ሕይወትህን የሚቆጣጠረው ዕድል ነውን?
“አላ ኖ ዶ።” ይህ አባባል በምዕራብ አፍሪካዊቷ አገር በማሊ በሚነገረው የባምብራ ቋንቋ ውስጥ የሚገኝ ሲሆን “የአምላክ ሥራ ነው” የሚል ትርጉም አለው። እንደነዚህ የመሳሰሉ አነጋገሮች በዚያ አካባቢ በሰፊው የተለመዱ ናቸው። በዎሎፍ ቋንቋ “ያላ ሞ ኮ ዴፍ” (የእግዚአብሔር ፍርጃ ነው) ይባላል። በዶጎን የጎሣ ቋንቋም “አማ ቢሬ” (አምላክ ያመጣው ነው) የሚል አባባል አለ።
በሌሎች አገሮችም ተመሳሳይ አባባሎች አሉ። ብዙ ጊዜ ሞት ወይም አንድ አሳዛኝ ሁኔታ ሲደርስ “ቀኑ ደርሶ ነው” እና “አምላክ አዝዞበት ነው” የሚሉት አነጋገሮች ይሰማሉ። በምዕራብ አፍሪካ ውስጥ “ሰው ያስባል፣ አምላክ ይፈጽማል” እንደሚለው የመሳሰሉ አባባሎች በሕዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎችና በሱቆች ላይ እንደምልክት ተለጥፈው መታየታቸው የተለመደ ነገር ነው። ብዙ ሰዎች እንዲሁ የተለመዱ አነጋገሮች ብቻ አድርገው ያዩአቸዋል። ይሁን እንጂ ብዙውን ጊዜ በዕድል ላይ የተመሠረተን ጠንካራ እምነት የሚያንጸባርቁ ናቸው።
የዕድል እምነት ምንድን ነው? ዘ ወርልድ ቡክ ኢንሳይክሎፔድያ “ማንኛውም ነገር ከሰው በላይ በሆኑ ኃይሎች ተወስኗል የሚል እምነት” ሲል ፍቺ ሰጥቶታል። እነዚህ “ኃይሎች” ምንድን ናቸው? ከብዙ ሺህ ዓመታት በፊት ባቢሎናውያን አንድ ሰው በሚወለድበት ጊዜ ከዋክብት የሚኖራቸው አቀማመጥ በግለሰቡ የወደፊት ዕጣ ፋንታ ላይ ትልቅ ተጽእኖ ይኖረዋል ብለው ያምኑ ነበር። (ከኢሳይያስ 47:13 ጋር አወዳድር።) ግሪካውያን የሰው ዕድል ያለው የሕይወትን ክር የመፍተል፣ የመለካትና የመቁረጥ ሥራ ባላቸው ሦስት ኃያላን ሴት አማልክት እጅ እንደሆነ ያምኑ ነበር። ይሁን እንጂ የሰዎችን ዕድል የሚወስነው አምላክ ራሱ ነው የሚለውን ሐሳብ ያመነጩት የሕዝበ ክርስትና የሃይማኖት ምሁራን ናቸው!
ለምሳሌ ያህል “ቅዱስ” አውጉስቲን የኮከብ ቆጣሪዎችን “ውሸትና መርዘኛ ሐሳብ” አልተቀበላቸውም። በሌላ በኩል ደግሞ “አምላክ መኖሩን እያመኑ ወደፊት የሚሆኑትን ነገሮች በቅድሚያ አያውቅም ብሎ መካድ ከሁሉ የከፋ ሞኝነት ነው” ሲል ተከራክሯል። አምላክ በእርግጥ ሁሉን ቻይ ከሆነ “ነገሮች ከመፈጸማቸው በፊት” ማወቅ ይኖርበታል፤ “አስቀድሞ ሳያውቀው የሚያልፍ ነገር ሊኖር አይገባም” የሚል እምነት ነበረው። ይሁንና አውጉስቲን አምላክ ወደፊት የሚሆኑትን ነገሮች ሁሉ አስቀድሞ የሚያውቅ ቢሆንም የሰዎችን ነጻ ምርጫ አልነፈጋቸውም ሲል ሽንጡን ገትሮ ተከራክሯል።—ዘ ሲቲ ኦቭ ጎድ፣ መጽሐፍ 5 ምዕራፍ 7-9
ብዙ መቶ ዘመናት ካለፉ በኋላ የፕሮቴስታንቱ ሃይማኖታዊ ምሁር ጆን ካልቪን አንዳንዶች “የአምላክ ልጆችና የሰማያዊው መንግሥት ወራሾች እንዲሆኑ” የቀሩት ደግሞ “ቁጣው እንዲወርድባቸው [በአምላክ] ተወስነዋል” የሚል ክርክር በማንሳት ይህን ሐሳብ ይበልጥ አጠናክሮታል።
በዛሬው ጊዜ በዕድል ማመን በብዙ አገሮች ሰፊ ተቀባይነት እያገኘ መጥቷል። በምዕራብ አፍሪካ የሚገኝ ዑስማን የተባለ ወጣት የገጠመውን ተሞክሮ ተመልከት። በትምህርት ቤቱ ውስጥ ካሉት በጣም ጎበዝ ተማሪዎች መካከል አንዱ ነበር፤ ይሁን እንጂ የትምህርት ቤት መልቀቂያ ፈተና ሲወስድ ወደቀ! በፈተናው መውደቁ ክፍል የመድገም ጉዳይ ብቻ ሳይሆን በቤተሰቡና በወዳጆቹ ፊት ታላቅ ኀፍረት ሆኖበት ነበር። አንድ ጓደኛው አምላክ አዞብህ ነው በማለት ሊያጽናናው ሞክሯል። የዑስማን እናትም በተመሳሳይ የልጅዋን ዕድል አማራለች።
መጀመሪያ አካባቢ በአዘኔታ እርሱን ለማጽናናት ያደረጉትን ሙከራ ዑስማን በደስታ ተቀብሎት ነበር። ደግሞስ የእርሱ መውደቅ የአምላክ ትእዛዝ ከሆነ እርሱ ምን ሊያደርግ ይችላል? ይሁን እንጂ አባቱ የነበረው ሐሳብ ከዚህ የተለየ ነበር። ዑስማን በፈተና የወደቀው በራሱ ጥፋት እንጂ አምላክ ስላዘዘበት እንዳልሆነ ነገረው። በቀላል አነጋገር ዑስማን የወደቀው ጥናቱን ቸል በማለቱ ነበር።
ስለ ዕድል የነበረው እምነት የተናጋበት ዑስማን ጉዳዩን ራሱ ለመመርመር ወሰነ። አንተም የሚቀጥለውን ርዕስ በማንበብ ስለ ጉዳዩ እንድትመረምር እናበረታታሃለን።