1 ይሖዋ ለሰዎች ያስባል። የእርሱን ፈቃድ የሚያደርገውን ማንኛውንም ሰው ያለ አድልዎ ይቀበላል። (ሥራ 10:34, 35) በተመሳሳይም ኢየሱስ ለሰዎች በሚሰብክበት ጊዜ አድልዎ አላሳየም። (ሉቃስ 20:21) ጳውሎስ እንዳደረገው ሁሉ እኛም የእነርሱን ምሳሌ መከተል አለብን። እርሱ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “አንዱ ጌታ የሁሉ ጌታ ነውና፣ ለሚጠሩትም ሁሉ ባለ ጠጋ ነው።”—ሮሜ 10:12
2 ለምናገኛቸው ሰዎች ሁሉ የአምላክን መንግሥት ምሥራች ማወጃችን ‘አምላክን ያስከብረዋል።’ ሰዎች ዘራቸው፣ በኅብረተሰቡ ውስጥ ያላቸው ቦታ፣ የትምህርት ደረጃቸው ወይም ያላቸው ሃብት ምንም ይሁን ምን ይህን አስደናቂ መልእክት ማካፈላችንን መቀጠል አለብን። (ሮሜ 10:11-13) ይህም ለሚያዳምጡን ሁሉ ወንድ፣ ሴት፣ ወጣት፣ አረጋዊ ሳንል እንሰብካለን ማለት ነው። የምናገኘው እያንዳንዱ ሰው እውነትን የመስማት አጋጣሚ እንዲያገኝ ሁሉንም በር ማንኳኳት አለብን።
3 ለሁሉም ሰው ትኩረት ስጡ፦ ግባችን አቅማችን የፈቀደውን ያህል ብዙ ሰዎች ማነጋገር ነው። አንዳንድ አስፋፊዎች ይህን በአእምሯቸው በመያዝ በክሊኒኮች፣ በሆስፒታሎች፣ በአረጋውያንና በአካል ጉዳተኞች መንከባከቢያ ጣቢያዎች፣ በለቅሶ ቤቶች፣ በመልሶ ማቋቋሚያ ጣቢያዎችና በሌሎች ተቋማት ውስጥና በዚያ አካባቢ ለሚገኙ ሰዎች በመመሥከር ረገድ ስኬታማ ሆነዋል። በተጨማሪም አንዳንድ አስፋፊዎች ለትምህርት ቤት ርዕሰ መምህራንና አማካሪዎች እንዲሁም ለዳኞች መመሥከር ችለዋል። ባለሥልጣኖችን ቀርበን ስናነጋግር ለኅብረተሰቡ ለሚሰጡት ጠቃሚ ግልጋሎት ያለንን አድናቆት መግለጻችን ተገቢ ይሆናል። አክብሮት አሳዩዋቸው፤ እንዲሁም ከሥራቸው ባሕርይ እና ከሥራቸው ጋር ግንኙነት ስላላቸው ችግሮች የሚናገሩ ወቅታዊ ጽሑፎችን መርጣችሁ ስጧቸው።
4 በአንድ አጋጣሚ አንዲት እህት ወደ አንድ ዳኛ ቢሮ ሄዳ ዳኛውን ማነጋገር ችላ ነበር። ጥሩ ውይይት ካደረጉ በኋላ እንዲህ ሲሉ ሐሳብ ሰጡ:- “ስለ ይሖዋ ምሥክሮች ደስ የሚለኝ ነገር ምን እንደሆነ ታውቂያለሽ? ጥብቅ መሠረት ያለው መሠረታዊ ሥርዓት አላቸው፤ ከዚያ ፍንክች አይሉም።” ለእኚህ ከፍተኛ ባለሥልጣን ጥሩ ምሥክርነት ተሰጥቷል።
5 እኛ የሰዎችን ልብ የማንበብ ችሎታ የለንም። ይሁን እንጂ ለምናገኛቸው ሰዎች ሁሉ በመመሥከር አምላክ ለሥራችን አመራር ለመስጠት ባለው ችሎታ ላይ እምነት እንዳለን እናሳያለን። በተጨማሪም እንዲህ ማድረጋችን ሰዎች ተስፋ ያዘለውን መልእክት የመስማትና ምላሽ የመስጠት አጋጣሚ ይሰጣቸዋል። (1 ጢሞ. 2:3, 4) ጊዜያችንን በጥበብ ተጠቅመን ለምናገኛቸው ሰዎች ሁሉ ምሥራቹን በማዳረስ የማያዳላውን አምላክ ይሖዋን ለመምሰል ጥረት እናድርግ።—ሮሜ 2:11፤ ኤፌ. 5:1, 2