ፍላጎት ላሳዩ ሰዎች ክትትል ማድረግ
1 ከቤት ወደ ቤት ስንሠራ ፍላጎት ካሳዩ ሰዎች ጋር ለመወያየት ያለን ጊዜ አጭር ነው። ብዙውን ጊዜ የማስተማሩ ሥራ በይበልጥ የሚከናወነው ተመላልሶ መጠየቆችን ስናደርግና የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶችን ስንመራ ነው። (ማቴ. 28:19, 20) በተመላልሶ መጠየቆች ወቅት ውጤታማ በሆነ መንገድ ለማስተማር መጀመሪያ የተነጋገርንበትን ሐሳብ መከለስና ከዚያ በኋላ ለተጨማሪ ውይይት መዘጋጀት ያስፈልገናል።
2 ስለ ቤተሰብ ተቋም መፈራረስ ተነጋግራችሁ ከነበረ “ለዘላለም መኖር” መጽሐፍ ምዕራፍ 29 ላይ የሚገኘውን ሐሳብ ልትጠቀም ትችላለህ። እንዲህ ልትል ትችላለህ:-
◼ “እንደገና ስላገኘንዎት ተደስተናል። ከዚህ በፊት ደስተኛ ቤተሰብ ለመገንባት የመጽሐፍ ቅዱስን ምክር መከተል ጥበብ እንደሆነ ተወያይተን ነበር። በአሁኑ ጊዜ አንድነት ያላቸው ቤተሰቦች ለመመሥረት ቁልፉ ምንድን ነው ይላሉ?” [መልስ እንዲሰጥ ፍቀድለት።] ገጽ 247 አንቀጽ 27ን ጥቀስና ቆላስይስ 3:12–14ን አንብብ። እውነተኛ ፍቅር ቤተሰቦችን እንዴት ሊያስተሳስራቸው እንደሚችል የሚያሳዩ ተጨማሪ ሐሳቦችን ጥቀስ። ለዘላለም መኖር የተባለውን መጽሐፍ በቅደም ተከተሉ መሠረት ማጥናት ችግሮችን ለማቃለል እንዴት ሊረዳ እንደሚችል ግለጽ።
3 በመጀመሪያ ውይይታችሁ ወቅት እየተበላሹ ስለሚሄዱ የዓለም ሁኔታዎች ተወያይታችሁ ከነበረ እንዲህ በማለት ሰዎች ያሳዩትን ፍላጎት ልትከታተል ትችላለህ:-
◼ “በሰላም ለመኖር እንድንችል ከፍተኛ ለውጦች መደረግ አለባቸው ቢባል እንደሚስማሙ እርግጠኛ ነኝ። መጽሐፍ ቅዱስ የችግሮቻችን ዋና መንስኤ ሰይጣን እንደሆነ ያሳያል። ብዙዎች አምላክ እስካሁን እንዲኖር ለምን እንደፈቀደለት ይጠይቃሉ። እርስዎስ ምን ይላሉ?” [መልስ እንዲሰጥ ፍቀድለት።] ለዘላለም መኖር የተባለውን መጽሐፍ ገጽ 20 አውጣና አንቀጽ 14, 15ን አንብብ፤ ሰይጣን እስካሁን ለምን እንዳልጠፋ አብራራ። ከዚያም በቅርቡ ምን መጠበቅ እንደምንችል የሚያሳየውን ሮሜ 16:20ን አንብብ።
4 የአምላክ መንግሥት ስለምታመጣቸው በረከቶች ተነጋግራችሁ ከነበረ ተመላልሶ መጠየቅ ስታደርግ እንዲህ ልትል ትችላለህ:-
◼ “የአምላክ መንግሥት ስለምታመጣቸው በረከቶች ያደረግነውን ውይይት እንደሚያስታውሱ ተስፋ እናደርጋለን። እነዚህ በረከቶች እዚህ ገጽ 12 እና 13 ላይ ባሉት ሥዕሎች በደንብ ተገልጸዋል። እርስዎን ይበልጥ የሚያስደስትዎት የቱ ነው? [መልስ እንዲሰጥ ፍቀድለት።] እንዲህ በመሰለው ዓለም ውስጥ መኖር ምን እንደሚመስል ያስቡ።” አንቀጽ 12ን አንብብ። ሰውዬው ፍላጎት ካሳየ በገጽ 13 ላይ ያለውን ጥያቄ ጠይቅና መልሱን ተወያዩ። ይህ ምዕራፍ ስለ አምላክ መንግሥት የሚነሡ ብዙ ጥያቄዎችን እንደሚመልስና በሚቀጥለው ጊዜ መጥተህ እነዚህን ጥያቄዎች ብታወያየው ደስ እንደሚልህ ጥቀስ።
5 እንዲህ በማለት ጥናት ማስጀመር ትችል ይሆናል:-
◼ “ባለፈው ጊዜ ካደረግነው ውይይት በኋላ ብዙ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጥያቄዎቻቸው እንዲመለስላቸው የረዳቸውን የዚህን መጽሐፍ ጠቀሜታ ላሳይዎት ፈለግሁ።” የመጽሐፉን አርዕስት ማውጫ አውጣና “ከዚህ ውስጥ ይበልጥ ለማወቅ የሚፈልጉት ስለ የትኛው ርዕስ ነው?” ብለህ ጠይቀው። መልስ እንዲሰጥ ፍቀድለት፤ ፍላጎቱን የቀሰቀሰውን ምዕራፍ አውጣና የመጀመሪያውን አንቀጽ አንብብ። በመጽሐፉ ግርጌ ላይ ያሉ ጥያቄዎች በየአንቀጹ ውስጥ ያሉትን ዋና ዋና ነጥቦች እንዴት እንደሚያጎሉ ግለጽ። አንድ ወይም ሁለት አንቀጾችን በማወያየት ሐሳቡን አብራራ፤ ከዚያም እንደገና ተመልሰህ ለመሄድ ዝግጅት አድርግ።
6 ለዘላለም መኖር በተባለው መጽሐፍ በመጠቀም ፍላጎት ላሳዩ ሰዎች ክትትል ማድረጋችን አገልግሎታችንን ሙሉ በመሉ ለመፈጸም ያለንን ፍላጎት ያሳያል። (2 ጢሞ. 4:5) አድማጮቻችንን የዘላለም ሕይወት እንዲያገኙ ልንረዳቸው እንችል ይሆናል።— ዮሐ. 17:3