ሌሎች ማጽናኛ እንዲያገኙ እርዷቸው
1 ብዙ ሰዎች ስለ ተፈጥሮ አደጋዎች፣ ጦርነቶች፣ ወንጀልና ሥቃይ መስማት ሰልችቷቸዋል። ማጽናኛ የሰው ልጆች በጣም የሚያስፈልጋቸው ነገር ቢሆንም በዛሬው ጊዜ ካሉት የዜና ዘገባዎች ውስጥ ፈጽሞ ጠፍቷል። ማጽናናት “ብርታትንና ተስፋን መስጠት” በተጨማሪም የሌላውን “ሐዘንና ችግር ማቃለል” ማለት ነው። የይሖዋ ምሥክሮች እንደመሆናችን መጠን ሰዎችን በዚህ መንገድ ለመርዳት ታጥቀናል። (2 ቆሮ. 1:3, 4) ለሰዎች የምናበረክታቸው በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሰረቱት ብሮሹሮቻችን የእውነትን አጽናኝ መልእክት ይዘዋል። (ሮሜ 15:4) እነዚህን ብሮሹሮች በተለያዩ ሁኔታዎች ሥር ለማበርከት የምንችልባቸው ሐሳቦች ቀጥሎ ቀርበዋል:-
2 አንድ አሳዛኝ የዜና ዘገባ ለሌሎች ለመመስከርና ማጽናኛ ለመስጠት አጋጣሚ ሊከፍትልን ይችላል። ምናልባትም ቀጥሎ ካለው አቀራረብ ጋር ተመሳሳይ የሆነ ነገር በመናገር ይህን ማከ ናወን ትችል ይሆናል:-
◼ “እነዚህን የመሳሰሉ ነገሮች ሲከሰቱ አንዳንዶች አምላክ በእርግጥ ስለመኖሩና ካለ ደግሞ ለኛ ያስብ እንደሆነና እንዳልሆነ ራሳቸውን ይጠይቃሉ። እርስዎስ ምን ይሰማዎታል? [መልስ እንዲሰጥ ፍቀድለት] አምላክ መኖሩን የምናረጋግጥበት አንዱ መንገድ አንድ በጣም ግልጽ የሆነ መሠረታዊ ሥርዓት በመጠቀም ነው።” ዕብራውያን 3:4ን አንብብ። በአካባቢያችን ያሉ ሠሪ እንዳላቸው ምንም የማያጠራጥሩ ሌሎች ነገሮችንም ጥቀስ። በመቀጠልም “ሊያጽናናዎት የሚችል አንድ ብሮሹር አለኝ። ርዕሱ የአምላክ መንግሥት ገነትን ታመጣለች ይላል። አምላክ መኖሩን ብቻ ሳይሆን የሚያጋጥሙንን ፍትህ የጎደላቸው ሁኔታዎች በሙሉ በቅርቡ እንደሚያስወግዳቸው የሚያሳይ አሳማኝ ማስረጃ ይዟል። ብሮሹሩን ለማንበብ ይፈልጋሉ?” ተመልሰህ ለመሄድ ቀጠሮ ያዝ።
3 በተመላልሶ መጠየቅ ጊዜ፣ ቀጥሎ የቀረበውን በመናገር የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት የማስጀመር ግብህን ለመከታተል ትችላለህ:-
◼ “ባለፈው ጊዜ አምላክ ለእኛ ያለውን አሳቢነት አስመልክቶ የተወያየንበትን ርዕስ አስቤበታለሁ፤ ያስደስትዎታል ብዬ ያሰብኩትን አንድ ጽሑፍም ይዤልዎት መጥቻለሁ። [አምላክ ከእኛ የሚፈልገው የተባለውን ብሮሹር አሳየውና ገጽ 3ን ገልጠህ ከላይ ያሉትን 3 ጥያቄዎች አንብብ] ጥቂት ደቂቃዎች ካልዎት ከዚህ ማብራሪያ እንዴት ጥሩ ጥቅም ሊያገኙ እንደሚችሉ አሳይዎታለሁ።” ከዚህ በኋላ ትምህርት 1ን ማጥናት ጀምሩ።
4 ውይይት ለመጀመር ሌላው መንገድ አንድን ችግር በማንሣት ነው። እንደዚህ ለማለት ትችላለህ:-
◼ “ምንም እንኳን እያንዳንዱ ሰው የደስታና የእርካታ ስሜት ለማግኘት የሚፈልግ ቢሆንም፣ ብዙ ቤተሰቦች በዚህ ረገድ የተሳካላቸው አይመስልም። እውነተኛ ደስታ እንዲያገኙ ምን ሊረዳቸው ይችላል ብለው ያስባሉ? [መልስ እንዲሰጥ ፍቀድለት] መጽሐፍ ቅዱስ ከረዥም ጊዜ በፊት፣ በጊዜያችን በቤተሰቦች ላይ ምን ዓይነት ችግሮች እንደሚከሰቱ ገልጿል። [2 ጢሞቴዎስ 3:1-3ን አንብብ] ነገር ግን መጽሐፍ ቅዱስ እነዚህን ችግሮች ለማስወገድና ዘላቂ ደስታ ለማግኘት ቤተሰቦች ምን ማድረግ እንደሚችሉም ጭምር ይናገራል። መሠረታዊ ሥርዓቶቹ የቤተሰብ ደስታ የሚገኝበት ምሥጢር በተባለው በዚህ መጽሐፍ ላይ ቀርበዋል (ወይም በምድር ላይ በደስታ ለዘላለም ኑር! ከተባለው የአማርኛ ብሮሹር ሥዕል 68ና 69)።” ከዚያ በኋላ ተስማሚ ሆኖ ባገኘኸው ምዕራፍ መጨረሻ ላይ ያለውን የክለሳ ጥያቄ ሣጥን አሳይ፣ ጥያቄዎቹን አንብብና መጽሐፉን አበርክት።
5 ተመልሰህ በምትሄድበት ጊዜ፣ ጥናት ለማስጀመር “አምላክ ከእኛ የሚፈልገው” የተባለውን ብሮሹር ተጠቀም። እንዲህ ማለት ትችላለህ:-
◼ “የቤተሰብ ኑሮን አስመልክቶ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙትን መሠረታዊ ሥርዓቶች ለመመርመር ፈቃደኛ በመሆንዎ ተደስቻለሁ። ከሁሉ የተሻለ ውጤት ማግኘት የሚቻለው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙትን ተግባራዊ ምክሮች በመከተል እንደሆነ ከተሞክሮ ማየት ተችሏል። ይህ ሊሆን የቻለበት ምክንያት እዚህ ላይ በአጭሩ ተብራርቷል።” አምላክ ከእኛ የሚፈልገው ከተባለው ብሮሹር የትምህርት አንድን የመጀመሪያ አንቀጽና መዝሙር 1:1-3ን ወይም ኢሳይያስ 48:17, 18ን ጨምረህ አንብብ። ሁኔታው የሚፈቅድልህ ከሆነ የቀረውንም የትምህርቱን ክፍል ሸፍኑ። በሌላ ጊዜ ተመልሰህ የሚቀጥለውን ትምህርት አብራችሁ እንድታጠኑ ሐሳብ አቅርብለት።
6 ቀጥሎ ያለው ጥሩ አቀራረብ የሚያፈቅሩትን ሰው በሞት ያጡ ሰዎችን ሊያጽናናቸው ይችል ይሆናል:-
◼ “የሚያፈቅሩትን ሰው በሞት ያጡ ሰዎችን ሁሉ የሚጠቅም ሕዝባዊ አገልግሎት እየሰጠሁ ነው። ይህ በሁላችንም ላይ ከሚደርሱትና ልንቋቋማቸው ከሚገቡ ከባድ ነገሮች አንዱ እንደመሆኑ መጠን በምድር ላይ በደስታ ለዘላለም ኑር! የተባለው ይህ ብሮሹር ትንሣኤ መቼና እንዴት እንደሚከናወን የሚገልጸውን የመጽሐፍ ቅዱስ ሐሳብ ይዟል። በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን ጠቅሟል። ኢየሱስ ክርስቶስ የሰጠውን አስደሳች ተስፋ አስመልክቶ ብሮሹሩ ምን እንደሚል ላሳይዎት እወዳለሁ። [ሥዕል 48ን አሳየውና የሚቻል ከሆነ ዮሐንስ 5:21, 28ንና 29ን አንብብ። በኋላም ብሮሹሩን አበርክት]”
7 ተመልሰህ በምትሄድበት ጊዜ፣ “የምትወዱት ሰው ሲሞት” ከተባለው ብሮሹር በገጽ 29 ላይ ያለውን ሥዕል ካሳየኸው በኋላ እንዲህ ማለት ትችላለህ:-
◼ “ክርስቶስ አልዓዛርን ከሞት ስለማስነሳቱ ተወያይተን እንደነበረ ያስታውሱ ይሆናል። [በገጽ 28 ላይ ያለውን የሥዕሉን ማብራሪያ አንብብና “ይህ ተአምር እውነት ተፈጽሞ ነበርን?” በሚለው ንዑስ ርዕስ ሥር ባለው ሐሳብ አወያየው] በሞት የተለየዎትን የሚወዱትን ሰው እንደገና ለማየት ልብዎ የሚጓጓ ከሆነ በትንሣኤ ተስፋ ላይ ሙሉ እምነት እንዲኖርዎ ለማስቻል ብረዳዎ ደስ ይለኛል።” የቤት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት እንዲጀምር ሐሳብ አቅርብ።
8 ደስታ የሚያስገኘው ምሥጢር በአምላክ ቃል ውስጥ ያሉትን መመሪያዎች መከተል እንደሆነ ሌሎችም እንዲገነዘቡ ለመርዳት የተቻለንን ሁሉ ጥረት እናድርግ።—መዝ. 19:7-10