድርገው ብቻ ይመለከቱታል። እርስዎስ መጽሐፍ ቅዱስን የሚመለከቱት እንዴት ነው? [ሐሳቡን እንዲገልጽ ዕድል ስጠው።] የምንከተለው ሃይማኖት ምንም ይሁን ምን መጽሐፍ ቅዱስን ለመመርመር የሚያነሳሳ በቂ ምክንያት አለን። [ገጽ 3 ላይ የሚገኘውን የመግቢያ ሐሳብ አንብብ።] የመጽሐፍ ቅዱስን ዋና ዋና ሐሳቦች አጠር ባለና ትኩረት በሚስብ መንገድ የሚያቀርበውን ይህን ብሮሹር ሲያነቡ አንድ አስደናቂ ነገር ያስተውላሉ፤ ይኸውም መጽሐፍ ቅዱስ አንድ አጠቃላይ ጭብጥ ወይም መልእክት እንዳለው ይገነዘባሉ።”
3. በተለይ ከክርስትና የተለየ ሃይማኖት ያላቸው ሰዎች በሚበዙበት አካባቢ የትኛውን መግቢያ መጠቀም እንችላለን?
3 በተለይ ከክርስትና የተለየ ሃይማኖት ያላቸው ሰዎች በሚበዙበት አካባቢ በምንሰብክበት ጊዜም እንዲህ ማለት እንችላለን፦ “በዚህ ቅዱስ መጽሐፍ ላይ ስለሚገኘው ስለዚህ ሐሳብ ምን እንደሚሰማዎት ቢነግሩን ደስ ይለናል። [መዝሙር 37:11ን አንብብ። (ይህ ጥቅስ በዚህ ብሮሹር ክፍል 11 ላይ ተጠቅሷል።)] ይህ ትንቢት ሲፈጸም በምድር ላይ ምን ዓይነት ሁኔታ የሚኖር ይመስልዎታል? [ሐሳቡን እንዲገልጽ ዕድል ስጠው።] የትኛውም ዓይነት ባሕልና እምነት ያላቸው ሰዎች እንዲህ ያለውን ተስፋና ማጽናኛ ከመጽሐፍ ቅዱስ ማግኘት ይችላሉ።” ገጽ 3 ላይ ያለውን የመግቢያ ሐሳብ ካነበብክ በኋላ ብሮሹሩን አበርክት።
4. ብሮሹሩን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ለማስጀመር እንዴት ልንጠቀምበት እንችላለን?
4 የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት አስጀምሩ፦ ተመላልሶ መጠየቅ በምናደርግበት ወቅት የቤቱን ባለቤት ባለፈው ውይይታችን ወቅት ያነሳነውን ጉዳይ ልናስታውሰው እንችላለን፤ ከዚያም በተወያየንበት ክፍል መጨረሻ ላይ ያሉትን ጥያቄዎች በመጠቀም አንድ ወይም ሁለት አንቀጾችን መከለስ እንችላለን። የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት የተባለውን መጽሐፍ ወዲያውኑ ለማስተዋወቅ ከፈለግን ደግሞ የብሮሹሩ መጨረሻ ገጽ ላይ ያለውን ሐሳብ አብረን ካነበብን በኋላ መጽሐፉን ልንሰጠው እንችላለን፤ ከዚያም በመጽሐፉ ውስጥ ከተዘረዘሩት ምዕራፎች ውስጥ በየትኛው ርዕስ ላይ መወያየት እንደሚፈልግ ጠይቀነው በአንድ ወይም በሁለት አንቀጾች ላይ መወያየት እንችላለን። ሁላችንም በኅዳር ወር ይህን ብሮሹር ለማበርከት የተሟላ ተሳትፎ እናድርግ!