ሐሙስ፣ ጥቅምት 16
የይሖዋን መንገድ ጥረጉ! በበረሃ ለአምላካችን አውራ ጎዳናውን አቅኑ።—ኢሳ. 40:3
ከባቢሎን ወደ እስራኤል የሚወስደው መንገድ አስቸጋሪ ከመሆኑም ሌላ አራት ወር ገደማ ይወስዳል። ሆኖም ይሖዋ ወደዚያ እንዳይመለሱ ሊያግዳቸው የሚችለውን ማንኛውንም እንቅፋት እንደሚያስወግድላቸው ቃል ገብቶላቸዋል። በታማኞቹ አይሁዳውያን ዓይን ወደ እስራኤል መመለስ የሚያስገኘው ጥቅም ከሚከፍሉት ከማንኛውም መሥዋዕት እጅግ የላቀ ነው። የሚያገኙት ትልቁ በረከት ከአምልኳቸው ጋር የተያያዘ ነው። በባቢሎን የይሖዋ መቅደስ አልነበረም። እስራኤላውያን በሙሴ ሕግ መሠረት የሚጠበቅባቸውን መሥዋዕት ማቅረብ የሚችሉበት መሠዊያ አልነበረም፤ እንዲሁም እነዚህን መሥዋዕቶች የሚያቀርብ የተደራጀ የክህነት ሥርዓት አልነበረም። በተጨማሪም በዚያ የነበሩት ጣዖት አምላኪዎች ቁጥር ከይሖዋ ሕዝቦች ቁጥር በእጅጉ ይበልጣል፤ እነዚህ ሰዎች ደግሞ ለይሖዋም ሆነ ለመሥፈርቶቹ አክብሮት አልነበራቸውም። በመሆኑም ፈሪሃ አምላክ የነበራቸው በሺዎች የሚቆጠሩ አይሁዳውያን ወደ አገራቸው ተመልሰው ንጹሕ አምልኮን መልሰው ለማቋቋም ጓጉተው ነበር። w23.05 14-15 አን. 3-4
ዓርብ፣ ጥቅምት 17
የብርሃን ልጆች ሆናችሁ መመላለሳችሁን ቀጥሉ።—ኤፌ. 5:8
‘ከብርሃን ልጆች’ የሚጠበቀውን ምግባር እያሳየን ለመኖር የአምላክ ቅዱስ መንፈስ እርዳታ ያስፈልገናል። ለምን? ምክንያቱም ሥነ ምግባር በጎደለው በዚህ ዓለም ውስጥ ንጹሕ ሆኖ መኖር በጣም ከባድ ነው። (1 ተሰ. 4:3-5, 7, 8) መንፈስ ቅዱስ ከአምላክ አስተሳሰብ ጋር የሚጋጩ ፍልስፍናዎችንና አመለካከቶችን ጨምሮ የዓለም አስተሳሰብ እንዳይጋባብን በምናደርገው ትግል ያግዘናል። “ሁሉንም ዓይነት ጥሩነት [እና] ጽድቅ” እንድናፈራም ይረዳናል። (ኤፌ. 5:9) መንፈስ ቅዱስን ማግኘት የምንችልበት አንዱ መንገድ ይሖዋ መንፈሱን እንዲሰጠን መጸለይ ነው። ይሖዋ “ለሚለምኑት መንፈስ ቅዱስን [እንደሚሰጣቸው]” ኢየሱስ ተናግሯል። (ሉቃስ 11:13) ክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ላይ ከወንድሞቻችን ጋር ሆነን ይሖዋን ስናወድስም መንፈስ ቅዱስን እናገኛለን። (ኤፌ. 5:19, 20) የአምላክ ቅዱስ መንፈስ የሚያሳድረው በጎ ተጽዕኖ አምላክን በሚያስደስት መንገድ ለመኖር ይረዳናል። w24.03 23-24 አን. 13-15
ቅዳሜ፣ ጥቅምት 18
ደጋግማችሁ ለምኑ፣ ይሰጣችኋል፤ ሳታሰልሱ ፈልጉ፣ ታገኛላችሁ፤ ደጋግማችሁ አንኳኩ፣ ይከፈትላችኋል።—ሉቃስ 11:9
ይበልጥ ትዕግሥተኛ መሆን ትፈልጋለህ? ከሆነ ጸልይ። ትዕግሥት ከመንፈስ ፍሬ ገጽታዎች አንዱ ነው። (ገላ. 5:22, 23) በመሆኑም ይሖዋ መንፈስ ቅዱስን እንዲሰጠን እንዲሁም የመንፈስ ፍሬ ለማፍራት እንዲረዳን መጸለይ እንችላለን። ትዕግሥታችንን የሚፈትን ሁኔታ ሲያጋጥመን ትዕግሥተኛ ለመሆን የሚረዳንን ቅዱስ መንፈሱን እንዲሰጠን ይሖዋን ‘ደጋግመን እንለምነዋለን።’ (ሉቃስ 11:13) በተጨማሪም ይሖዋ ሁኔታውን ከእሱ አመለካከት አንጻር ለማየት እንዲረዳን ልንጠይቀው እንችላለን። ከጸለይን በኋላ ደግሞ በየዕለቱ ትዕግሥተኛ ለመሆን አቅማችን የፈቀደውን ሁሉ እናደርጋለን። ትዕግሥት ለማዳበር በጸለይን እንዲሁም ትዕግሥተኛ ለመሆን ጥረት ባደረግን መጠን ይህ ባሕርይ በልባችን ውስጥ ይበልጥ ሥር በመስደድ የማንነታችን ክፍል እየሆነ ይሄዳል። በመጽሐፍ ቅዱስ ምሳሌዎች ላይ ማሰላሰላችንም ይጠቅመናል። መጽሐፍ ቅዱስ ትዕግሥት ያሳዩ በርካታ ሰዎችን ምሳሌ ይዟል። በእነዚህ ዘገባዎች ላይ ማሰላሰላችን ትዕግሥት ማሳየት የምንችልባቸውን መንገዶች ለማወቅ ይረዳናል። w23.08 22-23 አን. 10-11