ዘሩ እንዲያድግ ውኃ መጠጣት አለበት
1. ለማደግ ውኃ መጠጣት የሚያስፈልገው ምንድን ነው?
1 በአንድ የአትክልት ስፍራ የተተከለ ዘር እንዲያድግ ከተፈለገ ውኃ መጠጣት አለበት። በክልላችን ውስጥ በሚገኙ ሰዎች ልብ ውስጥ የምንተክለውን የእውነት ዘር በተመለከተም ሁኔታው ተመሳሳይ ነው። (1 ቆሮ. 3:6) እነዚህ ምሳሌያዊ ዘሮች ሥር እንዲሰዱ፣ እንዲያድጉና እንዲያፈሩ ከፈለግን ተመላልሶ መጠየቅ ልናደርግላቸውና በአምላክ ቃል ተጠቅመን ውኃ ልናጠጣቸው ይገባል።
2. ለተመላልሶ መጠየቅ መሠረት መጣል የምንችለው እንዴት ነው?
2 ጥያቄ አንሱ፦ መግቢያ ስትዘጋጁ የምታነጋግሩትን ሰው ፍላጎት የሚያነሳሳ በተመላልሶ መጠየቅ ወቅት የምትመልሱለትን ጥያቄ ለምን አታዘጋጁም? ይህን ጥያቄ በውይይታችሁ መጨረሻ ላይ ልታነሱለት ትችላላችሁ፤ ከዚያም በሌላ ጊዜ የምትገናኙበትን ቁርጥ ያለ ቀጠሮ ያዙ። ብዙዎች የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት እንዴት እንደሚመራ ለማሳየት እንዲረዳቸው በማሰብ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ከተባለው መጽሐፍ አንዳንድ ነጥቦች መምረጡን ጠቃሚ ሆኖ አግኝተውታል።
3. አንድን ሰው ለመጀመሪያ ጊዜ ካነጋገርን በኋላ ምን ነገሮችን በማስታወሻችን ላይ መጻፍ እንችላለን?
3 ማስታወሻ ያዙ፦ ሰዎችን ለመጀመሪያ ጊዜ አግኝተን ካነጋገርን በኋላ ወዲያውኑ ማስታወሻ መያዝ ይኖርብናል። በመሆኑም በማስታወሻችሁ ላይ የግለሰቡን ስምና አድራሻ ጻፉ። በተጨማሪም የተወያያችሁበትን ቀንና ሰዓት፣ የተወያያችሁበትን ርዕሰ ጉዳይ፣ የቀጠሮውን ቀንና ሰዓት እንዲሁም ያበረከታችሁለት ጽሑፍ ካለ ያንንም መመዝገባችሁ ጠቃሚ ነው። ግለሰቡ ሃይማኖቱ ምን እንደሆነ ነግሯችኋል? ቤተሰብ አለው? ትኩረቱን ስለሚስቡትና ስለሚያሳስቡት ነገሮች አንስቶላችኋል? እንዲህ ስላሉ ነገሮች ማወቃችሁ ተመላልሶ መጠየቅ ስታደርጉ ምን ዓይነት ርዕሰ ጉዳይ ብታነሱ የተሻለ እንደሚሆን እንድታስቡበት ያስችላችኋል። ከዚህም ባሻገር የቀጠሮውን ቀንና ሰዓት እንዲሁም ያነሳችሁለትን ጥያቄ ጻፉ።
4. ሰዎችን ተከታትለን በመርዳት ረገድ ተስፋ መቁረጥ የማይኖርብን ለምንድን ነው?
4 ተስፋ አትቁረጡ፦ ሰይጣን በሰዎች ልብ ውስጥ ‘የተዘራውን ቃል ለመውሰድ’ ጥረት ማድረጉን አያቆምም። (ማር. 4:14, 15) በመሆኑም ፍላጎት ያሳየን አንድ ሰው ቤቱ ማግኘት አስቸጋሪ ከሆነባችሁ ተስፋ አትቁረጡ። ለግለሰቡ ደብዳቤ መጻፍ አሊያም ማስታወሻ ትታችሁ መሄድ ትችሉ ይሆን? አንዲት አቅኚ እህት ጥናት ያስጀመረቻትን ሴት ቤቷ ማግኘት ስላልቻለች ደብዳቤ ጻፈችላት። ከጊዜ በኋላ እህት ሴትየዋን ቤቷ ስታገኛት፣ ባሳየቻት ልባዊ አሳቢነት በጥልቅ እንደተነካች ለእህት ገለጸችላት። ተመላልሶ መጠየቅ በማድረግ የእውነትን ዘር ውኃ የምናጠጣ ከሆነ ዘሩ ሥር ሲሰድ፣ ሲያድግና “ሠላሳ፣ ስልሳና መቶ እጥፍ [ሲያፈራ]” በማየት ደስታ እናገኛለን።—ማር. 4:20