ሐሙስ፣ ሐምሌ 17
እውነተኛ ወዳጅ ምንጊዜም አፍቃሪ ነው፤ ደግሞም ለመከራ ቀን የተወለደ ወንድም ነው።—ምሳሌ 17:17
የኢየሱስ እናት ማርያም ጥንካሬ አስፈልጓት ነበር። ማርያም አላገባችም፤ ሆኖም እንደምትፀንስ ተነገራት። የራሷን ልጆች አሳድጋ አታውቅም፤ ሆኖም መሲሑን ማሳደግ ሊኖርባት ነው። ደግሞም ከወንድ ጋር ግንኙነት ሳትፈጽም ስላረገዘች ሁኔታውን ለእጮኛዋ ለዮሴፍ እንዴት ልታብራራለት ትችላለች? (ሉቃስ 1:26-33) ማርያም ጥንካሬ ያገኘችው እንዴት ነው? የሌሎችን እርዳታ ለማግኘት ጥረት አድርጋለች። ለምሳሌ የተሰጣትን ኃላፊነት አስመልክቶ ተጨማሪ መረጃ እንዲሰጣት ገብርኤልን ጠይቃዋለች። (ሉቃስ 1:34) ከዚያ ብዙም ሳይቆይ ደግሞ ዘመዷን ኤልሳቤጥን ለመጠየቅ ረጅም መንገድ ተጉዛ “በተራራማው አገር” ወደምትገኝ አንዲት የይሁዳ ከተማ ሄዳለች። ኤልሳቤጥ ማርያምን አመሰገነቻት፤ እንዲሁም በይሖዋ መንፈስ ተመርታ በማርያም ማኅፀን ውስጥ ያለውን ልጅ በተመለከተ የሚያበረታታ ትንቢት ተናገረች። (ሉቃስ 1:39-45) ማርያም፣ ይሖዋ ‘በክንዱ ታላላቅ ሥራዎች እንዳከናወነ’ ገልጻለች። (ሉቃስ 1:46-51) ይሖዋ በገብርኤልና በኤልሳቤጥ አማካኝነት ማርያምን አጠንክሯታል። w23.10 14-15 አን. 10-12
ዓርብ፣ ሐምሌ 18
ነገሥታት እንዲሁም ለአምላኩና ለአባቱ ካህናት [አደረገን]።—ራእይ 1:6
የተወሰነ ቁጥር ያላቸው የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት በመንፈስ ቅዱስ ተቀብተዋል፤ እነዚህ ሰዎች ከይሖዋ ጋር ልዩ ዝምድና አላቸው። እነዚህ 144,000 ሰዎች በሰማይ ከኢየሱስ ጋር ካህናት ሆነው ያገለግላሉ። (ራእይ 14:1) ቅድስት የተባለው የማደሪያ ድንኳኑ ክፍል ቅቡዓን ክርስቲያኖች ገና ምድር ላይ ሳሉ ያሉበትን ሁኔታ ማለትም በመንፈስ የተወለዱ የአምላክ ልጆች መሆናቸውን ያመለክታል። (ሮም 8:15-17) ቅድስተ ቅዱሳን የተባለው የማደሪያ ድንኳኑ ክፍል ደግሞ ይሖዋ የሚኖርበትን ሰማይን ያመለክታል። ቅድስቱንና ቅድስተ ቅዱሳኑን የሚለየው “መጋረጃ” ኢየሱስ የመንፈሳዊው ቤተ መቅደስ ታላቅ ሊቀ ካህናት ሆኖ ወደ ሰማይ እንዳይገባ ያገደውን ሥጋዊ አካሉን ያመለክታል። ኢየሱስ ሰብዓዊ አካሉን ለሰው ልጆች መሥዋዕት አድርጎ በማቅረብ ሁሉም ቅቡዓን ክርስቲያኖች ሰማያዊ ሕይወት ማግኘት የሚችሉበትን መንገድ ከፍቷል። እነሱም ቢሆኑ ሰማያዊ ሽልማታቸውን ለመቀበል ሥጋዊ አካላቸውን መተው ይጠበቅባቸዋል።—ዕብ. 10:19, 20፤ 1 ቆሮ. 15:50፤ w23.10 28 አን. 13
ቅዳሜ፣ ሐምሌ 19
ስለ ጌድዮን . . . እንዳልተርክ ጊዜ ያጥረኛል።—ዕብ. 11:32
ጌድዮን ኤፍሬማውያን ትችት በሰነዘሩበት ወቅት በገርነት ምላሽ ሰጥቷል። (መሳ. 8:1-3) መልስ የሰጠው በቁጣ አልነበረም። ስሜታቸውን ሲገልጹ በማዳመጥ ትሕትና አሳይቷል፤ እንዲሁም ውጥረት የሰፈነበትን ሁኔታ በዘዴ አርግቧል። ጥበበኛ የሆኑ ሽማግሌዎችም ትችት ሲሰነዘርባቸው በጥሞና በማዳመጥ እንዲሁም በገርነት ምላሽ በመስጠት የጌድዮንን ምሳሌ መከተል ይችላሉ። (ያዕ. 3:13) በዚህ መንገድ ለጉባኤው ሰላም አስተዋጽኦ ያበረክታሉ። ጌድዮን ምድያማውያንን ድል በማድረጉ የተነሳ ክብር ሲሰጠው የሰዎቹ ትኩረት ወደ ይሖዋ እንዲዞር አድርጓል። (መሳ. 8:22, 23) ኃላፊነት ያላቸው ወንድሞች የጌድዮንን ምሳሌ መከተል የሚችሉት እንዴት ነው? ላከናወኑት ሥራ ይሖዋ እንዲመሰገን ማድረግ ይችላሉ። (1 ቆሮ. 4:6, 7) ለምሳሌ አንድ የጉባኤ ሽማግሌ የማስተማር ችሎታውን በተመለከተ ቢመሰገን የሰዎቹን ትኩረት የትምህርቱ ምንጭ ወደሆነው ወደ አምላክ ቃል ወይም ከይሖዋ ድርጅት ወደምናገኘው ሥልጠና ማዞር ይችላል። ሽማግሌዎች ‘ወደ ራሴ አላስፈላጊ ትኩረት እየሳብኩ ነው?’ ብለው አልፎ አልፎ ራሳቸውን መመርመራቸው ጠቃሚ ነው። w23.06 4 አን. 7-8