አዲስ የልዩ ስብሰባ ቀን ፕሮግራም
1 ምሥራቹን ያለመታከት ማወጅ ያለብን ለምንድን ነው? የምሥራቹ ሰባኪ ለመሆን የሚያስፈልጉ ብቃቶች የትኞቹ ናቸው? ዓይነ አፋሮች እንኳ ሳይቀሩ ምሥራቹን ለሌሎች መስበክ የሚችሉት እንዴት ነው? እነዚህና ሌሎች ስሜት ቀስቃሽ ጥያቄዎች ከመስከረም ጀምሮ እየተደረገ ባለው “ብቁ የምሥራቹ አገልጋዮች መሆን” የሚል ጭብጥ ባለው የልዩ ስብሰባ ቀን መልስ ይሰጥባቸዋል።— ከ2 ቆሮንቶስ 3:5 ጋር አወዳድር።
2 የይሖዋ ሕዝቦች እንደመሆናችን መጠን ጠባያችንን በተመለከተ ጠንቃቆች መሆን አለብን። የእኩዮቻቸውን ተጽዕኖ እንዴት እንደተቋቋሙ የሚናገሩት ወጣቶች የሚያበረታታ ተሞክሮ ያካፍሉናል። ወላጆች ልጆቻቸውን የአምላክ አገልጋዮች አድርገው የማሠልጠንን አስፈላጊነት በተመለከተ ፍቅር የተሞላበት ማበረታቻ ያገኛሉ። ሁላችንም የመስበኩን አስፈላጊነትና እኛም ሆንን የሚሰሙን ሰዎች በምላሹ የምናገኘውን በረከቶች እንድንገነዘብ የሚያስችሉን ጠቃሚ ትምህርቶች እናገኛለን።— 1 ጢሞ. 4:16
3 ጥምቀት በቀኑ ፕሮግራም ውስጥ ጎላ ያለ ቦታ ይይዛል። ጥምቀቱ ከመከናወኑ በፊት በተለይ ራሳቸውን ለወሰኑ አዳዲስ ሰዎች በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረተ ንግግር ይቀርባል። እርግጥ ነው በስብሰባው ላይ የተገኙት ሁሉ ጥምቀትን በተመለከተ ትምህርት ሲሰጥና የጥምቀት ትርጉም ሲብራራ ሐሳባቸውን ሰብሰብ አድርገው በትኩረት መከታተል ይኖርባቸዋል። በልዩ ስብሰባው ቀን ለመጠመቅ የሚፈልጉ ቀደም ብለው ለሰብሳቢ የበላይ ተመልካቹ ማስታወቅ አለባቸው። እንዲህ ከሆነ ሰብሳቢ የበላይ ተመልካቹ ለመጠመቅ ለሚፈልጉ ሰዎች የተዘጋጁትን ጥያቄዎች ሽማግሌዎች ከጥምቀት እጩዎች ጋር የሚከልሱበትን ጊዜ ለማመቻቸት በቂ ጊዜ ይኖረዋል።
4 ሌላው በስብሰባው ላይ ጉልህ ሥፍራ የሚይዘው በእንግዳ ተናጋሪ የሚቀርበው ዋናው ንግግር ነው። “ብቁና የታጠቁ የአምላክ አገልጋዮች መሆን” የሚል ርዕስ አለው። ንግግሩ ብቁ የአምላክ አገልጋዮች ለመሆን የሚያስችሉንን አራት መሠረታዊ ዝግጅቶች የሚያብራራ ሲሆን እምነት የሚገነቡ ተሞክሮዎችንም ይዟል።
5 ተጀምሮ እስኪያልቅ ድረስ በፕሮግራሙ ላይ ለመገኘት አሁኑኑ ዕቅድ አውጣ። በዚህ ዕለት ከሚሰጠው ቲኦክራሲያዊ ትምህርት ተጠቃሚዎች መሆን እንዲችሉ ፍላጎት ያሳዩ ሰዎችንና የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎችን ወደ ስብሰባው መጋበዝህን አትርሳ። በዚህ መንገድ “ብቁ” የምሥራቹ አገልጋይ መሆን እንችላለን።