የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
የኢትዮጵያ ምልክት ቋንቋ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • nwt ዕንባቆም
  • ዕንባቆም

በዚህ ክፍል ውስጥ ምንም ቪዲዮ አይገኝም።

ይቅርታ፣ ቪዲዮውን ማጫወት አልተቻለም።

  • ዕንባቆም
  • አዲስ ዓለም ትርጉም መጽሐፍ ቅዱስ
አዲስ ዓለም ትርጉም መጽሐፍ ቅዱስ
ዕንባቆም

ዕንባቆም

1 ነቢዩ ዕንባቆም* በራእይ የተቀበለው መልእክት፦

 2 ይሖዋ ሆይ፣ እርዳታ ለማግኘት ስጮኽ የማትሰማው እስከ መቼ ነው?+

ከግፍ እንድታስጥለኝ ስለምን ጣልቃ የማትገባው እስከ መቼ ነው?*+

 3 ለምን በደል ሲፈጸም እንዳይ ታደርገኛለህ?

ጭቆናንስ ለምን ዝም ብለህ ታያለህ?

ጥፋትና ግፍ በፊቴ የሚፈጸመው ለምንድን ነው?

ጠብና ግጭትስ ለምን በዛ?

 4 ስለዚህ ሕግ ላልቷል፤

ፍትሕም ጨርሶ የለም።

ክፉው ጻድቁን ከቦታልና፤

ከዚህ የተነሳ ፍትሕ ተጣሟል።+

 5 “ብሔራትን እዩ፣ ደግሞም ልብ በሉ!

በመገረም ተመልከቱ፤ ተደነቁም፤

እናንተ ቢነገራችሁም እንኳ የማታምኑት አንድ ነገር

በዘመናችሁ ይከናወናልና።+

 6 እነሆ፣ ጨካኝና ፈጣን የሆነውን ብሔር ይኸውም

ከለዳውያንን አስነሳለሁና።+

የእነሱ ያልሆኑ ቤቶችን ለመውረስ፣

ሰፋፊ የምድር ክፍሎችን ይወራሉ።+

 7 እነሱ አስደንጋጭና አስፈሪ ናቸው።

የገዛ ራሳቸውን ፍትሕና ሥልጣን* ያቋቁማሉ።+

 8 ፈረሶቻቸው ከነብር ይልቅ ፈጣኖች ናቸው፤

ከሌሊት ተኩላዎችም ይልቅ ጨካኞች ናቸው።+

የጦር ፈረሶቻቸው በፍጥነት ይጋልባሉ፤

ፈረሶቻቸው ከሩቅ ስፍራ ይመጣሉ።

ለመብላት እንደሚጣደፍ ንስር ተምዘግዝገው ይወርዳሉ።+

 9 ሁሉም ዓመፅ ለመፈጸም ቆርጠው ይመጣሉ።+

እንደ ምሥራቅ ነፋስ ፊታቸውን ያቀናሉ፤+

ምርኮኞችንም እንደ አሸዋ ያፍሳሉ።

10 በነገሥታት ይሳለቃሉ፤

በከፍተኛ ባለሥልጣናትም ላይ ይስቃሉ።+

በተመሸገ ስፍራ ሁሉ ላይ ይስቃሉ፤+

የአፈር ቁልልም ሠርተው ይይዙታል።

11 ከዚያም እንደ ነፋስ ወደ ፊት እየገሰገሱ በምድሪቱ ላይ ያልፋሉ፤

ይሁንና በደለኛ ይሆናሉ፤+

ምክንያቱም የኃይላቸው ምንጭ አምላካቸው እንደሆነ* ይናገራሉ።”+

12 ይሖዋ ሆይ፣ አንተ ከዘላለም አንስቶ ያለህ አይደለህም?+

ቅዱስ የሆንከው አምላኬ ሆይ፣ አንተ አትሞትም።*+

ይሖዋ ሆይ፣ እነሱን ፍርድ ለማስፈጸም ሾመሃቸዋል፤

ዓለቴ+ ሆይ፣ ቅጣት ለማስፈጸም* አቋቁመሃቸዋል።+

13 ዓይኖችህ ክፉ የሆነውን ነገር እንዳያዩ እጅግ ንጹሐን ናቸው፤

ክፋትንም ዝም ብለህ ማየት አትችልም።+

ታዲያ ከዳተኛውን ዝም ብለህ የምትመለከተው ለምንድን ነው?+

ደግሞስ ክፉ ሰው ከእሱ ይልቅ ጻድቅ የሆነውን ሲውጥ ለምን ዝም ትላለህ?+

14 ሰው እንደ ባሕር ዓሣ፣

ገዢም እንደሌላቸው መሬት ለመሬት የሚሳቡ ፍጥረታት እንዲሆን ለምን ትፈቅዳለህ?

15 እሱ* እነዚህን ሁሉ በመንጠቆ ጎትቶ ያወጣል።

በመረቡ ይይዛቸዋል፤

በዓሣ ማጥመጃ መረቡም ይሰበስባቸዋል።

በዚህም እጅግ ሐሴት ያደርጋል።+

16 በመሆኑም ለመረቡ መሥዋዕት ይሠዋል፤

ለዓሣ ማጥመጃ መረቡም መሥዋዕት* ያቀርባል፤

በእነሱ የተነሳ ድርሻው በቅባት ተሞልቷል፤

ምግቡም ምርጥ ነው።

17 ታዲያ መረቡን ሁልጊዜ ያራግፋል?*

ብሔራትንስ ያለርኅራኄ መፍጀቱን ይቀጥላል?+

2 በጥበቃ ቦታዬ ላይ እሰየማለሁ፤+

በመከላከያ ግንቧም ላይ እቆማለሁ።

በእኔ አማካኝነት ምን መናገር እንደሚፈልግ ለማየትና

በምወቀስበት ጊዜ ምን መልስ እንደምሰጥ ለማወቅ በንቃት እጠባበቃለሁ።

 2 ይሖዋም እንዲህ ሲል መለሰልኝ፦

“ድምፁን ከፍ አድርጎ የሚያነበው ሰው በቀላሉ* እንዲያነበው+

ራእዩን ጻፈው፤ በጽላትም ላይ ግልጽ በሆነ መንገድ ቅረጸው።+

 3 ራእዩ የተወሰነለትን ጊዜ ገና ይጠብቃልና፤

ወደ ፍጻሜውም ይቸኩላል፤ ደግሞም አይዋሽም።

ቢዘገይ* እንኳ በተስፋ ጠብቀው!*+

ያላንዳች ጥርጥር ይፈጸማልና።

ራእዩ አይዘገይም!

 4 ኩሩ የሆነውን ተመልከት፤*

ውስጡ ቀና አይደለም።

ጻድቅ ግን በታማኝነቱ* በሕይወት ይኖራል።+

 5 በእርግጥም የወይን ጠጅ አታላይ ስለሆነ

እብሪተኛው ሰው ግቡን አይመታም።

ፍላጎቱን* እንደ መቃብር* ያሰፋል፤

እሱ እንደ ሞት ነው፤ ደግሞም ሊጠግብ አይችልም።

ብሔራትን ሁሉ ወደ ራሱ መሰብሰቡን ይቀጥላል፤

ሕዝቦችንም ሁሉ ለራሱ ያከማቻል።+

 6 እነዚህ ሁሉ ሰዎች በእሱ ላይ አይተርቱም? ደግሞስ አሽሙርና ግራ የሚያጋባ ቃል አይሰነዝሩም?+

እንዲህ ይላሉ፦

‘የራሱ ያልሆነውን የሚያጋብስ፣

ዕዳውንም የሚያበዛ ወዮለት!

ይህን የሚያደርገው እስከ መቼ ነው?

 7 አበዳሪዎችህ በድንገት አይነሱም?

ተነስተው በኃይል ይነቀንቁሃል፤

በእነሱም እጅ ለብዝበዛ ትዳረጋለህ።+

 8 ብዙ ብሔራትን ስለዘረፍክ

ከሕዝቦቹ መካከል የቀሩት ሁሉ ይዘርፉሃል፤+

ምክንያቱም አንተ የሰው ልጆችን ደም አፍስሰሃል፤

በምድሪቱ፣ በከተሞችና

በዚያ በሚኖሩት ሁሉ ላይ ግፍ ፈጽመሃል።+

 9 ከጥፋት እጅ ያመልጥ ዘንድ

ጎጆውን ከፍ ባለ ቦታ ላይ ለመሥራት

ለቤቱ አግባብ ያልሆነ ጥቅም የሚሰበስብ ወዮለት!

10 በቤትህ ላይ አሳፋሪ ነገር አሲረሃል።

ብዙ ሕዝቦችን ጠራርገህ በማጥፋት በራስህ* ላይ ኃጢአት ሠርተሃል።+

11 ድንጋይ ከግንቡ ውስጥ ይጮኻል፤

ከጣሪያው እንጨቶችም መካከል አንድ ወራጅ ይመልስለታል።

12 ከተማን ደም በማፍሰስ ለሚገነባና

በዓመፅ ለሚመሠርታት ወዮለት!

13 እነሆ፣ ሰዎች እሳት ለሚበላው ነገር እንዲደክሙ፣

ብሔራትም ከንቱ ለሆነ ነገር እንዲለፉ የሚያደርገው የሠራዊት ጌታ ይሖዋ አይደለም?+

14 ውኃ ባሕርን እንደሚሸፍን፣

ምድርም የይሖዋን ክብር በማወቅ ትሞላለችና።+

15 እርቃናቸውን ለማየት ሲል

ታላቅ ቁጣውንና ንዴቱን ቀላቅሎ

ለባልንጀሮቹ መጠጥ በመስጠት እንዲሰክሩ ለሚያደርግ ሰው ወዮለት!

16 በክብር ፋንታ ውርደት ትሞላለህ።

አንተ ራስህም ጠጣ፤ ያልተገረዝክ መሆንህንም አሳይ።*

በይሖዋ ቀኝ እጅ ያለው ጽዋ ወደ አንተ ይዞራል፤+

ክብርህም በውርደት ይሸፈናል፤

17 በሊባኖስ ላይ የተፈጸመው ግፍ ይሸፍንሃል፤

አራዊትንም ያሸበረው ጥፋት በአንተ ላይ ይደርሳል፤

ምክንያቱም አንተ የሰዎችን ደም አፍስሰሃል፤

በምድር፣ በከተሞቿና

በውስጧ በሚኖሩ ሁሉ ላይ ግፍ ፈጽመሃል።+

18 የተቀረጸ ምስል፣

ሠሪው የቀረጸው ከሆነ ምን ጥቅም አለው?

ሠሪው እምነት ቢጥልበትም እንኳ

ከብረት የተሠራ ሐውልትና* ሐሰትን የሚናገር አስተማሪ ምን ፋይዳ አለው?

መናገር የማይችሉ ከንቱ አማልክት መሥራት ምን እርባና አለው?+

19 እንጨቱን “ንቃ!”

መናገር የማይችለውንም ድንጋይ “ተነስ! አስተምረን!” ለሚል ወዮለት!

እነሆ፣ በወርቅና በብር ተለብጧል፤+

በውስጡም እስትንፋስ የለም።+

20 ይሖዋ ግን በቅዱስ ቤተ መቅደሱ ውስጥ ነው።+

ምድር ሁሉ በፊቱ ጸጥ በይ!’”+

3 ነቢዩ ዕንባቆም በሙሾ* ያቀረበው ጸሎት፦

 2 ይሖዋ ሆይ፣ ስለ አንተ የተወራውን ሰምቻለሁ።

ይሖዋ ሆይ፣ ሥራህ ፍርሃት* አሳደረብኝ።

በዓመታት መካከል* ሥራህን ሕያው አድርግ!

በዓመታትም መካከል* ሥራህን አሳውቅ።

መዓት በሚወርድበት ጊዜ ምሕረትን አስታውስ።+

 3 አምላክ ከቴማን፣

ቅዱሱም ከፋራን ተራራ መጣ።+ (ሴላ)*

ግርማው ሰማያትን ሸፈነ፤+

ምድርም በውዳሴው ተሞላች።

 4 ጸዳሉ እንደ ፀሐይ ብርሃን ነው።+

ከእጁ ሁለት ጨረሮች ፈነጠቁ፤

ብርታቱም በዚያ ተሰውሯል።

 5 ቸነፈር ከፊቱ ሄደ፤+

የሚያቃጥል ትኩሳትም እግር በእግር ተከተለው።

 6 ቆመ፤ ምድርንም አንቀጠቀጠ።+

ባየም ጊዜ ብሔራትን አብረከረካቸው።+

ዘላለማዊ የሆኑት ተራሮች ተፈረካከሱ፤

የጥንቶቹ ኮረብቶች ተደፉ።+

የጥንቶቹ መንገዶች የእሱ ናቸው።

 7 በኩሻን ድንኳኖች ውስጥ ችግር አየሁ።

የምድያም የድንኳን ሸራዎች ተንቀጠቀጡ።+

 8 ይሖዋ ሆይ፣ ቁጣህ የነደደው በወንዞች ላይ ነው?

በእርግጥ በወንዞች ላይ ነው?

ወይስ ታላቅ ቁጣህን የገለጽከው በባሕሩ ላይ ነው?+

በፈረሶችህ ላይ ተቀምጠህ ጋልበሃልና፤+

ሠረገሎችህ ድል ተቀዳጅተዋል።*+

 9 የቀስትህ ሽፋን ተነስቷል፤ ቀስትህም ተዘጋጅቷል።

ዘንጎቹ* በመሐላ ተመድበዋል።* (ሴላ)

ምድሪቱን በወንዞች ከፈልክ።

10 ተራሮች አንተን ሲያዩ በሥቃይ ተንፈራገጡ።+

ዶፍ ዝናብ ጠራርጎ ሄደ።

ጥልቁ በኃይል ጮኸ።+

እጁን ወደ ላይ አነሳ።

11 ፀሐይና ጨረቃ ከፍ ባለው መኖሪያ ስፍራቸው ቆሙ።+

ፍላጾችህ እንደ ብርሃን ተወረወሩ።+

ጦርህ እንደ መብረቅ አብረቀረቀ።

12 በምድር ላይ በቁጣ ዘመትክ።

ብሔራትን በቁጣ ረገጥካቸው።*

13 ሕዝብህን ለመታደግ፣ የቀባኸውንም ለማዳን ወጣህ።

የክፉውን ቤት መሪ* አደቀቅክ።

ቤቱ ከመሠረቱ አንስቶ እስከ አናቱ* ድረስ ተጋለጠ። (ሴላ)

14 እኔን ለመበታተን በቁጣ በተነሱ ጊዜ

በገዛ ራሱ መሣሪያዎች* የተዋጊዎቹን ራስ ወጋህ።

እነሱ ጎስቋላውን ሰው በስውር በመዋጥ ሐሴት አድርገዋል።

15 በባሕር ውስጥ፣ በሚናወጠው ብዙ ውኃ መካከል

በፈረሶችህ እየጋለብክ አለፍክ።

16 እኔ ሰማሁ፤ ሆዴም ታወከ፤

ከድምፁ የተነሳ ከንፈሮቼ ተንቀጠቀጡ።

አጥንቶቼም ነቀዙ፤+

ከታች ያሉት እግሮቼ ተብረከረኩ።

ሆኖም የጭንቀትን ቀን ዝም ብዬ እጠብቃለሁ፤+

ይህ ቀን ጥቃት በሚሰነዝርብን ሕዝብ ላይ ይመጣልና።

17 የበለስ ዛፍ ባያፈራ፣

የወይን ተክልም ፍሬ ባይሰጥ፣

የወይራ ዛፍም ባያፈራ፣

እርሻዎቹም* እህል ባይሰጡ፣

መንጋው ከጉረኖው ቢጠፋ፣

ከብቶቹም ሁሉ በረት ውስጥ ባይገኙ፣

18 እኔ ግን በይሖዋ ሐሴት አደርጋለሁ፤

አዳኜ በሆነውም አምላክ እደሰታለሁ።+

19 ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ብርታቴ ነው፤+

እግሮቼን እንደ ዋልያ እግሮች ያደርጋል፤

በከፍታ ስፍራዎችም ላይ ያስኬደኛል።+

ለዘማሪዎች አለቃ፤ በባለ አውታር መሣሪያዎቼ።

“አጥብቆ ማቀፍ” የሚል ትርጉም ሊኖረው ይችላል።

ወይም “የማታድነው እስከ መቼ ነው?”

ወይም “ክብር።”

“ኃይላቸው አምላካቸው እንደሆነ” ማለትም ሊሆን ይችላል።

“እኛ አንሞትም” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ወይም “እንዲወቅሱ።”

ከለዳዊ የሆነ ጠላትን ያመለክታል።

ወይም “የሚጨስ መሥዋዕት።”

“ሁልጊዜ ሰይፉን ይመዛል?” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ወይም “አቀላጥፎ።”

ወይም “የሚዘገይ ቢመስልም።”

ወይም “ቢዘገይ እንኳ በጉጉት ጠብቀው!”

ወይም “እነሆ፣ ነፍሱ በትዕቢት ተወጥራለች።”

“በእምነቱ” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ወይም “ነፍሱን።”

ወይም “ሲኦል።” የሰው ልጆችን ሁሉ መቃብር ያመለክታል። የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ወይም “በነፍስህ።”

“ተንገዳገድም” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ወይም “ቀልጦ የተሠራ ሐውልትና።”

ወይም “በሐዘን እንጉርጉሮ።”

ወይም “አክብሮታዊ ፍርሃት።”

“በእኛ ዘመን” ማለትም ሊሆን ይችላል።

“በእኛም ዘመን” ማለትም ሊሆን ይችላል።

የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ወይም “መዳን አስገኝተዋል።”

“ቀስቶቹ” ማለትም ሊሆን ይችላል።

“ነገዶቹ የገቧቸው ቃለ መሐላዎች ተገልጸዋል” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ቃል በቃል “ወቃሃቸው።”

ቃል በቃል “ራስ።”

ቃል በቃል “አንገቱ።”

ቃል በቃል “በዘንጎቹ።”

ወይም “እርከኖቹም።”

    የኢትዮጵያ ምልክት ቋንቋ ጽሑፎች (2011-2025)
    ውጣ
    ግባ
    • የኢትዮጵያ ምልክት ቋንቋ
    • አጋራ
    • የግል ምርጫዎች
    • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
    • የአጠቃቀም ውል
    • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
    • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
    • JW.ORG
    • ግባ
    አጋራ