ክርስቲያናዊ ሕይወት
የይሖዋን የሥነ ምግባር መሥፈርቶች ደግፉ
ይሖዋ አምላክ፣ የሰው ልጆች ሊከተሏቸው የሚገቡ የሥነ ምግባር መሥፈርቶችን አውጥቷል። ለምሳሌ ያህል፣ ጋብቻ በአንድ ወንድና በአንዲት ሴት መካከል የሚፈጸም ዘላቂ ጥምረት እንደሆነ ደንግጓል። (ማቴ 19:4-6, 9) ይሖዋ ማንኛውንም ዓይነት የፆታ ብልግና ያወግዛል። (1ቆሮ 6:9, 10) ሌላው ቀርቶ በአለባበስና በአጋጌጥ ረገድ ሕዝቡ ከሌሎች የተለዩ እንዲሆኑ የሚያደርጓቸውን መሠረታዊ ሥርዓቶች ሰጥቷል።—ዘዳ 22:5፤ 1ጢሞ 2:9, 10
በዛሬው ጊዜ ያሉ በርካታ ሰዎች የይሖዋን መሥፈርቶች አይቀበሉም። (ሮም 1:18-32) በአለባበሳቸውና በአጋጌጣቸው እንዲሁም በምግባራቸው ብዙኃኑን እንደሚከተሉ ያሳያሉ። ብዙዎች ስለሚፈጽሙት መጥፎ ምግባር በኩራት የሚገልጹ ሲሆን ከእነሱ የተለየ የሥነ ምግባር መሥፈርት የሚከተሉ ሰዎችን ይነቅፋሉ።—1ጴጥ 4:3, 4
እኛ ግን የይሖዋ ምሥክሮች እንደመሆናችን መጠን የአምላክን የሥነ ምግባር መሥፈርቶች በድፍረት ልንደግፍ ይገባል። (ሮም 12:9) ይህን የምናደርገው እንዴት ነው? በአምላክ ዘንድ ተቀባይነት ያለው አካሄድ የትኛው እንደሆነ ሌሎችን ቅር በማያሰኝ መንገድ መናገር ይኖርብናል። በተጨማሪም የይሖዋን ላቅ ያሉ መሥፈርቶች በሕይወታችን ውስጥ ተግባራዊ ማድረግ አለብን። ለምሳሌ ያህል፣ ከአለባበሳችንና ከአጋጌጣችን ጋር በተያያዘ ራሳችንን እንደሚከተለው ብለን መጠየቅ እንችላለን፦ ‘በዚህ ረገድ የይሖዋን መሥፈርቶች ነው የምከተለው? ወይስ የዓለምን? ምርጫዬ ምን ያሳያል? አለባበሴ ፈሪሃ አምላክ ያለኝ ክርስቲያን መሆኔን ያሳያል?’ አሊያም ደግሞ የምንመለከተውን የቴሌቪዥን ፕሮግራም ወይም ፊልም በምንመርጥበት ወቅት ራሳችንን እንደሚከተለው ብለን መጠየቅ እንችላለን፦ ‘ይህ ፕሮግራም በይሖዋ ዘንድ ተቀባይነት ይኖረዋል? የማንን የሥነ ምግባር አቋም የሚያንጸባርቅ ነው? የመዝናኛ ምርጫዬ መጥፎ ሥነ ምግባርን እንዳልጸየፍ የሚያደርግ ነው? (መዝ 101:3) ለቤተሰቤ አባላት ወይም ለሌሎች ሰዎች እንቅፋት ይፈጥር ይሆን?’—1ቆሮ 10:31-33
የይሖዋን የሥነ ምግባር መሥፈርቶች መደገፋችን በጣም አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው? ክርስቶስ ኢየሱስ በቅርቡ ብሔራትንና ክፋትን በሙሉ ስለሚያጠፋ ነው። (ሕዝ 9:4-7) ከጥፋቱ የሚተርፉት የአምላክን ፈቃድ የሚያደርጉ ብቻ ናቸው። (1ዮሐ 2:15-17) እንግዲያው መልካም ምግባራችንን የሚመለከቱ ሰዎች አምላክን እንዲያከብሩ የይሖዋን የሥነ ምግባር መሥፈርቶች እንደግፍ።—1ጴጥ 2:11, 12
የአለባበስና የአጋጌጥ ምርጫዬ የማንን የሥነ ምግባር መሥፈርቶች እንደምከተል የሚያሳይ ነው?
የይሖዋ ወዳጅ ሁን—አንድ ወንድና አንዲት ሴት የተባለውን ቪዲዮ ከተመለከታችሁ በኋላ የሚከተሉትን ጥያቄዎች ለመመለስ ሞክሩ፦
የይሖዋን መሥፈርቶች በሕይወታችን ተግባራዊ ማድረግ የጥበብ አካሄድ የሆነው ለምንድን ነው?
ወላጆች የይሖዋን የሥነ ምግባር መሥፈርቶች ለልጆቻቸው ከትንሽነታቸው ጀምሮ ማስተማር ያለባቸው ለምንድን ነው?
ሰዎች ከአምላክ ጥሩነት ጥቅም እንዲያገኙ ልጆችም ሆኑ አዋቂዎች ሊረዷቸው የሚችሉት እንዴት ነው?