የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
የኢትዮጵያ ምልክት ቋንቋ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • nwt ምሳሌ 1:1-31:31
  • ምሳሌ

በዚህ ክፍል ውስጥ ምንም ቪዲዮ አይገኝም።

ይቅርታ፣ ቪዲዮውን ማጫወት አልተቻለም።

  • ምሳሌ
  • አዲስ ዓለም ትርጉም መጽሐፍ ቅዱስ
አዲስ ዓለም ትርጉም መጽሐፍ ቅዱስ
ምሳሌ

ምሳሌ

1 የእስራኤል ንጉሥ፣+ የዳዊት ልጅ+ የሰለሞን ምሳሌዎች፦+

 2 ጥበብንና+ ተግሣጽን ለመማር፣*

ጥበብ ያዘሉ አባባሎችን ለመረዳት፣

 3 ጥልቅ ማስተዋል፣ ጽድቅ፣+ ጥሩ ፍርድና*+

ቅንነት* የሚያስገኝ ተግሣጽ ለመቀበል፣+

 4 ተሞክሮ ለሌላቸው ብልሃትን፣+

ለወጣቶች እውቀትንና የማመዛዘን ችሎታን ለመስጠት።+

 5 ጥበበኛ ሰው ያዳምጣል፤ ደግሞም ተጨማሪ ትምህርት ይቀስማል፤+

ማስተዋል ያለው ሰውም ጥበብ ያለበትን መመሪያ ይቀበላል፤+

 6 ይህም ምሳሌንና ስውር የሆነ አባባልን

እንዲሁም የጥበበኞችን ቃላትና የሚናገሩትን እንቆቅልሽ ይረዳ ዘንድ ነው።+

 7 ይሖዋን መፍራት* የእውቀት መጀመሪያ ነው።+

ጥበብንና ተግሣጽን የሚንቁት ሞኞች ብቻ ናቸው።+

 8 ልጄ ሆይ፣ የአባትህን ተግሣጽ አዳምጥ፤+

የእናትህንም መመሪያ* አትተው።+

 9 ለራስህ የሚያምር የአበባ ጉንጉን፣+

ለአንገትህም ውብ ጌጥ ይሆንልሃል።+

10 ልጄ ሆይ፣ ኃጢአተኞች ሊያግባቡህ ቢሞክሩ እሺ አትበላቸው።+

11 እንዲህ ይሉህ ይሆናል፦ “ና አብረን እንሂድ።

ደም ለማፍሰስ እናድባ።

ንጹሐን ሰዎችን ያለምክንያት ለማጥቃት እናደፍጣለን።

12 እንደ መቃብር፣* በሕይወት እንዳሉ እንውጣቸዋለን፤

ወደ ጉድጓድ እንደሚወርዱ ሰዎች ሙሉ በሙሉ እንሰለቅጣቸዋለን።

13 ውድ ሀብታቸውን ሁሉ እንውሰድባቸው፤

ቤቶቻችንን በዘረፍናቸው ነገሮች እንሞላለን።

14 ከእኛ ጋር ልትተባበር ይገባል፤*

ሁላችንም የሰረቅነውን እኩል እንካፈላለን።”*

15 ልጄ ሆይ፣ አትከተላቸው።

እግርህን ከመንገዳቸው አርቅ፤+

16 እግሮቻቸው ክፉ ነገር ለመሥራት ይሮጣሉና፤

ደም ለማፍሰስ ይጣደፋሉ።+

17 ወፎች ዓይናቸው እያየ እነሱን ለማጥመድ መረብ መዘርጋት ከንቱ ነው።

18 እነዚህ ሰዎች ደም ለማፍሰስ የሚያደቡት ለዚህ ነው፤

የሰዎችን ሕይወት* ለማጥፋት ያደፍጣሉ።

19 በማጭበርበር ትርፍ ለማግኘት የሚሹ መንገዳቸው ይህ ነው፤

እንዲህ ያለው ትርፍ የተጠቃሚዎቹን ሕይወት* ያጠፋል።+

20 እውነተኛ ጥበብ+ በጎዳና ላይ ትጮኻለች።+

በአደባባይ ላይ ያለማቋረጥ ድምፅዋን ታሰማለች።+

21 ሰው በሚበዛባቸው ጎዳናዎች ማዕዘን* ላይ ሆና ትጣራለች።

በከተማው መግቢያ በሮች ላይ እንዲህ ትላለች፦+

22 “እናንተ አላዋቂዎች እስከ መቼ አላዋቂነትን ትወዳላችሁ?

እናንተ ፌዘኞች እስከ መቼ በሌሎች ላይ በማፌዝ ትደሰታላችሁ?

እናንተ ሞኞች እስከ መቼ እውቀትን ትጠላላችሁ?+

23 ለወቀሳዬ ምላሽ ስጡ።*+

እንዲህ ብታደርጉ መንፈሴን አፈስላችኋለሁ፤

ቃሌን አሳውቃችኋለሁ።+

24 በተጣራሁ ጊዜ በእንቢተኝነታችሁ ጸንታችኋል፤

እጄን በዘረጋሁ ጊዜ ማንም ትኩረት አልሰጠም፤+

25 ምክሬን ሁሉ ችላ ብላችኋል፤

ወቀሳዬንም አልተቀበላችሁም፤

26 እኔም ጥፋት ሲደርስባችሁ እስቃለሁ፤

የፈራችሁት ነገር ሲደርስ አላግጥባችኋለሁ፤+

27 የፈራችሁት ነገር እንደ ማዕበል ሲደርስባችሁ፣

ጥፋታችሁም እንደ አውሎ ነፋስ ከተፍ ሲልባችሁ፣

ጭንቀትና መከራ ሲመጣባችሁ አፌዝባችኋለሁ።

28 በዚያን ጊዜ ደጋግመው ይጠሩኛል፤ እኔ ግን አልመልስላቸውም፤

አጥብቀው ይፈልጉኛል፤ ሆኖም አያገኙኝም፤+

29 ምክንያቱም እውቀትን ጠልተዋል፤+

ይሖዋን መፍራትንም አልወደዱም።+

30 ምክሬን አልተቀበሉም፤

ወቀሳዬን ሁሉ አቃለዋል።

31 ስለዚህ መንገዳቸው የሚያስከትለውን መዘዝ ይቀበላሉ፤*+

በገዛ ራሳቸውም ምክር* ከልክ በላይ ይጠግባሉ።

32 ተሞክሮ የሌላቸውን ሰዎች ጋጠወጥነታቸው ይገድላቸዋልና፤

ሞኞችን ደግሞ ቸልተኝነታቸው ያጠፋቸዋል።

33 እኔን የሚሰማ ሰው ግን ተረጋግቶ ይኖራል፤+

መከራ ይደርስብኛል የሚል ስጋትም አያድርበትም።”+

2 ልጄ ሆይ፣ ቃሌን ብትቀበልና

ትእዛዛቴን እንደ ውድ ሀብት ብታስቀምጥ፣+

 2 ይህን ለማድረግ ጆሮህን ወደ ጥበብ ብታቀና፣+

ጥልቅ ግንዛቤ ለማግኘት ልብህን ብታዘነብል፣+

 3 ደግሞም ማስተዋልን ብትጣራና+

ጥልቅ ግንዛቤ ለማግኘት ድምፅህን ብታሰማ፣+

 4 እንደ ብር ተግተህ ብትፈልጋት፣+

እንዲሁም እንደተሸሸገ ሀብት አጥብቀህ ብትሻት፣+

 5 ያን ጊዜ ይሖዋን መፍራት ምን ማለት እንደሆነ ትረዳለህ፤+

ደግሞም ስለ አምላክ እውቀት ትቀስማለህ።+

 6 ይሖዋ ራሱ ጥበብ ይሰጣልና፤+

ከአፉ እውቀትና ጥልቅ ግንዛቤ ይወጣል።

 7 ለቅኖች ጥበብን* እንደ ውድ ሀብት ያከማቻል፤

ንጹሕ አቋማቸውን* ጠብቀው ለሚመላለሱት ጋሻ ነው።+

 8 የፍትሕን ጎዳና ይከታተላል፤

የታማኞቹንም መንገድ ይጠብቃል።+

 9 በዚህ ጊዜ ጽድቅ፣ ፍትሕና ትክክል የሆነውን ነገር

ይኸውም የጥሩነትን ጎዳና በሙሉ ትረዳለህ።+

10 ጥበብ ወደ ልብህ ስትገባና+

እውቀት ነፍስህን* ደስ ስታሰኝ፣+

11 የማመዛዘን ችሎታ ምንጊዜም ይጠብቅሃል፤+

ጥልቅ ግንዛቤም ይጋርድሃል፤

12 ይህም አንተን ከክፉ መንገድ ለማዳን

እንዲሁም ጠማማ ነገር ከሚናገር ሰው፣+

13 በጨለማ መንገድ ለመጓዝ

ቀናውን ጎዳና ከሚተዉ፣+

14 መጥፎ ድርጊት በመፈጸም ሐሴት ከሚያደርጉ፣

ጠማማ በሆኑ ክፉ ነገሮች ከሚደሰቱ፣

15 መንገዳቸው ጠማማ ከሆነና

አካሄዳቸው በተንኮል ከተሞላ ሰዎች አንተን ለመታደግ ነው።

16 ጋጠወጥ* ከሆነች ሴት፣

ባለጌ* ሴት ከምትናገረው የሚያባብል* ቃል ያድንሃል፤+

17 ይህች ሴት በወጣትነቷ የነበራትን የቅርብ ወዳጇን*+ የምትተው

እንዲሁም ከአምላኳ ጋር የገባችውን ቃል ኪዳን የምትረሳ ናት፤

18 ቤቷ ሰውን ይዞ ወደ ሞት ይወርዳልና፤

አካሄዷም* በሞት ወደተረቱት ይወስዳል።+

19 ከእሷ ጋር ግንኙነት ያላቸው* ሁሉ አይመለሱም፤

የሕይወትንም መንገድ ዳግመኛ አያገኙም።+

20 በመሆኑም የጥሩ ሰዎችን መንገድ ተከተል፤

እንዲሁም ከጻድቃን ጎዳና አትውጣ፤+

21 በምድር ላይ የሚኖሩት ቅኖች ብቻ ናቸውና፤

በእሷም ላይ የሚቀሩት ነቀፋ የሌለባቸው* ናቸው።+

22 ክፉዎች ግን ከምድር ገጽ ይጠፋሉ፤+

ከዳተኞችም ከእሷ ይወገዳሉ።+

3 ልጄ ሆይ፣ ትምህርቴን* አትርሳ፤

ልብህም ትእዛዛቴን ይጠብቅ፤

 2 ረጅም ዕድሜና የሕይወት ዘመን

እንዲሁም ሰላም ያስገኙልሃልና።+

 3 ታማኝ ፍቅርና ታማኝነት* አይለዩህ።+

በአንገትህ ዙሪያ እሰራቸው፤

በልብህ ጽላት ላይ ጻፋቸው፤+

 4 ያን ጊዜ በአምላክና በሰው ፊት ሞገስ ታገኛለህ፤+

እንዲሁም ጥሩ ማስተዋል እንዳለህ ታስመሠክራለህ።

 5 በሙሉ ልብህ በይሖዋ ታመን፤+

ደግሞም በገዛ ራስህ ማስተዋል አትመካ።*+

 6 በመንገድህ ሁሉ እሱን ግምት ውስጥ አስገባ፤+

እሱም ጎዳናህን ቀና ያደርገዋል።+

 7 በራስህ አመለካከት ጥበበኛ አትሁን።+

ይሖዋን ፍራ፤ ከክፉም ራቅ።

 8 ለሰውነትህ* ፈውስ፣

ለአጥንትህም ብርታት ይሆንልሃል።

 9 ባሉህ ውድ ነገሮች፣+

ከምርትህ* ሁሉ በኩራት* ይሖዋን አክብር፤+

10 ይህን ካደረግክ ጎተራዎችህ ጢም ብለው ይሞላሉ፤+

በወይን መጭመቂያዎችህም አዲስ የወይን ጠጅ ሞልቶ ይፈስሳል።

11 ልጄ ሆይ፣ የይሖዋን ተግሣጽ ለመቀበል እንቢተኛ አትሁን፤+

ወቀሳውም አያስመርርህ፤+

12 አባት ደስ የሚሰኝበትን ልጁን እንደሚወቅስ ሁሉ

ይሖዋም የሚወዳቸውን ይወቅሳልና።+

13 ጥበብን የሚያገኝ፣+

ጥልቅ ግንዛቤንም የራሱ የሚያደርግ ሰው ደስተኛ ነው፤

14 ጥበብን ማግኘት ብርን ከማግኘት የተሻለ ነው፤

እሷንም ማትረፍ ወርቅ ከማግኘት የተሻለ ነው።+

15 ከዛጎል* ይበልጥ ውድ ናት፤

አንተ የምትመኘው ማንኛውም ነገር ሊተካከላት አይችልም።

16 በቀኟ ረጅም ዕድሜ አለ፤

በግራዋም ሀብትና ክብር ይገኛል።

17 መንገዷ ደስ የሚያሰኝ ነው፤

ጎዳናዋም ሁሉ ሰላም የሰፈነበት ነው።+

18 ለሚይዟት የሕይወት ዛፍ ናት፤

አጥብቀው የሚይዟትም ደስተኞች ይባላሉ።+

19 ይሖዋ በጥበብ ምድርን መሠረተ።+

በማስተዋል ሰማያትን አጸና።+

20 በእውቀቱ ጥልቅ ውኃዎች ተከፈሉ፤

ደመና ያዘሉ ሰማያትም ጠል አንጠባጠቡ።+

21 ልጄ ሆይ፣ እነዚህ ባሕርያት ከእይታህ አይራቁ።*

ጥበብንና* የማመዛዘን ችሎታን ጠብቅ፤

22 ሕይወት ያስገኙልሃል፤*

ለአንገትህም ጌጥ ይሆናሉ፤

23 በዚያን ጊዜ በመንገድህ ላይ ተማምነህ ትሄዳለህ፤

እግርህም ፈጽሞ አይሰናከልም።*+

24 በምትተኛበት ጊዜ አትፈራም፤+

ትተኛለህ፤ እንቅልፍህም ጣፋጭ ይሆናል።+

25 ድንገት የሚከሰት የሚያሸብር ነገርም+ ሆነ

በክፉ ሰዎች ላይ የሚመጣ መዓት አያስፈራህም።+

26 ይሖዋ መታመኛህ ይሆናልና፤+

እግርህን በወጥመድ እንዳይያዝ ይጠብቃል።+

27 ሰዎችን ለመርዳት የሚያስችል አቅም ካለህ*+

ለሚገባቸው መልካም ነገር ከማድረግ ወደኋላ አትበል።+

28 ለባልንጀራህ አሁኑኑ መስጠት እየቻልክ

“ሂድና በኋላ ተመልሰህ ና! ነገ እሰጥሃለሁ” አትበለው።

29 ከአንተ ጋር ተማምኖ እየኖረ ሳለ

ባልንጀራህን ለመጉዳት አታሲር።+

30 መጥፎ ነገር ካላደረገብህ

ከሰው ጋር ያለምክንያት አትጣላ።+

31 በዓመፀኛ ሰው አትቅና፤+

የትኛውንም መንገዱን አትምረጥ፤

32 ይሖዋ ተንኮለኛን ሰው ይጸየፋልና፤+

ከቅኖች ጋር ግን የጠበቀ ወዳጅነት አለው።+

33 ይሖዋ የክፉውን ቤት ይረግማል፤+

የጻድቁን መኖሪያ ግን ይባርካል።+

34 በፌዘኞች ላይ ይሳለቃል፤+

ለየዋሆች ግን ሞገስ ያሳያል።+

35 ጥበበኞች ክብርን ይወርሳሉ፤

ሞኞች ግን ለውርደት የሚዳርግን ነገር ከፍ አድርገው ይመለከታሉ።+

4 ልጆቼ ሆይ፣ የአባትን ተግሣጽ ስሙ፤+

ማስተዋል እንድታገኙ በትኩረት አዳምጡ፤

 2 ጥሩ መመሪያ እሰጣችኋለሁና፤

ትምህርቴን* አትተዉ።+

 3 እኔ ለአባቴ ጥሩ ልጅ ነበርኩ፤+

እናቴም ለእኔ ልዩ ፍቅር ነበራት።+

 4 አባቴ እንዲህ ሲል አስተማረኝ፦ “ልብህ ቃሌን አጥብቆ ይያዝ።+

ትእዛዛቴን ጠብቅ፤ በሕይወትም ትኖራለህ።+

 5 ጥበብን አግኝ፤ ማስተዋልንም አዳብር።+

የምናገረውን ነገር አትርሳ፤ ከእሱም ፈቀቅ አትበል።

 6 ጥበብን አትተዋት፤ እሷም ትጠብቅሃለች።

ውደዳት፤ እሷም ትከልልሃለች።

 7 ጥበብ በጣም አስፈላጊ* ነገር ናት፤+ ስለዚህ ጥበብን አግኝ፤

ደግሞም ባለህ ነገር ሁሉ ማስተዋልን ለማግኘት ጥረት አድርግ።+

 8 ለጥበብ የላቀ ዋጋ ስጥ፤ እሷም ከፍ ከፍ ታደርግሃለች።+

ብታቅፋት ታከብርሃለች።+

 9 በራስህ ላይ የሚያምር የአበባ ጉንጉን ትደፋልሃለች፤

በውበት አክሊልም ታስጌጥሃለች።”

10 ልጄ ሆይ፣ አዳምጥ፤ የምናገረውንም ተቀበል፤

የሕይወትህም ዘመን ይረዝማል።+

11 በጥበብ መንገድ እንድትሄድ አስተምርሃለሁ፤+

ቀና በሆነ ጎዳና እመራሃለሁ።+

12 በምትጓዝበት ጊዜ እርምጃህ አይስተጓጎልም፤

ብትሮጥም አትሰናከልም።

13 ተግሣጽን ያዛት፤ አትልቀቃትም።+

ጠብቃት፤ ሕይወትህ ናትና።+

14 ወደ ክፉዎች መንገድ አትግባ፤

በመጥፎ ሰዎች ጎዳናም አትሂድ።+

15 ከእሱ ራቅ፤ በዚያም አትሂድ፤+

ከዚያ ጎዳና ፈቀቅ በል፤ ደግሞም አልፈኸው ሂድ።+

16 እነሱ ክፋት ካልሠሩ አይተኙምና።

ሰውን ለውድቀት ካልዳረጉ እንቅልፍ በዓይናቸው አይዞርም።

17 የክፋት ምግብ ይበላሉ፤

የዓመፅም ወይን ጠጅ ይጠጣሉ።

18 የጻድቃን መንገድ ግን ፍንትው ብሎ እንደሚወጣ የማለዳ ብርሃን ነው፤

እንደ ቀትር ብርሃን ቦግ ብሎ እስኪበራም ድረስ እየደመቀ ይሄዳል።+

19 የክፉዎች መንገድ እንደ ጨለማ ነው፤

ምን እንደሚያሰናክላቸው አያውቁም።

20 ልጄ ሆይ፣ ቃሌን በትኩረት ተከታተል፤

ንግግሬን በጥሞና አዳምጥ።*

21 ከእይታህ አይራቅ፤

በልብህ ውስጥ አስቀምጠው፤+

22 ለሚያገኙት ሕይወት ነውና፤+

ለመላ አካላቸውም* ጤና ነው።

23 ከምንም ነገር በላይ ልብህን ጠብቅ፤+

የሕይወት ምንጭ ከእሱ ዘንድ ነውና።

24 ጠማማ አንደበትን ከአንተ አስወግድ፤+

አታላይ የሆነን ንግግርም ከአንተ አርቅ።

25 ዓይኖችህ በቀጥታ ይዩ፤

አዎ፣ ፊት ለፊት በትኩረት ተመልከት።*+

26 የእግርህን መንገድ ደልዳላ አድርግ፤*+

መንገድህም ሁሉ አስተማማኝ ይሆናል።

27 ወደ ቀኝም ሆነ ወደ ግራ ዞር አትበል።+

እግርህን ከክፉ ነገር መልስ።

5 ልጄ ሆይ፣ ጥበቤን ልብ በል።

ማስተዋልን በተመለከተ የምሰጠውን ትምህርት በጥሞና አዳምጥ፤*+

 2 ይህም የማመዛዘን ችሎታህን እንድትጠብቅ፣

በከንፈሮችህም እውቀትን በጥንቃቄ እንድትይዝ ነው።+

 3 የጋጠወጥ* ሴት ከንፈር እንደ ማር እንጀራ ያንጠባጥባልና፤+

አፏም ከዘይት ይለሰልሳል።+

 4 በመጨረሻ ግን እንደ ጭቁኝ ትመርራለች፤+

ደግሞም በሁለት በኩል እንደተሳለ ሰይፍ ትሆናለች።+

 5 እግሮቿ ወደ ሞት ይወርዳሉ።

እርምጃዎቿ በቀጥታ ወደ መቃብር* ይመራሉ።

 6 ስለ ሕይወት መንገድ ግድ የላትም።

በጎዳናዎቿ ላይ ትባዝናለች፤ ወዴት እንደሚወስዱም አታውቅም።

 7 እንግዲህ ልጆቼ ሆይ፣ አዳምጡኝ፤

ከምናገረውም ቃል አትራቁ።

 8 ከእሷ ራቅ፤

ወደ ቤቷም ደጃፍ አትቅረብ፤+

 9 ይህም ክብርህን ለሌሎች አሳልፈህ እንዳትሰጥ ነው፤+

ቀሪ የሕይወት ዘመንህም በመከራ የተሞላ እንዳይሆን ነው፤+

10 ደግሞም እንግዳ የሆኑ ሰዎች ጥሪትህን* እንዳያሟጥጡ፣+

የለፋህበትንም ነገር የባዕድ አገር ሰው እንዳይወርሰው ነው።

11 አለዚያ በሕይወትህ ማብቂያ

ሥጋህና መላ ሰውነትህ እየመነመነ ሲሄድ ትቃትታለህ፤+

12 ደግሞም እንዲህ ትላለህ፦ “ምነው ተግሣጽን ጠላሁ!

ልቤስ ምነው ወቀሳን ናቀ!

13 የአስተማሪዎቼን ቃል አላዳመጥኩም፤

መምህሮቼንም በጥሞና አልሰማሁም።

14 በመላው ጉባኤ መካከል*

ሙሉ በሙሉ ልጠፋ ምንም አልቀረኝም ነበር።”+

15 ከራስህ ጉድጓድ እንዲሁም

ከገዛ ምንጭህ የሚፈልቀውን ውኃ ጠጣ።*+

16 ምንጮችህ ወደ ውጭ፣

ጅረቶችህም በአደባባይ ሊፈሱ ይገባል?+

17 ለአንተ ብቻ ይሁኑ፤

ከአንተ ጋር ላሉ እንግዶችም አይሁኑ።+

18 ምንጭህ የተባረከ ይሁን፤

ከወጣትነት ሚስትህም ጋር ደስ ይበልህ፤+

19 እሷ እንደምትወደድ ሚዳቋና እንደምታምር የተራራ ፍየል* ናት።+

ጡቶቿ ምንጊዜም ያርኩህ።*

ፍቅሯ ምንጊዜም ይማርክህ።+

20 ልጄ ሆይ፣ ጋጠወጥ* ሴት ለምን ትማርክሃለች?

ባለጌ* ሴትንስ ለምን ታቅፋለህ?+

21 የሰው መንገድ በይሖዋ ዓይኖች ፊት ነውና፤

እሱ መንገዱን ሁሉ ይመረምራል።+

22 ክፉ ሰው የገዛ ጥፋቱ ወጥመድ ይሆንበታል፤

ኃጢአቱም እንደ ገመድ ተብትቦ ይይዘዋል።+

23 ተግሣጽ ከማጣቱ የተነሳ ይሞታል፤

በጣም ሞኝ ከመሆኑም የተነሳ መንገድ ይስታል።

6 ልጄ ሆይ፣ ለባልንጀራህ ዋስ* ብትሆን፣+

የማታውቀውን ሰው እጅ ብትመታ፣*+

 2 በገባኸው ቃል ብትጠመድ፣

ከአፍህ በወጣው ቃል ብትያዝ፣+

 3 ልጄ ሆይ፣ በባልንጀራህ እጅ ወድቀሃልና፣

ይህን በማድረግ ራስህን ነፃ አውጣ፦

ሂድና ባልንጀራህን በትሕትና አጥብቀህ ለምነው።+

 4 ይህን ሳታደርግ አትተኛ፤

በዓይንህም እንቅልፍ አይዙር።

 5 እንደ ሜዳ ፍየል ከአዳኝ እጅ፣

እንደ ወፍም ከወፍ አዳኝ እጅ ራስህን አድን።

 6 አንተ ሰነፍ፣ ወደ ጉንዳን ሂድ፤+

መንገዷንም በጥሞና ተመልክተህ ጥበበኛ ሁን።

 7 አዛዥ፣ አለቃ ወይም ገዢ ባይኖራትም እንኳ፣

 8 ምግቧን በበጋ ታዘጋጃለች፤+

ቀለቧንም በመከር ወቅት ትሰበስባለች።

 9 አንተ ሰነፍ፣ የምትጋደመው እስከ መቼ ነው?

ከእንቅልፍህ የምትነሳውስ መቼ ነው?

10 ቆይ ትንሽ ልተኛ፣ ቆይ ትንሽ ላንቀላፋ፣

እጄንም አጣጥፌ እስቲ ትንሽ ጋደም ልበል ካልክ፣+

11 ድህነት እንደ ወንበዴ፣

እጦትም መሣሪያ እንደታጠቀ ሰው ይመጣብሃል።+

12 የማይረባና ክፉ ሰው ንግግሩ ጠማማ ነው፤+

13 በዓይኑ ይጣቀሳል፤+ በእግሩ ምልክት ይሰጣል፤ በጣቶቹም ይጠቁማል።

14 ጠማማ በሆነው ልቡ፣

ነጋ ጠባ ሴራ ይጠነስሳል፤+ ጠብም ይዘራል።+

15 በመሆኑም ጥፋት በድንገት ይመጣበታል፤

እንደማይጠገን ሆኖ በቅጽበት ይሰበራል።+

16 ይሖዋ የሚጠላቸው ስድስት ነገሮች አሉ፤

እንዲያውም እሱ የሚጸየፋቸው* ነገሮች ሰባት ናቸው፦

17 ትዕቢተኛ ዓይን፣+ ውሸታም ምላስ፣+ ንጹሕ ደም የሚያፈሱ እጆች፣+

18 ክፉ ሐሳብ የሚያውጠነጥን ልብና+ ወደ ክፋት በፍጥነት የሚሮጡ እግሮች፣

19 ባወራ ቁጥር ውሸት የሚናገር ሐሰተኛ ምሥክርና+

በወንድማማቾች መካከል ጠብ የሚዘራ ሰው።+

20 ልጄ ሆይ፣ የአባትህን ትእዛዝ ጠብቅ፤

የእናትህንም መመሪያ* ቸል አትበል።+

21 ምንጊዜም በልብህ አኑራቸው፤

በአንገትህም ዙሪያ እሰራቸው።

22 በምትሄድበት ሁሉ ይመራሃል፤

ስትተኛም ይጠብቅሃል፤

ስትነቃም ያነጋግርሃል።*

23 ትእዛዙ መብራት ነውና፤+

ሕጉም ብርሃን ነው፤+

የተግሣጽ ወቀሳም ወደ ሕይወት ይመራል።+

24 ከክፉ ሴት፣+ ከባለጌ* ሴትም

የሚያባብል አንደበት ይጠብቁሃል።+

25 ውበቷን በልብህ አትመኝ፤+

የሚያማምሩ ዓይኖቿም አይማርኩህ፤

26 አንድ ሰው በዝሙት አዳሪ የተነሳ ለድህነት ይዳረጋልና፤*+

አመንዝራ ሴት ደግሞ የሰውን ውድ ሕይወት* ታጠምዳለች።

27 በጉያው እሳት ታቅፎ ልብሱ የማይቃጠልበት ሰው አለ?+

28 ወይስ በፍም ላይ ተራምዶ እግሮቹ የማይቃጠሉበት ሰው ይኖራል?

29 ከባልንጀራው ሚስት ጋር የሚተኛ ሰውም እንደዚሁ ነው፤

የሚነካት ሁሉ መቀጣቱ አይቀርም።+

30 ሌባ በተራበ ጊዜ ራሱን* ሊያጠግብ ቢሰርቅ፣

ሰዎች በንቀት አያዩትም።

31 በተያዘ ጊዜ ግን ሰባት እጥፍ ይከፍላል፤

በቤቱ ያለውን ውድ ነገር ሁሉ ያስረክባል።+

32 ከሴት ጋር ምንዝር የሚፈጽም ሁሉ ማስተዋል* ይጎድለዋል፤

እንዲህ የሚያደርግ ሰው በራሱ* ላይ ጥፋት ያመጣል።+

33 የሚያተርፈው ነገር ቢኖር ቁስልና ውርደት ነው፤+

ኀፍረቱም መቼም አይወገድም።+

34 ቅናት ባልን እጅግ ያስቆጣዋልና፤

ለበቀል በሚነሳበት ጊዜም ፈጽሞ ርኅራኄ አያሳይም።+

35 ማንኛውንም ዓይነት ካሳ* አይቀበልም፤

ምንም ያህል ስጦታ ብታቀርብለት ቁጣው አይበርድም።

7 ልጄ ሆይ፣ ቃሌን ጠብቅ፤

ትእዛዛቴንም እንደ ውድ ሀብት ያዝ።+

 2 ትእዛዛቴን ጠብቅ፤ በሕይወትም ትኖራለህ፤+

መመሪያዬን* እንደ ዓይንህ ብሌን ጠብቅ።

 3 በጣቶችህ ላይ እሰራቸው፤

በልብህ ጽላት ላይ ጻፋቸው።+

 4 ጥበብን “እህቴ ነሽ” በላት፤

ማስተዋልንም “ዘመዴ” ብለህ ጥራት፤

 5 ጋጠወጥና*+ ባለጌ* ከሆነች ሴት፣

እንዲሁም ከምትናገረው የሚያባብል* ቃል ይጠብቁሃል።+

 6 በቤቴ መስኮት በፍርግርጉ በኩል

አጮልቄ ወደ ታች ተመለከትኩ፤

 7 ደግሞም ሞኞችን* ትክ ብዬ በማይበት ጊዜ፣

በዚያ ከነበሩት ወንዶች ልጆች መካከል ማስተዋል* የጎደለውን አንድ ወጣት አየሁ።+

 8 በቤቷ አቅራቢያ በሚገኝ መታጠፊያ አልፎ

ወደ ቤቷ አቅጣጫ አመራ፤

 9 ቀኑ መሸትሸት ብሎ ለዓይን ያዝ አድርጓል፤+

የሌሊቱ ጨለማ እየተቃረበ ነበር።

10 ከዚያም እንደ ዝሙት አዳሪ* የለበሰችና+

በልቧ አታላይ የሆነች ሴት ከእሱ ጋር ስትገናኝ አየሁ።

11 ሴትየዋ ጯኺና ማን አለብኝ ባይ ነች።+

ፈጽሞ ቤቷ አትቀመጥም።*

12 አንዴ በመንገድ፣ አንዴ በአደባባይ ትታያለች፤

በየመንገዱ መታጠፊያም ታደባለች።+

13 አፈፍ አድርጋ ይዛ ሳመችው፤

ያላንዳች ኀፍረትም እንዲህ አለችው፦

14 “የኅብረት መሥዋዕት ማቅረብ ነበረብኝ።+

ዛሬ ስእለቴን ፈጽሜአለሁ።

15 አንተን ለማግኘት የወጣሁት ለዚህ ነው፤

አንተን ፍለጋ ወጣሁ፤ ደግሞም አገኘሁህ!

16 መኝታዬን ባማረ የአልጋ ልብስ፣

ከግብፅ በመጣ በቀለማት ያሸበረቀ በፍታ አስጊጬዋለሁ።+

17 አልጋዬ ላይ ከርቤ፣ እሬትና* ቀረፋ አርከፍክፌአለሁ።+

18 ና፣ እስኪነጋ ድረስ በፍቅር እንርካ፤

እርስ በርሳችን ፍቅራችንን በመግለጽ እንደሰት፤

19 ባሌ ቤት የለምና፤

ወደ ሩቅ ቦታ ሄዷል።

20 በከረጢት ገንዘብ ይዟል፤

ደግሞም ጨረቃዋ ሙሉ እስክትሆን ድረስ ወደ ቤት አይመለስም።”

21 እንደ ምንም ብላ አግባብታ ታሳስተዋለች።+

በለሰለሰ አንደበቷ ታታልለዋለች።

22 ለእርድ እንደሚነዳ በሬ፣

ለቅጣትም በእግር ግንድ* እንደታሰረ ሞኝ ሰው በድንገት ይከተላታል፤+

23 ፍላጻ ጉበቱን እስኪሰነጥቀው ድረስ፣

በወጥመድ ለመያዝ እንደምትቸኩል ወፍ ተከትሏት ይሄዳል፤ ሕይወቱን* ሊያሳጣው እንደሚችል አላወቀም።+

24 እንግዲህ ልጆቼ ሆይ፣ አዳምጡኝ፤

የምናገረውንም ቃል በትኩረት ስሙ።

25 ልባችሁን ወደ መንገዷ አታዘንብሉ።

መንገድ ስታችሁ ወደ ጎዳናዋ አትግቡ፤+

26 ተሰይፈው እንዲወድቁ ያደረገቻቸው ብዙ ናቸውና፤+

እሷ የገደለቻቸውም እጅግ ብዙ ናቸው።+

27 ቤቷ ወደ መቃብር* ይወስዳል፤

ሙታን ወዳሉበት ስፍራም* ይወርዳል።

8 ጥበብ እየተጣራች አይደለም?

ማስተዋልስ ድምፅዋን ከፍ አድርጋ እያሰማች አይደለም?+

 2 በጎዳና አጠገብ በሚገኙ ከፍታ ቦታዎች፣+

መንገዶች በሚገናኙበት ቦታ ላይ ቆማለች።

 3 ወደ ከተማዋ በሚያስገቡት በሮች አጠገብ፣

በደጆቹ መግቢያዎች ላይ

ድምፅዋን ከፍ አድርጋ ትጮኻለች፦+

 4 “ሰዎች ሆይ፣ የምጣራው እናንተን ነው፤

ድምፄን ከፍ አድርጌ የማሰማው ለሁሉም* ነው።

 5 እናንተ ተሞክሮ የሌላችሁ፣ ብልሃትን ተማሩ፤+

እናንተ ሞኞች፣ አስተዋይ ልብ ይኑራችሁ።

 6 የምናገረው ነገር በጣም አስፈላጊ ስለሆነ አዳምጡኝ፤

ከንፈሮቼ ትክክል የሆነውን ይናገራሉ፤

 7 አንደበቴ በለሰለሰ ድምፅ እውነትን ይናገራልና፤

ከንፈሮቼም ክፋትን ይጸየፋሉ።

 8 ከአፌ የሚወጡት ቃላት ሁሉ ጽድቅ ናቸው።

የተጣመመ ወይም የተወላገደ ነገር አይገኝባቸውም።

 9 ጥልቅ ግንዛቤ ላለው፣ ሁሉም ቀና ናቸው፤

እውቀት ላላቸውም ትክክል ናቸው።

10 ከብር ይልቅ ተግሣጼን፣

ጥራት ካለውም ወርቅ ይልቅ እውቀትን ተቀበሉ፤+

11 ጥበብ ከዛጎል* ትበልጣለችና፤

ተፈላጊ የሆኑ ሌሎች ነገሮች ሁሉ ከእሷ ጋር ሊወዳደሩ አይችሉም።

12 እኔ ጥበብ፣ ከብልሃት ጋር አብሬ እኖራለሁ፤

እውቀትና የማመዛዘን ችሎታ አግኝቻለሁ።+

13 ይሖዋን መፍራት ማለት ክፉ ነገርን መጥላት ነው።+

ትዕቢትን፣ ኩራትን፣+ ክፉ መንገድንና ጠማማ ንግግርን እጠላለሁ።+

14 ጥሩ ምክር መስጠት እችላለሁ፤ ማስተዋል የታከለበት ጥበብም አለኝ፤+

ማስተዋልና+ ኃይል+ የእኔ ናቸው።

15 ነገሥታት የሚገዙት በእኔ ነው፤

ከፍተኛ ባለሥልጣናትም የጽድቅ ድንጋጌ የሚያወጡት በእኔ ነው።+

16 መኳንንት የሚገዙት በእኔ ነው፤

ታላላቅ ሰዎችም በጽድቅ የሚፈርዱት በእኔ ነው።

17 የሚወዱኝን እወዳቸዋለሁ፤

የሚፈልጉኝም ያገኙኛል።+

18 ሀብትና ክብር፣

ዘላቂ ብልጽግናና* ጽድቅ በእኔ ዘንድ አሉ።

19 ፍሬዬ ከወርቅ፣ አልፎ ተርፎም ከጠራ ወርቅ ይሻላል፤

ከእኔ የምታገኙት ስጦታም ጥራት ካለው ብር ይበልጣል።+

20 በጽድቅ መንገድ፣

በፍትሕ ጎዳና መካከል እጓዛለሁ፤

21 ለሚወዱኝ ውድ የሆኑ ነገሮችን አወርሳለሁ፤

ግምጃ ቤቶቻቸውንም እሞላለሁ።

22 ይሖዋ የመንገዱ መጀመሪያ አድርጎ ፈጠረኝ፤+

ከብዙ ዘመን በፊት ካከናወናቸው ሥራዎች ቀዳሚው አደረገኝ።+

23 ከጥንት፣* ከመጀመሪያው አንስቶ፣

ምድርም ከመፈጠሯ አስቀድሞ+ ከፍ ያለ ቦታ ተሰጠኝ።+

24 ጥልቅ ውኃዎች ባልነበሩበት ጊዜ፣+

ምንጮች ከመፍለቃቸው በፊት ተወለድኩ።*

25 ተራሮች ገና ሳይመሠረቱ፣

ከኮረብቶች በፊት ተወለድኩ፤

26 ምድርንም ሆነ ሜዳዎቹን እንዲሁም

የመጀመሪያዎቹን የአፈር ጓሎች ከመሥራቱ በፊት ተወለድኩ።

27 ሰማያትን ባዘጋጀ ጊዜ+ በዚያ ነበርኩ፤

በውኃዎች ላይ የአድማስን ምልክት* ባደረገ ጊዜ፣+

28 ደመናትን በላይ ባዘጋጀ* ጊዜ፣

የጥልቅ ውኃ ምንጮችን በመሠረተ ጊዜ፣

29 የባሕሩ ውኃ

ከትእዛዙ አልፎ እንዳይሄድ በደነገገ ጊዜ፣+

የምድርን መሠረቶች ባቆመ* ጊዜ፣

30 በዚያን ወቅት የተዋጣለት ሠራተኛ ሆኜ ከጎኑ ነበርኩ።+

በየዕለቱ በእኔ የተነሳ ልዩ ደስታ ይሰማው ነበር፤+

እኔም በፊቱ ሁልጊዜ ሐሴት አደርግ ነበር፤+

31 እሱ በፈጠረው፣ ሰው በሚኖርበት ምድር ሐሴት አደረግኩ፤

በተለይ ደግሞ በሰው ልጆች እጅግ እደሰት ነበር።

32 እንግዲህ ልጆቼ ሆይ፣ አዳምጡኝ፤

አዎ፣ መንገዴን የሚጠብቁ ደስተኞች ናቸው።

33 ተግሣጽን ስሙ፤+ ጥበበኞችም ሁኑ፤

ፈጽሞም ቸል አትበሉት።

34 በየዕለቱ በማለዳ በራፌ ላይ መጥቶ፣*

በበሬ መቃን አጠገብ ቆሞ በመጠባበቅ

የሚያዳምጠኝ ሰው ደስተኛ ነው፤

35 እኔን የሚያገኝ ሕይወትን ያገኛልና፤+

በይሖዋም ዘንድ ሞገስ ያገኛል።

36 እኔን ችላ የሚል ግን ራሱን* ይጎዳል፤

የሚጠሉኝ ሁሉ ሞትን ይወዳሉ።”+

9 እውነተኛ ጥበብ ቤቷን ሠራች፤

ሰባቱን ምሰሶዎቿንም ጠርባ አዘጋጀች።

 2 ሥጋዋን በሚገባ አዘጋጀች፤*

የወይን ጠጇንም ደባለቀች፤

ደግሞም ገበታዋን አሰናዳች።

 3 ከከተማዋ በላይ ባሉ ከፍታ ቦታዎች ላይ ሆነው

እንዲህ ብለው እንዲጣሩ ሴት አገልጋዮቿን ላከች፦+

 4 “ተሞክሮ የሌለው ሁሉ ወደዚህ ይምጣ።”

ማስተዋል* ለጎደለው እንዲህ ትላለች፦

 5 “ኑ፣ ያዘጋጀሁትን ምግብ ብሉ፤

የደባለቅኩትንም የወይን ጠጅ ጠጡ።

 6 አላዋቂነታችሁን ተዉ፤* በሕይወትም ኑሩ፤+

በማስተዋል መንገድ ወደ ፊት ሂዱ።”+

 7 ፌዘኛን የሚያርም በራሱ ላይ ውርደት ያመጣል፤+

ክፉን ሰው የሚወቅስም ሁሉ ጉዳት ይደርስበታል።

 8 ፌዘኛን አትውቀስ፤ አለዚያ ይጠላሃል።+

ጥበበኛን ሰው ውቀሰው፤ እሱም ይወድሃል።+

 9 ጥበበኛን ሰው አስተምረው፤ ይበልጥ ጥበበኛ ይሆናል።+

ጻድቅን ሰው አስተምረው፤ ተጨማሪ እውቀት ያገኛል።

10 የጥበብ መጀመሪያ ይሖዋን መፍራት ነው፤+

እጅግ ቅዱስ ስለሆነው አምላክ ማወቅም+ ማስተዋል ነው።

11 በእኔ ምክንያት ዘመንህ ይረዝማል፤+

በሕይወትህም ላይ ዕድሜ ይጨመርልሃል።

12 ጥበበኛ ብትሆን፣ ጥበበኛነትህ የሚጠቅመው ራስህን ነው፤

ፌዘኛ ብትሆን ግን መዘዙን የምትቀበለው አንተው ነህ።

13 ማስተዋል የጎደላት ሴት ጯኺ ናት።+

እሷ ጨርሶ ማመዛዘን አትችልም፤ ደግሞም አንዳች ነገር አታውቅም።

14 በከተማዋ ከፍ ያሉ ቦታዎች ላይ፣

በቤቷ ደጃፍ ወንበር ላይ ትቀመጣለች፤+

15 በጎዳናው የሚያልፉትን፣

ቀጥ ብለው በመንገዳቸው የሚሄዱትን ትጣራለች፦

16 “ተሞክሮ የሌለው ሁሉ ወደዚህ ይምጣ።”

ማስተዋል* ለጎደላቸው ሁሉ እንዲህ ትላለች፦+

17 “የተሰረቀ ውኃ ይጣፍጣል፤

ተደብቀው የበሉት ምግብም ይጥማል።”+

18 እሱ ግን በሞት የተረቱት በዚያ እንዳሉ፣

እንግዶቿም በመቃብር* ጥልቅ ውስጥ እንደሚገኙ አያውቅም።+

10 የሰለሞን ምሳሌዎች።+

ጥበበኛ ልጅ አባቱን ደስ ያሰኛል፤+

ሞኝ ልጅ ግን እናቱን ያሳዝናል።

 2 በክፋት የተገኘ ሀብት ምንም ፋይዳ የለውም፤

ጽድቅ ግን ከሞት ይታደጋል።+

 3 ይሖዋ ጻድቅ ሰው እንዲራብ* አያደርግም፤+

የክፉዎችን ምኞት ግን ያጨናግፋል።

 4 ሥራ የፈቱ እጆች ያደኸያሉ፤+

ትጉ እጆች ግን ብልጽግና ያስገኛሉ።+

 5 ጥልቅ ማስተዋል ያለው ልጅ እህሉን በበጋ ይሰበስባል፤

አሳፋሪ ልጅ ግን በመከር ወቅት ለጥ ብሎ ይተኛል።+

 6 በረከት በጻድቅ ራስ ላይ ነው፤+

የክፉዎች አፍ ግን የዓመፅ ዕቅዳቸውን ይሰውራል።

 7 የጻድቅ መታሰቢያ* በረከት ያስገኛል፤+

የክፉዎች ስም ግን ይጠፋል።*+

 8 ጥበበኛ ልብ ያለው ሰው መመሪያዎችን* ይቀበላል፤+

በሞኝነት የሚናገር ሰው ግን ጥፋት ይደርስበታል።+

 9 ንጹሕ አቋሙን* ጠብቆ የሚሄድ ያለስጋት ይመላለሳል፤+

መንገዱን ጠማማ የሚያደርግ ግን ይጋለጣል።+

10 በተንኮል የሚጣቀስ ሐዘን ያመጣል፤+

በሞኝነት የሚናገር ሰውም ጥፋት ይደርስበታል።+

11 የጻድቅ አፍ የሕይወት ምንጭ ነው፤+

የክፉዎች አፍ ግን የዓመፅ ዕቅዳቸውን ይሰውራል።+

12 ጥላቻ ጭቅጭቅ ያስነሳል፤

ፍቅር ግን በደልን ሁሉ ይሸፍናል።+

13 አስተዋይ በሆነ ሰው ከንፈር ጥበብ ትገኛለች፤+

በትር ግን ማስተዋል* ለጎደለው ሰው ጀርባ ነው።+

14 ጥበበኞች እውቀትን እንደ ውድ ሀብት ያከማቻሉ፤+

የሞኝ ሰው አፍ ግን ጥፋት ይጋብዛል።+

15 የባለጸጋ ሀብት* የተመሸገ ከተማው ነው።

ድሆችን የሚያጠፋቸው ድህነታቸው ነው።+

16 የጻድቅ ሰው ሥራ ወደ ሕይወት ይመራል፤

የክፉ ሰው ፍሬ ግን ወደ ኃጢአት ይመራል።+

17 ተግሣጽን የሚቀበል ለሌሎች የሕይወት መንገድ ይሆናል፤*

ወቀሳን ችላ የሚል ግን ሌሎች መንገድ እንዲስቱ ያደርጋል።

18 ጥላቻውን የሚሸፋፍን ሰው ሐሰት ይናገራል፤+

ተንኮል ያዘለ ወሬ* የሚያስፋፋ ሰውም ሞኝ ነው።

19 ከቃላት ብዛት ስህተት አይታጣም፤+

ከንፈሩን የሚገታ ግን ልባም ሰው ነው።+

20 የጻድቅ አንደበት ጥራት ያለው ብር ነው፤+

የክፉ ሰው ልብ ግን እርባና የለውም።

21 የጻድቅ ከንፈሮች ብዙዎችን ይመግባሉ፤*+

ሞኞች ግን ማስተዋል ስለሚጎድላቸው ይሞታሉ።+

22 የይሖዋ በረከት ባለጸጋ ታደርጋለች፤+

እሱም ከበረከቱ ጋር ሥቃይን* አይጨምርም።

23 አሳፋሪ ምግባር መፈጸም ለሞኝ ሰው እንደ ጨዋታ ነው፤

ጥልቅ ግንዛቤ ያለው ሰው ግን ጥበበኛ ነው።+

24 ክፉ ሰው የፈራው ነገር ይደርስበታል፤

ጻድቅ ግን የተመኘውን ያገኛል።+

25 አውሎ ነፋስ ሲያልፍ ክፉ ሰው ተጠርጎ ይወሰዳል፤+

ጻድቅ ግን ለዘላለም እንደሚኖር መሠረት ነው።+

26 ኮምጣጤ ጥርስን፣ ጭስም ዓይንን እንደሚጎዳ፣

ሰነፍም ለሚልከው ሰው* እንዲሁ ነው።

27 ይሖዋን መፍራት ዕድሜን ያስረዝማል፤+

የክፉዎች ዕድሜ ግን በአጭሩ ይቀጫል።+

28 የጻድቃን ተስፋ ደስታ ያስገኛል፤+

የክፉዎች ተስፋ ግን መና ይቀራል።+

29 የይሖዋ መንገድ፣ ያለነቀፋ ለሚመላለስ ሰው መሸሸጊያ ነው፤+

ለክፉ አድራጊዎች ግን መጥፊያቸው ነው።+

30 ጻድቅ ሰው ምንም ነገር አይጥለውም፤+

ክፉዎች ግን በምድር ላይ መኖራቸውን አይቀጥሉም።+

31 የጻድቅ አፍ ጥበብን ያፈልቃል፤*

ጠማማ ምላስ ግን ትቆረጣለች።

32 የጻድቅ ሰው ከንፈሮች ደስ የሚያሰኘው ነገር ምን እንደሆነ ያውቃሉ፤

የክፉዎች አፍ ግን ጠማማ ነው።

11 አባይ* ሚዛን በይሖዋ ዘንድ አስጸያፊ ነው፤

ትክክለኛ መለኪያ* ግን ደስ ያሰኘዋል።+

 2 እብሪት ከመጣ ውርደት ይከተላል፤+

ልካቸውን በሚያውቁ ዘንድ ግን ጥበብ ትገኛለች።+

 3 ቅኖችን ንጹሕ አቋማቸው* ይመራቸዋል፤+

ከዳተኞችን ግን ተንኮላቸው ያጠፋቸዋል።+

 4 በቁጣ ቀን ሀብት ፋይዳ አይኖረውም፤*+

ጽድቅ ግን ከሞት ይታደጋል።+

 5 ነቀፋ የሌለበት ሰው የሚሠራው ጽድቅ መንገዱን ቀና ያደርግለታል፤

ክፉ ሰው ግን በገዛ ክፋቱ ይወድቃል።+

 6 ቅኖችን ጽድቃቸው ያድናቸዋል፤+

ከዳተኞች ግን በገዛ ምኞታቸው ይጠመዳሉ።+

 7 ክፉ ሰው ሲሞት ተስፋው መና ይቀራል፤

በኃይሉ ተመክቶ ተስፋ የሚያደርገው ነገርም ይጠፋል።+

 8 ጻድቅ ከመከራ ይድናል፤

ክፉ ሰው ደግሞ በእሱ ቦታ ይተካል።+

 9 ከሃዲ ሰው* በአፉ ባልንጀራውን ያጠፋል፤

ጻድቃን ግን በእውቀት ይድናሉ።+

10 በጻድቃን ጥሩነት ከተማ ሐሴት ታደርጋለች፤

ክፉዎች ሲጠፉም እልልታ ይሆናል።+

11 በቅኖች በረከት ከተማ ከፍ ከፍ ትላለች፤+

የክፉዎች አፍ ግን ያፈራርሳታል።+

12 ማስተዋል* የጎደለው ሰው ባልንጀራውን ይንቃል፤*

ጥልቅ ግንዛቤ ያለው ሰው ግን ዝም ይላል።+

13 ስም የሚያጠፋ ሰው እየዞረ የሌሎችን ሚስጥር ይገልጣል፤+

እምነት የሚጣልበት ሰው* ግን ሚስጥር ይጠብቃል።*

14 ጥበብ ያለበት አመራር ሲጓደል ሕዝብ ይጎዳል፤

ብዙ አማካሪዎች ባሉበት ግን ስኬት* ይገኛል።+

15 የማያውቀው ሰው ለወሰደው ብድር ዋስ የሚሆን* ጉዳት ላይ መውደቁ አይቀርም፤+

እጅ በመምታት* ቃል ከመግባት የሚቆጠብ* ግን ምንም አይደርስበትም።

16 ሞገስ ያላት* ሴት ክብር ታገኛለች፤+

ጨካኞች ግን ሀብት ያካብታሉ።

17 ደግ ሰው ራሱን ይጠቅማል፤*+

ጨካኝ ሰው ግን በራሱ ላይ መከራ* ያመጣል።+

18 ክፉ ሰው የሚያገኘው ደሞዝ እርባና የለውም፤+

ጽድቅን የሚዘራ ግን እውነተኛ ብድራት ያገኛል።+

19 ለጽድቅ ጽኑ አቋም ያለው ሰው ሕይወት የማግኘት ተስፋ አለው፤+

ክፋትን የሚያሳድድ ግን ለሞት መዳረጉ አይቀርም።

20 ይሖዋ ጠማማ ልብ ያላቸውን ሰዎች ይጸየፋል፤+

ነቀፋ በሌለበት ጎዳና የሚመላለሱ ግን ደስ ያሰኙታል።+

21 ይህን አትጠራጠር፦ ክፉ ሰው ከቅጣት አያመልጥም፤+

የጻድቃን ልጆች ግን ይድናሉ።

22 ማስተዋልን የምትንቅ ቆንጆ ሴት፣

በአሳማ አፍንጫ ላይ እንዳለ የወርቅ ቀለበት ናት።

23 የጻድቅ ምኞት መልካም ነገር ያስገኛል፤+

የክፉ ሰው ተስፋ ግን ወደ ቁጣ ይመራል።

24 አንዱ በልግስና ይሰጣል፤* ሆኖም ተጨማሪ ያገኛል፤+

ሌላው ደግሞ ለመስጠት ይሰስታል፤ ነገር ግን ለድህነት ይዳረጋል።+

25 ለጋስ ሰው* ይበለጽጋል፤*+

ሌሎችን የሚያረካም* እሱ ራሱ ይረካል።+

26 እህል ለመሸጥ ፈቃደኛ ያልሆነውን ሕዝቡ ይረግመዋል፤

የሚሸጠውን ግን ይባርከዋል።

27 መልካም ነገር ለማድረግ የሚተጋ ሞገስ ለማግኘት ይጥራል፤+

መጥፎ ነገር ለማድረግ የሚፈልግ ግን ክፋቱ በራሱ ላይ እንደሚመጣ የተረጋገጠ ነው።+

28 በሀብቱ የሚታመን ሰው ይወድቃል፤+

ጻድቅ ግን እንዳማረ ቅጠል ይለመልማል።+

29 ቤተሰቡ ላይ ችግር* የሚያመጣ ሰው ሁሉ ነፋስን ይወርሳል፤+

ሞኝ ሰውም ጥበበኛ ልብ ላለው ሰው አገልጋይ ይሆናል።

30 የጻድቅ ፍሬ የሕይወት ዛፍ ነው፤+

ነፍሳትንም* የሚማርክ ጥበበኛ ነው።+

31 በእርግጥ ጻድቅ በምድር ላይ የሚገባውን ብድራት የሚቀበል ከሆነ

ክፉውና ኃጢአተኛው የሚቀበሉት ብድራትማ ምንኛ የከፋ ይሆን!+

12 ተግሣጽን የሚወድ እውቀትን ይወዳል፤+

ወቀሳን የሚጠላ ግን የማመዛዘን ችሎታ* ይጎድለዋል።+

 2 ጥሩ ሰው የይሖዋን ሞገስ ያገኛል፤

ክፋት የሚያሴርን ሰው ግን እሱ ይፈርድበታል።+

 3 በክፋት ጸንቶ መቆም የሚችል ሰው የለም፤+

ጻድቅ ግን ፈጽሞ አይነቀልም።

 4 ጥሩ ሚስት ለባሏ ዘውድ ናት፤+

አሳፋሪ* ሚስት ግን አጥንቱ ውስጥ እንዳለ ንቅዘት ናት።+

 5 የጻድቃን ሐሳብ ፍትሐዊ ነው፤

የክፉዎች ምክር ግን አሳሳች ነው።

 6 የክፉዎች ቃል ገዳይ ወጥመድ ነው፤*+

የቅኖች አፍ ግን ይታደጋቸዋል።+

 7 ክፉዎች ሲገለበጡ ደብዛቸው ይጠፋል፤

የጻድቃን ቤት ግን ጸንቶ ይኖራል።+

 8 ሰው አስተዋይ በሆነ አንደበቱ ይመሰገናል፤+

ልቡ ጠማማ የሆነ ግን ይናቃል።+

 9 የሚበላው* ሳይኖረው ራሱን ከፍ ከፍ ከሚያደርግ ሰው ይልቅ

አገልጋይ ኖሮት ራሱን ዝቅ አድርጎ የሚኖር ሰው ይሻላል።+

10 ጻድቅ የቤት እንስሳቱን* ይንከባከባል፤+

ክፉዎች ግን ርኅራኄያቸው እንኳ ጭካኔ ነው።

11 መሬቱን የሚያርስ ሰው የተትረፈረፈ ምግብ ያገኛል፤+

ከንቱ ነገሮችን የሚያሳድድ ግን ማስተዋል* ይጎድለዋል።

12 ክፉ ሰው፣ ሌሎች መጥፎ ሰዎች ባጠመዱት ነገር ይቀናል፤

የጻድቃን ሥር ግን ፍሬ ያፈራል።

13 መጥፎ ሰው በክፉ ንግግሩ ይጠመዳል፤+

ጻድቅ ግን ከመከራ ያመልጣል።

14 ሰው ከአፉ ፍሬ መልካም ነገር ይጠግባል፤+

የእጁ ሥራም ብድራት ይከፍለዋል።

15 የሞኝ መንገድ በራሱ ዓይን ትክክል ነው፤+

ጥበበኛ ግን ምክር ይቀበላል።+

16 ሞኝ ሰው ቁጣውን ወዲያውኑ* ይገልጻል፤+

ብልህ ሰው ግን ስድብን ችላ ብሎ ያልፋል።*

17 ታማኝ ምሥክር እውነቱን* ይናገራል፤

ውሸታም ምሥክር ግን ያታልላል።

18 ሳይታሰብበት የሚነገር ቃል እንደ ሰይፍ ይወጋል፤

የጥበበኞች ምላስ ግን ፈውስ ነው።+

19 እውነት የሚናገሩ ከንፈሮች ለዘላለም ጸንተው ይኖራሉ፤+

ሐሰተኛ ምላስ ግን የሚቆየው ለቅጽበት ብቻ ነው።+

20 ተንኮል በሚሸርቡ ሰዎች ልብ ውስጥ ማታለያ አለ፤

ሰላምን የሚያራምዱ* ግን ደስተኞች ናቸው።+

21 ጻድቅ ምንም ዓይነት ጉዳት አያገኘውም፤+

የክፉዎች ሕይወት ግን በመከራ የተሞላ ይሆናል።+

22 ይሖዋ ውሸታም ከንፈሮችን ይጸየፋል፤+

በታማኝነት የሚመላለሱ ግን ደስ ያሰኙታል።

23 ብልህ ሰው እውቀቱን ይሰውራል፤

የሞኝ ልብ ግን ሞኝነቱን ይዘከዝካል።+

24 የትጉ ሰዎች እጅ ገዢ ትሆናለች፤+

ሥራ ፈት እጆች ግን ለባርነት ይዳረጋሉ።+

25 በሰው ልብ ውስጥ ያለ ጭንቀት ልቡ እንዲዝል ያደርገዋል፤*+

መልካም ቃል ግን ደስ ያሰኘዋል።+

26 ጻድቅ የግጦሽ መሬቱን በሚገባ ይቃኛል፤

የክፉዎች መንገድ ግን እንዲባዝኑ ያደርጋቸዋል።

27 ሰነፍ ሰው አደኑን አሳድዶ አይዝም፤+

ትጋት ግን የሰው ውድ ሀብት ነው።

28 የጽድቅ ጎዳና ወደ ሕይወት ይመራል፤+

በጎዳናው ላይ ሞት የለም።

13 ጥበበኛ ልጅ የአባቱን ተግሣጽ ይቀበላል፤+

ፌዘኛ ግን ተግሣጽን* አይሰማም።+

 2 ሰው ከአፉ ፍሬ መልካም ነገር ይበላል፤+

ከዳተኞች* ግን ዓመፅን ይመኛሉ።

 3 አፉን የሚጠብቅ ሕይወቱን ይጠብቃል።*+

አፉን የሚከፍት ግን ይጠፋል።+

 4 ሰነፍ ሰው ይመኛል፤ ነገር ግን ምንም አያገኝም፤*+

ትጉ ሰው* ግን በሚገባ ይጠግባል።*+

 5 ጻድቅ ውሸትን ይጠላል፤+

የክፉ ሰው ድርጊት ግን ኀፍረትና ውርደት ያመጣበታል።

 6 በመንገዱ ነቀፋ የሌለበትን ሰው ጽድቅ ትጠብቀዋለች፤+

ክፋት ግን ኃጢአተኛውን ትጥለዋለች።

 7 ምንም ሳይኖረው ባለጸጋ መስሎ ለመታየት የሚሞክር ሰው አለ፤+

ሌላው ደግሞ ብዙ ሀብት እያለው ድሃ መስሎ ይኖራል።

 8 የሰው ሀብት ለሕይወቱ* ቤዛ ነው፤+

ድሃ ግን ምንም ዓይነት ስጋት የለበትም።+

 9 የጻድቃን ብርሃን ደምቆ ይበራል፤*+

የክፉዎች መብራት ግን ይጠፋል።+

10 እብሪተኝነት ጠብ ከመፍጠር ውጭ የሚያመጣው ነገር የለም፤+

ምክር በሚሹ* ዘንድ ግን ጥበብ ትገኛለች።+

11 በፍጥነት የተገኘ ሀብት* ይመናመናል፤+

ጥቂት በጥቂት የሚያጠራቅም* ሰው ግን ሀብቱ ይጨምራል።

12 የዘገየ ተስፋ ልብን ያሳምማል፤+

የተሳካ ምኞት ግን የሕይወት ዛፍ ነው።+

13 መመሪያን የሚንቅ* ሁሉ ይቀጣል፤+

ትእዛዝን የሚያከብር ግን ብድራት ያገኛል።+

14 የጥበበኛ ሰው ትምህርት* የሕይወት ምንጭ ነው፤+

ሰውን ከሞት ወጥመድ እንዲያመልጥ ይረዳዋል።

15 ጥልቅ ማስተዋል ሞገስ ያስገኛል፤

የከዳተኞች መንገድ ግን አስቸጋሪ ነው።

16 ብልህ ሰው ተግባሩን በእውቀት ያከናውናል፤+

ሞኝ ሰው ግን የገዛ ራሱን ሞኝነት ይገልጣል።+

17 ክፉ መልእክተኛ ችግር ውስጥ ይወድቃል፤+

ታማኝ መልእክተኛ ግን ፈውስ ያመጣል።+

18 ተግሣጽን ችላ የሚል ሁሉ ይደኸያል፤ ይዋረዳልም፤

እርማትን የሚቀበል* ግን ይከበራል።+

19 ሰው* የተመኘው ነገር ሲፈጸም ደስ ይለዋል፤+

ሞኞች ግን ከክፋት መራቅን ይጸየፋሉ።+

20 ከጥበበኞች ጋር የሚሄድ ጥበበኛ ይሆናል፤+

ከሞኞች ጋር የሚገጥም ግን ጉዳት ይደርስበታል።+

21 ኃጢአተኞችን ጥፋት ያሳድዳቸዋል፤+

ጻድቃንን ግን ብልጽግና ይክሳቸዋል።+

22 ጥሩ ሰው ለልጅ ልጆቹ ውርስ ይተዋል፤

የኃጢአተኛ ሀብት ግን ለጻድቅ ይከማቻል።+

23 የድሃ እርሻ ብዙ እህል ያስገኛል፤

ሆኖም ከፍትሕ መጓደል የተነሳ ተጠራርጎ ይጠፋል።*

24 ልጁን በበትር ከመምታት* ወደኋላ የሚል ይጠላዋል፤+

የሚወደው ግን ተግቶ* ይገሥጸዋል።+

25 ጻድቅ ይበላል፤ የምግብ ፍላጎቱንም * ያረካል፤+

የክፉ ሰው ሆድ ግን ባዶ ነው።+

14 ጥበበኛ ሴት ቤቷን ትገነባለች፤+

ሞኝ ሴት ግን በገዛ እጇ ታፈርሰዋለች።

 2 አካሄዱ ቅን የሆነ ሰው ይሖዋን ይፈራል፤

መንገዱ መሠሪ* የሆነ ግን ይንቀዋል።

 3 በሞኝ ሰው አፍ የትዕቢት በትር አለ፤

የጥበበኞች ከንፈር ግን ትጠብቃቸዋለች።

 4 ከብት በሌለበት ግርግሙ ንጹሕ ይሆናል፤

የበሬ ጉልበት ግን ብዙ ምርት ያስገኛል።

 5 ሐቀኛ ምሥክር አይዋሽም፤

ሐሰተኛ ምሥክር ግን ባወራ ቁጥር ይዋሻል።+

 6 ፌዘኛ ጥበብን ይፈልጋል፤ ሆኖም አያገኛትም፤

አስተዋይ ሰው ግን እውቀትን በቀላሉ ያገኛል።+

 7 ከሞኝ ሰው ራቅ፤

ከከንፈሮቹ ምንም ዓይነት እውቀት አታገኝምና።+

 8 ብልህ ሰው የሚሄድበትን መንገድ በጥበብ ያስተውላል፤

ሞኞች ግን በቂልነታቸው ይታለላሉ።*+

 9 ሞኞች በደል ፈጽመው* ያፌዛሉ፤+

ቅኖች ግን እርቅ ለመፍጠር ፈቃደኞች ናቸው።*

10 ልብ የራሱን* ምሬት ያውቃል፤

ደስታውንም ሌላ ሰው ሊጋራው አይችልም።

11 የክፉዎች ቤት ይወድማል፤+

የቅኖች ድንኳን ግን ይበለጽጋል።

12 ለሰው ትክክለኛ መስሎ የሚታይ መንገድ አለ፤+

በመጨረሻ ግን ወደ ሞት ይመራል።+

13 አንድ ሰው እየሳቀ እንኳ ልቡ ሊያዝን ይችላል፤

ደስታም በሐዘን ሊቋጭ ይችላል።

14 በልቡ ጋጠወጥ የሆነ ሰው አካሄዱ የሚያስከትለውን መዘዝ ይቀበላል፤+

ጥሩ ሰው ግን የሥራውን ውጤት ያገኛል።+

15 ተላላ* ቃልን ሁሉ ያምናል፤

ብልህ ግን አካሄዱን አንድ በአንድ ያጤናል።+

16 ጥበበኛ ሰው ጠንቃቃ ነው፤ ከክፉም ይርቃል፤

ሞኝ ግን ደንታ ቢስ ነው፤* ደግሞም ከልክ በላይ በራሱ ይመካል።

17 ለቁጣ የሚቸኩል ሰው የሞኝነት ተግባር ይፈጽማል፤+

በጥሞና የሚያስብ ሰው* አይወደድም።

18 ተላሎች* ሞኝነትን ይወርሳሉ፤

ብልሆች ግን እውቀትን እንደ አክሊል ይጎናጸፋሉ።+

19 መጥፎ ሰዎች በጥሩ ሰዎች ፊት፣

ክፉዎችም በጻድቅ ደጃፍ ይሰግዳሉ።

20 ድሃ በባልንጀሮቹ ዘንድ እንኳ የተጠላ ነው፤+

የባለጸጋ ወዳጆች ግን ብዙ ናቸው።+

21 ባልንጀራውን የሚንቅ ኃጢአት ይሆንበታል፤

ለችግረኞች የሚራራ ግን ደስተኛ ነው።+

22 ተንኮል የሚሸርቡ ሰዎች መንገድ ይስቱ የለም?

መልካም ነገር ለመሥራት የሚያስቡ ሰዎች ግን ታማኝ ፍቅርንና ታማኝነትን ያተርፋሉ።+

23 በትጋት ያከናወኑት ነገር ሁሉ ጥቅም ያስገኛል፤

እንዲሁ ማውራት ግን ችግር ላይ ይጥላል።+

24 የጥበበኞች ዘውድ ሀብታቸው ነው፤

የሞኞች ቂልነት ግን ለከፋ ሞኝነት ይዳርጋል።+

25 እውነተኛ ምሥክር ሕይወትን* ይታደጋል፤

አታላይ ግን ባወራ ቁጥር ይዋሻል።

26 ይሖዋን የሚፈራ ሁሉ በማንኛውም ነገር በእሱ ይታመናል፤+

ልጆቹም መጠጊያ ያገኛሉ።+

27 ይሖዋን መፍራት የሕይወት ምንጭ ነው፤

ሰውን ከሞት ወጥመድ እንዲያመልጥ ይረዳዋል።

28 የሕዝብ ብዛት የንጉሥ ግርማ ነው፤+

ተገዢዎች የሌሉት ገዢ ግን ይጠፋል።

29 ቶሎ የማይቆጣ ሰው ትልቅ ማስተዋል አለው፤+

ትዕግሥት የሌለው ሰው ግን ሞኝነቱን ይገልጣል።+

30 የሰከነ ልብ ለሰውነት ሕይወት* ይሰጣል፤

ቅናት ግን አጥንትን ያነቅዛል።+

31 ችግረኛን የሚያጭበረብር ፈጣሪውን ይሰድባል፤+

ለድሃ የሚራራ ሁሉ ግን አምላክን ያከብራል።+

32 ክፉ ሰው በገዛ ክፋቱ ይወድቃል፤

ጻድቅ ግን ንጹሕ አቋሙ* መጠጊያ ያስገኝለታል።+

33 ጥበብ በአስተዋይ ልብ ውስጥ በጸጥታ ታርፋለች፤+

በሞኞች መካከል ግን ራሷን ትገልጣለች።

34 ጽድቅ አንድን ብሔር ከፍ ከፍ ታደርጋለች፤+

ኃጢአት ግን ሕዝብን ታዋርዳለች።

35 ንጉሥ አስተውሎ በሚሠራ አገልጋይ ደስ ይሰኛል፤+

አሳፋሪ ድርጊት በሚፈጽም አገልጋይ ላይ ግን ይቆጣል።+

15 የለዘበ* መልስ ቁጣን ያበርዳል፤+

ክፉ* ቃል ግን ቁጣን ያነሳሳል።+

 2 የጥበበኞች ምላስ እውቀትን በሚገባ ይጠቀማል፤+

የሞኞች አፍ ግን ሞኝነትን ይገልጣል።

 3 የይሖዋ ዓይኖች በሁሉም ቦታ ናቸው፤

ክፉዎችንም ሆነ ጥሩ ሰዎችን ይመለከታሉ።+

 4 የረጋ አንደበት* የሕይወት ዛፍ ነው፤+

ጠማማ ንግግር ግን ተስፋ ያስቆርጣል።*

 5 ሞኝ የአባቱን ተግሣጽ ይንቃል፤+

ብልህ ግን እርማትን ይቀበላል።+

 6 በጻድቅ ሰው ቤት ብዙ ሀብት አለ፤

የክፉ ሰው ምርት* ግን ችግር ያስከትልበታል።+

 7 የጥበበኞች ከንፈር እውቀትን ታስፋፋለች፤+

የሞኞች ልብ ግን እንዲህ አይደለም።+

 8 ይሖዋ የክፉዎችን መሥዋዕት ይጸየፋል፤+

የቅኖች ጸሎት ግን ደስ ያሰኘዋል።+

 9 ይሖዋ የክፉውን መንገድ ይጸየፋል፤+

ጽድቅን የሚከታተለውን ግን ይወደዋል።+

10 ከመንገድ የሚወጣ ሰው፣ ተግሣጽ መጥፎ* ነገር ይመስለዋል፤+

ወቀሳን የሚጠላ ሁሉ ግን ይሞታል።+

11 መቃብርና* የጥፋት ቦታ* በይሖዋ ፊት ወለል ብለው ይታያሉ።+

የሰዎች ልብማ በፊቱ ምንኛ የተገለጠ ነው!+

12 ፌዘኛ የሚያርመውን* ሰው አይወድም።+

ጥበበኞችን አያማክርም።+

13 ደስተኛ ልብ ፊትን ያፈካል፤

የልብ ሐዘን ግን መንፈስን ይደቁሳል።+

14 አስተዋይ ልብ እውቀትን ይፈልጋል፤+

የሞኞች አፍ ግን ቂልነትን ይመገባል።*+

15 ጎስቋላ ሰው ዘመኑ ሁሉ አስከፊ ነው፤+

ደስተኛ* ልብ ያለው ሰው ግን ሁልጊዜ ግብዣ ላይ ያለ ያህል ነው።+

16 ከጭንቀት* ጋር ከሚገኝ ብዙ ሀብት ይልቅ

ይሖዋን በመፍራት የሚገኝ ጥቂት ነገር ይሻላል።+

17 ጥላቻ ባለበት የሰባ* ፍሪዳ ከመብላት ይልቅ

ፍቅር ባለበት አትክልት መብላት ይሻላል።+

18 ግልፍተኛ ሰው ጭቅጭቅ ይፈጥራል፤+

ቶሎ የማይቆጣ ሰው ግን ጠብን ያበርዳል።+

19 የሰነፍ መንገድ እንደ እሾህ አጥር ነው፤+

የቅኖች መንገድ ግን እንደተስተካከለ አውራ ጎዳና ነው።+

20 ጥበበኛ ልጅ አባቱን ደስ ያሰኛል፤+

ሞኝ ግን እናቱን ያቃልላል።+

21 ማስተዋል* የጎደለው ሰው ሞኝነት ያስደስተዋል፤+

ጥልቅ ግንዛቤ ያለው ሰው ግን ቀጥተኛውን መንገድ ተከትሎ ይሄዳል።+

22 መመካከር* ከሌለ የታቀደው ነገር ሳይሳካ ይቀራል፤

በብዙ አማካሪዎች ግን ይሳካል።+

23 ሰው ትክክለኛውን መልስ በመስጠት* ሐሴት ያደርጋል፤+

በትክክለኛው ጊዜ የተነገረ ቃልም ምንኛ መልካም ነው!+

24 ጥልቅ ማስተዋል ያለው ሰው ወደ መቃብር* ከመውረድ ይድን ዘንድ

የሕይወት መንገድ ወደ ላይ ይመራዋል።+

25 ይሖዋ የትዕቢተኞችን ቤት ያፈርሳል፤+

የመበለቲቱን ወሰን ግን ያስከብራል።+

26 ይሖዋ የክፉውን ሰው ሐሳብ ይጸየፋል፤+

ያማረ ቃል ግን በፊቱ ንጹሕ ነው።+

27 በማጭበርበር የተገኘ ትርፍ የሚያጋብስ ሰው በቤተሰቡ ላይ ችግር* ያመጣል፤+

ጉቦን የሚጠላ ግን በሕይወት ይኖራል።+

28 የጻድቅ ልብ፣ መልስ ከመስጠቱ በፊት ያሰላስላል፤*+

የክፉዎች አፍ ግን መጥፎ ነገር ይዘከዝካል።

29 ይሖዋ ከክፉዎች እጅግ የራቀ ነው፤

የጻድቃንን ጸሎት ግን ይሰማል።+

30 ብሩህ ዓይን* ልብን ደስ ያሰኛል፤

መልካም ዜናም አጥንትን ያበረታል።*+

31 ሕይወት የሚያስገኝ ወቀሳን የሚሰማ፣

በጥበበኛ ሰዎች መካከል ይኖራል።+

32 ተግሣጽን ገሸሽ የሚያደርግ ሰው ሁሉ ሕይወቱን* ያቃልላል፤+

ወቀሳን የሚሰማ ሁሉ ግን ማስተዋል* ያገኛል።+

33 ይሖዋን መፍራት ጥበብን ያስተምራል፤+

ትሕትናም ክብርን ትቀድማለች።+

16 ሰው የልቡን ሐሳብ ያዘጋጃል፤*

የሚሰጠው መልስ* ግን ከይሖዋ ዘንድ ነው።+

 2 ሰው መንገዱ ሁሉ ትክክል* መስሎ ይታየዋል፤+

ይሖዋ ግን ውስጣዊ ዓላማን* ይመረምራል።+

 3 የምታደርገውን ሁሉ ለይሖዋ አደራ ስጥ፤*+

ዕቅድህም ሁሉ ይሳካል።

 4 ይሖዋ ማንኛውንም ነገር ያዘጋጀው ለራሱ ዓላማ ነው፤

ክፉውም ሰው እንኳ በመዓት ቀን እንዲጠፋ ያደርጋል።+

 5 ይሖዋ ኩሩ ልብ ያለውን ሁሉ ይጸየፋል።+

እንዲህ ያለው ሰው ሳይቀጣ እንደማይቀር እርግጠኛ ሁን።

 6 በታማኝ ፍቅርና በታማኝነት በደል ይሰረያል፤+

ሰውም ይሖዋን በመፍራት ከክፋት ይርቃል።+

 7 ይሖዋ በሰው አካሄድ ደስ በሚሰኝበት ጊዜ

ጠላቶቹ እንኳ ሳይቀሩ ከሰውየው ጋር ሰላም እንዲኖራቸው ያደርጋል።+

 8 አግባብ ባልሆነ መንገድ ከሚገኝ ብዙ ገቢ ይልቅ

በጽድቅ የሚገኝ ጥቂት ነገር ይሻላል።+

 9 ሰው በልቡ መንገዱን ያቅዳል፤

ይሖዋ ግን አካሄዱን ይመራለታል።+

10 የንጉሥ ከንፈር በመንፈስ ተመርቶ ውሳኔ* መስጠት ይገባዋል፤+

ፍትሕን ፈጽሞ ማዛባት የለበትም።+

11 ትክክለኛ መለኪያና ሚዛን ከይሖዋ ናቸው፤

በከረጢት ውስጥ ያሉት መለኪያዎች ሁሉ የእሱ ሥራ ናቸው።+

12 ክፉ ድርጊት በነገሥታት ዘንድ አስጸያፊ ነው፤+

ዙፋን የሚጸናው በጽድቅ ነውና።+

13 ነገሥታት የጽድቅ ንግግር ደስ ያሰኛቸዋል።

ሐቁን የሚናገር ሰው ይወዳሉ።+

14 የንጉሥ ቁጣ እንደ ሞት መልእክተኛ ነው፤+

ጥበበኛ ሰው ግን ቁጣውን ያበርደዋል።*+

15 የንጉሥ ፊት ሲፈካ ሰው በደስታ ይኖራል፤

ሞገሱም ዝናብ እንዳዘለ የበልግ ደመና ነው።+

16 ጥበብን ማግኘት ወርቅ ከማግኘት ምንኛ የተሻለ ነው!+

ማስተዋልን ማግኘትም ብር ከማግኘት ይመረጣል።+

17 ቅኖች ከክፋት ጎዳና ይርቃሉ።

መንገዱን የሚጠብቅ ሁሉ በሕይወት ይኖራል።*+

18 ኩራት ጥፋትን፣

የትዕቢት መንፈስም ውድቀትን ይቀድማል።+

19 የትዕቢተኞችን ምርኮ ከመካፈል ይልቅ

ከየዋሆች ጋር የትሕትና መንፈስ* ማሳየት ይሻላል።+

20 አንድን ነገር ጠለቅ ብሎ የሚያስተውል ሰው ስኬታማ ይሆናል፤*

በይሖዋ የሚታመንም ደስተኛ ነው።

21 ልቡ ጥበበኛ የሆነ ሰው አስተዋይ ይባላል፤+

በደግነት የሚናገርም* የማሳመን ችሎታ አለው።+

22 ጥልቅ ማስተዋል ለባለቤቱ የሕይወት ምንጭ ነው፤

ሞኞች ግን በገዛ ሞኝነታቸው ይቀጣሉ።

23 የጥበበኛ ሰው ልብ፣ አንደበቱ ጥልቅ ማስተዋል እንዲኖረው ያደርጋል፤+

ለንግግሩም የማሳመን ችሎታ ይጨምርለታል።

24 ደስ የሚያሰኝ ቃል እንደ ማር እንጀራ ነው፤

ለነፍስ* ጣፋጭ፣ ለአጥንትም ፈውስ ነው።+

25 ለሰው ትክክለኛ መስሎ የሚታይ መንገድ አለ፤

በመጨረሻ ግን ወደ ሞት ይመራል።+

26 ሠራተኛን የምግብ ፍላጎቱ* ተግቶ እንዲሠራ ያደርገዋል፤

ረሃቡ* እንዲህ እንዲያደርግ ያስገድደዋልና።+

27 የማይረባ ሰው ክፋትን ይምሳል፤+

ንግግሩ እንደሚለበልብ እሳት ነው።+

28 ነገረኛ ሰው* ጭቅጭቅ ያስነሳል፤+

ስም አጥፊም የልብ ጓደኛሞችን ይለያያል።+

29 ዓመፀኛ ሰው ባልንጀራውን ክፉ ነገር እንዲሠራ ያግባባዋል፤

ወደተሳሳተ መንገድም ይመራዋል።

30 በዓይኑ እየጠቀሰ ተንኮል ይሸርባል።

ከንፈሮቹን ነክሶ ሸር ይሠራል።

31 ሽበት በጽድቅ መንገድ ሲገኝ+

የውበት* ዘውድ ነው።+

32 ቶሎ የማይቆጣ ሰው+ ከኃያል ሰው፣

ስሜቱን የሚቆጣጠርም* ከተማን ድል ከሚያደርግ ሰው ይሻላል።+

33 ዕጣ ጭን ላይ ይጣላል፤+

ውሳኔውን በሙሉ የሚያስተላልፈው ግን ይሖዋ ነው።+

17 ጠብ እያለ ትልቅ ድግስ ከተደገሰበት* ቤት ይልቅ

ሰላም* ባለበት ደረቅ የዳቦ ቁራሽ መብላት ይሻላል።+

 2 ጥልቅ ማስተዋል ያለው አገልጋይ አሳፋሪ ድርጊት በሚፈጽም ልጅ ላይ ሥልጣን ይኖረዋል፤

ከወንድማማቾቹ እንደ አንዱ ውርስ ይካፈላል።

 3 ማቅለጫ ለብር፣ ምድጃ ለወርቅ ነው፤+

ልብን የሚመረምር ግን ይሖዋ ነው።+

 4 ክፉ ሰው ጎጂ የሆነን ንግግር በትኩረት ያዳምጣል፤

አታላይ ሰውም ተንኮለኛ የሆነን አንደበት ያዳምጣል።+

 5 በድሃ የሚያፌዝ ሁሉ ፈጣሪውን ይሳደባል፤+

በሌላው ሰው ላይ በደረሰው መከራ የሚደሰትም ሁሉ ከቅጣት አያመልጥም።+

 6 የልጅ ልጆች* የሽማግሌዎች ዘውድ ናቸው፤

አባቶችም * ለወንዶች ልጆቻቸው* ክብር ናቸው።

 7 ለሞኝ ሰው ቀና* ንግግር አይስማማውም።+

ለገዢ* ደግሞ ሐሰተኛ ንግግር ጨርሶ አይሆነውም!+

 8 ስጦታ ለባለቤቱ እንደከበረ ድንጋይ* ነው፤+

በሄደበት ሁሉ ስኬት ያስገኝለታል።+

 9 በደልን ይቅር የሚል* ሁሉ ፍቅርን ይሻል፤+

አንድን ጉዳይ ደጋግሞ የሚያወራ ግን የልብ ጓደኛሞችን ይለያያል።+

10 ሞኝን ሰው መቶ ጊዜ ከመግረፍ ይልቅ+

ማስተዋል ያለውን ሰው አንድ ጊዜ መገሠጽ የተሻለ ውጤት ያስገኛል።+

11 ክፉ ሰው የሚሻው ዓመፅን ብቻ ነው፤

ሆኖም እሱን እንዲቀጣ ጨካኝ መልእክተኛ ይላክበታል።+

12 የቂል ሥራ እየሠራ ካለ ሞኝ ሰው ጋር ከመገናኘት ይልቅ

ግልገሎቿን ካጣች ድብ ጋር መገናኘት ይሻላል።+

13 ማንኛውም ሰው ለመልካም ነገር ክፉ የሚመልስ ከሆነ

ክፉ ነገር ከቤቱ አይጠፋም።+

14 ጠብ መጫር ግድብን ከመሸንቆር* ተለይቶ አይታይም፤

ስለዚህ ጥል ከመነሳቱ በፊት ከአካባቢው ራቅ።+

15 ክፉውን ነፃ የሚያደርግ፣ በጻድቁም ላይ የሚፈርድ፣+

ሁለቱም በይሖዋ ዘንድ አስጸያፊ ናቸው።

16 ሞኝ ሰው ጥበብን የራሱ የሚያደርግበት ልብ* ከሌለው

ጥበብ የሚያገኝበት መንገድ ቢኖር ምን ይጠቅማል?+

17 እውነተኛ ወዳጅ ምንጊዜም አፍቃሪ ነው፤+

ደግሞም ለመከራ ቀን የተወለደ ወንድም ነው።+

18 ማስተዋል የጎደለው ሰው

በባልንጀራው ፊት እጅ በመጨበጥ ዋስ* ለመሆን ይስማማል።+

19 ጠብ የሚወድ ሁሉ በደልን ይወዳል።+

በሩን ወደ ላይ አስረዝሞ የሚሠራ ጥፋትን ይጋብዛል።+

20 ልቡ ጠማማ የሆነ አይሳካለትም፤*+

በምላሱም የሚያታልል ጥፋት ይደርስበታል።

21 የሞኝ ልጅ አባት ሐዘን ላይ ይወድቃል፤

የማመዛዘን ችሎታ የጎደለው ልጅ የወለደም ደስታ አይኖረውም።+

22 ደስተኛ ልብ ጥሩ መድኃኒት ነው፤*+

የተደቆሰ መንፈስ ግን ኃይል ያሟጥጣል።*+

23 ክፉ ሰው ፍትሕን ለማዛባት

በስውር* ጉቦ ይቀበላል።+

24 ጥልቅ ግንዛቤ ባለው ሰው ፊት ጥበብ ትገኛለች፤

የሞኝ ሰው ዓይን ግን እስከ ምድር ዳርቻ ይንከራተታል።+

25 ሞኝ ልጅ በአባቱ ላይ ሐዘን ያስከትላል፤

እናቱም እንድትመረር ያደርጋል።+

26 ጻድቁን መቅጣት* መልካም አይደለም።

የተከበሩ ሰዎችንም መግረፍ ትክክል አይደለም።

27 አዋቂ ሰው ንግግሩ ቁጥብ ነው፤+

ጥልቅ ግንዛቤ ያለው ሰውም የተረጋጋ ነው።*+

28 ሞኝ ሰው እንኳ ዝም ሲል እንደ ጥበበኛ ይቆጠራል፤

ከንፈሮቹንም የሚዘጋ ማስተዋል እንዳለው ተደርጎ ይታያል።

18 ራሱን የሚያገል ሰው ሁሉ የራስ ወዳድነት ምኞቱን ያሳድዳል፤

ጥበብንም* ሁሉ ይቃወማል።*

 2 ሞኝ ሰው ማስተዋል አያስደስተውም፤

ይልቁንም በልቡ ያለውን ሐሳብ ይገልጣል።+

 3 ክፉ ሰው ሲመጣ ንቀትም ይመጣል፤

ከውርደትም ጋር ኀፍረት ይመጣል።+

 4 ከሰው አፍ የሚወጣ ቃል ጥልቅ ውኃ ነው።+

የጥበብ ምንጭ የሚንዶለዶል ጅረት ነው።

 5 ለክፉ ሰው ማድላት፣

ጻድቁንም ፍትሕ መንፈግ+ መልካም አይደለም።+

 6 የሞኝ ሰው ንግግር ጠብ ያስነሳል፤+

አፉም ዱላ ይጋብዛል።+

 7 የሞኝ አንደበት መጥፊያው ነው፤+

ከንፈሮቹም ለሕይወቱ* ወጥመድ ናቸው።

 8 ስም አጥፊ የሚናገረው ቃል ጣፋጭ እንደሆነ ቁራሽ ምግብ ነው፤*+

በፍጥነት ተውጦ በቀጥታ ወደ ሆድ ይገባል።+

 9 በሥራው ታካች የሆነ ሰው ሁሉ፣

የአጥፊ ወንድም ነው።+

10 የይሖዋ ስም ጽኑ ግንብ ነው።+

ጻድቅ ወደዚያ በመሮጥ ጥበቃ ያገኛል።*+

11 የባለጸጋ ሰው ሀብት የተመሸገ ከተማው ነው፤

በሐሳቡም ጥበቃ እንደሚያስገኝ ግንብ አድርጎ ይመለከተዋል።+

12 ሰው ለውድቀት ከመዳረጉ በፊት ልቡ ይታበያል፤+

ትሕትና ግን ክብርን ትቀድማለች።+

13 እውነታውን ከመስማቱ በፊት መልስ የሚሰጥ ሰው፣

ሞኝነት ይሆንበታል፤ ውርደትም ይከናነባል።+

14 ጠንካራ መንፈስ ያለው ሰው ሕመሙን መቋቋም ይችላል፤+

የተደቆሰን መንፈስ* ግን ማን ሊቋቋም ይችላል?+

15 የአስተዋይ ሰው ልብ እውቀትን ያገኛል፤+

የጥበበኛም ጆሮ እውቀትን ለማግኘት ይጥራል።

16 ስጦታ ለሰጪው መንገዱን ይከፍትለታል፤+

በታላላቅ ሰዎችም ፊት መቅረብ ያስችለዋል።

17 ክሱን አስቀድሞ ያሰማ ትክክለኛ ይመስላል፤+

ይህም ሌላው ወገን መጥቶ እስኪመረምረው ድረስ ነው።+

18 ዕጣ መጣል ጭቅጭቅ እንዲያበቃ ያደርጋል፤+

ኃይለኛ ባላንጣዎችንም ይገላግላል።

19 የተበደለ ወንድም ከተመሸገች ከተማ ይበልጥ የማይበገር ነው፤+

እንደ ግንብ በሮች መቀርቀሪያም የጠነከረ ጠብ አለ።+

20 ሰው በአፉ ፍሬ ሆዱ ይሞላል፤+

ከንፈሩም በሚያስገኘው ምርት ይረካል።

21 አንደበት የሞትና የሕይወት ኃይል አላት፤+

ሊጠቀምባት የሚወድ ፍሬዋን ይበላል።+

22 ጥሩ ሚስት ያገኘ ጥሩ ነገር አግኝቷል፤+

የይሖዋንም ሞገስ* ያገኛል።+

23 ድሃ እየተለማመጠ ይናገራል፤

ሀብታም ግን በኃይለ ቃል ይመልሳል።

24 እርስ በርስ ከመጠፋፋት ወደኋላ የማይሉ ጓደኛሞች አሉ፤+

ነገር ግን ከወንድም ይበልጥ የሚቀርብ ጓደኛ አለ።+

19 ሞኝ ከመሆንና ውሸት ከመናገር

ድሃ ሆኖ ንጹሕ አቋምን* ጠብቆ መመላለስ ይሻላል።+

 2 እውቀት የሌለው ሰው* ጥሩ አይደለም፤+

ችኩል* ሰውም ኃጢአት ይሠራል።

 3 የሰውን መንገድ የሚያጣምምበት የገዛ ሞኝነቱ ነው፤

ልቡም በይሖዋ ላይ ይቆጣል።

 4 ሀብት ብዙ ወዳጆችን ይስባል፤

ድሃን ግን ጓደኛው እንኳ ይተወዋል።+

 5 ሐሰተኛ ምሥክር መቀጣቱ አይቀርም፤+

ባወራ ቁጥር የሚዋሽም ከቅጣት አያመልጥም።+

 6 ብዙዎች በተከበረ ሰው* ዘንድ ሞገስ ለማግኘት ይጥራሉ፤

ስጦታ ከሚሰጥ ሰው ጋር ደግሞ ሁሉም ይወዳጃል።

 7 ድሃን ወንድሞቹ ሁሉ ይጠሉታል፤+

ጓደኞቹማ ምን ያህል ይርቁት!+

እየተከታተለ ሊለማመጣቸው ይሞክራል፤ ምላሽ የሚሰጠው ግን የለም።

 8 ማስተዋል* የሚያገኝ ሰው ሁሉ ራሱን* ይወዳል።+

ጥልቅ ግንዛቤን እንደ ውድ ሀብት አድርጎ የሚመለከት ሁሉ ይሳካለታል።*+

 9 ሐሰተኛ ምሥክር መቀጣቱ አይቀርም፤

ባወራ ቁጥር የሚዋሽም ይጠፋል።+

10 ሞኝ ሰው ተንደላቆ መኖር አይገባውም፤

አገልጋይ መኳንንትን ቢገዛማ ምንኛ የከፋ ነው!+

11 ጥልቅ ማስተዋል ሰውን ቶሎ እንዳይቆጣ ያደርገዋል፤+

በደልንም መተዉ* ውበት ያጎናጽፈዋል።+

12 የንጉሥ ቁጣ እንደ አንበሳ* ግሳት ነው፤+

ሞገሱ ግን በሣር ላይ እንዳለ ጤዛ ነው።

13 ሞኝ ልጅ በአባቱ ላይ መከራ ያመጣል፤+

ጨቅጫቃ ሚስትም * ያለማቋረጥ እንደሚያንጠባጥብ ጣሪያ ናት።+

14 ቤትና ሀብት ከአባቶች ይወረሳል፤

ልባም ሚስት ግን የምትገኘው ከይሖዋ ነው።+

15 ስንፍና ከባድ እንቅልፍ ላይ ይጥላል፤

ታካች ሰውም ይራባል።*+

16 ትእዛዝን የሚጠብቅ ሕይወቱን* ይጠብቃል፤+

መንገዱን ቸል የሚል ይሞታል።+

17 ለችግረኛ ሞገስ የሚያሳይ ለይሖዋ ያበድራል፤+

ላደረገውም ነገር ብድራት* ይከፍለዋል።+

18 ገና ተስፋ ሳለ ልጅህን ገሥጽ፤+

ለእሱም ሞት ተጠያቂ አትሁን።*+

19 ግልፍተኛ ሰው ይቀጣል፤

ልታድነው ብትሞክር እንኳ በተደጋጋሚ እንዲህ ለማድረግ ትገደዳለህ።+

20 የኋላ ኋላ ጥበበኛ እንድትሆን

ምክርን ስማ፤ ተግሣጽንም ተቀበል።+

21 ሰው በልቡ ብዙ ነገር ያቅዳል፤

የሚፈጸመው ግን የይሖዋ ፈቃድ* ነው።+

22 የሰው ተወዳጅ ባሕርይ ታማኝ ፍቅሩ ነው፤+

ውሸታም ከመሆን ድሃ መሆን ይሻላል።

23 ይሖዋን መፍራት ወደ ሕይወት ይመራል፤+

እንዲህ የሚያደርግ ሰው ጥሩ እረፍት ያገኛል፤ ጉዳትም አይደርስበትም።+

24 ሰነፍ እጁን ወደ ሳህን ያጠልቃል፤

ሆኖም ወደ አፉ እንኳ መመለስ ይሳነዋል።+

25 ተሞክሮ የሌለው ብልህ+ እንዲሆን ፌዘኛን ምታው፤+

ተጨማሪ እውቀት እንዲያገኝም አስተዋይ የሆነን ሰው ውቀሰው።+

26 አባቱን የሚበድልና እናቱን የሚያባርር ልጅ

ኀፍረትና ውርደት ያመጣል።+

27 ልጄ ሆይ፣ ተግሣጽን መስማት ከተውክ

እውቀት ከሚገኝበት ቃል ትርቃለህ።

28 የማይረባ ምሥክር በፍትሕ ላይ ያፌዛል፤+

የክፉዎችም አፍ ክፋትን ይሰለቅጣል።+

29 ፌዘኞች ፍርድ ይጠብቃቸዋል፤+

ለሞኞች ጀርባ ደግሞ ዱላ ተዘጋጅቷል።+

20 የወይን ጠጅ ፌዘኛ፣+ የሚያሰክር መጠጥም ሥርዓት አልበኛ ያደርጋል፤+

በዚህ ምክንያት ከትክክለኛው መንገድ የሚወጣ ሁሉ ጥበበኛ አይደለም።+

 2 ንጉሥ የሚፈጥረው ሽብር* እንደ አንበሳ* ግሳት ነው፤+

የእሱን ቁጣ የሚያነሳሳ ሁሉ ሕይወቱን ለአደጋ ያጋልጣል።+

 3 ሰው ከጠብ መራቁ ያስከብረዋል፤+

ሞኝ የሆነ ሁሉ ግን ጥል ውስጥ ይዘፈቃል።+

 4 ሰነፍ ሰው በክረምት አያርስም፤

በመሆኑም በመከር ወራት ባዶውን ሲቀር ይለምናል።*+

 5 በሰው ልብ ውስጥ ያለ ሐሳብ* እንደ ጥልቅ ውኃ ነው፤

አስተዋይ ሰው ግን ቀድቶ ያወጣዋል።

 6 ብዙ ሰዎች ስለ ራሳቸው ታማኝ ፍቅር ያወራሉ፤

ይሁንና ታማኝ የሆነን ሰው ማን ሊያገኘው ይችላል?

 7 ጻድቅ ንጹሕ አቋሙን* ጠብቆ ይመላለሳል።+

ከእሱ በኋላ የሚመጡት ልጆቹ ደስተኞች ናቸው።+

 8 ንጉሥ ለመፍረድ በዙፋን ላይ ሲቀመጥ፣+

ክፋትን ሁሉ በዓይኖቹ ያበጥራል።+

 9 “ልቤን አንጽቻለሁ፤+

ከኃጢአቴም ነጽቻለሁ” ሊል የሚችል ማን ነው?+

10 አባይ ሚዛንና የሐሰት መለኪያ፣*

ሁለቱም በይሖዋ ፊት አስጸያፊ ናቸው።+

11 ሕፃን እንኳ ባሕርይው ንጹሕና ትክክል መሆኑ

በአድራጎቱ ይታወቃል።+

12 የሚሰማ ጆሮንና የሚያይ ዓይንን፣

ሁለቱንም የሠራው ይሖዋ ነው።+

13 እንቅልፍ አትውደድ፤ አለዚያ ድሃ ትሆናለህ።+

ዓይንህን ግለጥ፤ የተትረፈረፈ ምግብም ታገኛለህ።+

14 ዕቃ የሚገዛ ሰው “የማይረባ ነው፣ የማይረባ ነው!” ይላል፤

ከሄደ በኋላ ግን በራሱ ይኩራራል።+

15 ወርቅ አለ፤ ዛጎልም* ተትረፍርፏል፤

እውቀትን የሚናገሩ ከንፈሮች ግን ውድ ናቸው።+

16 አንድ ሰው ለማያውቀው ሰው ዋስ ከሆነ ልብሱን ውሰድበት፤+

ይህን ያደረገው ለባዕድ ሴት* ብሎ ከሆነ መያዣውን ውሰድ።+

17 ሰው በማጭበርበር ያገኘው ምግብ ያስደስተዋል፤

በኋላ ግን አፉን ኮረት ይሞላዋል።+

18 መመካከር* ሲኖር የታቀደው ነገር ይሳካል፤*+

ለውጊያም ስትወጣ ጥበብ ያለበት አመራር ተቀበል።+

19 ስም የሚያጠፋ ሰው እየዞረ የሌሎችን ሚስጥር ይገልጣል፤+

ማማት ከሚወድ ሰው* ጋር አትወዳጅ።

20 አባቱንና እናቱን የሚረግም ሁሉ

ጨለማ ሲሆን መብራቱ ይጠፋበታል።+

21 በመጀመሪያ በስግብግብነት የተገኘ ውርስ፣

የኋላ ኋላ በረከት አይሆንም።+

22 “ቆይ፣ ብድሬን ባልመልስ!” አትበል።+

ይሖዋን ተስፋ አድርግ፤+ እሱም ያድንሃል።+

23 አባይ ሚዛን* በይሖዋ ፊት አስጸያፊ ነው፤

ለማጭበርበር የሚያገለግሉ መለኪያዎችንም መጠቀም ጥሩ አይደለም።

24 ይሖዋ የሰውን አካሄድ ይመራል፤+

ሰው የገዛ መንገዱን* እንዴት ማስተዋል ይችላል?

25 ሰው ቸኩሎ “የተቀደሰ ነው!”+ ቢልና

ከተሳለ በኋላ ስእለቱን መልሶ ማጤን ቢጀምር ወጥመድ ይሆንበታል።+

26 ጥበበኛ ንጉሥ ክፉ ሰዎችን ያበጥራል፤+

የመውቂያ መንኮራኩርም* በላያቸው ያስኬዳል።+

27 የሰው እስትንፋስ የይሖዋ መብራት ነው፤

ውስጣዊ ማንነቱን በሚገባ ይመረምራል።

28 ታማኝ ፍቅርና ታማኝነት ንጉሥን ይጠብቃሉ፤+

በታማኝ ፍቅርም ዙፋኑን ያጸናል።+

29 የወጣቶች ክብር ጉልበታቸው ነው፤+

የአረጋውያንም ግርማ ሽበታቸው ነው።+

30 ሰንበርና ቁስል ክፋትን ያስወግዳል፤*+

ግርፋትም የአንድን ሰው ውስጣዊ ማንነት ያጠራል።

21 የንጉሥ ልብ በይሖዋ እጅ እንዳለ ጅረት ነው።+

እሱ ደስ ወዳሰኘው አቅጣጫ ሁሉ ይመራዋል።+

 2 ሰው መንገዱ ሁሉ ትክክል መስሎ ይታየዋል፤+

ይሖዋ ግን ልብን ይመረምራል።*+

 3 መሥዋዕት ከማቅረብ ይልቅ

ትክክልና ፍትሐዊ የሆነ ነገር ማድረግ ይሖዋን ይበልጥ ደስ ያሰኘዋል።+

 4 ትዕቢተኛ ዓይንና እብሪተኛ ልብ

የክፉዎች መብራት ናቸው፤ ደግሞም ኃጢአት ናቸው።+

 5 የትጉ ሰው ዕቅድ ለስኬት ያበቃዋል፤*+

ችኩሎች ሁሉ ግን ለድህነት ይዳረጋሉ።+

 6 በሐሰተኛ ምላስ የሚገኝ ውድ ሀብት

ወዲያው እንደሚጠፋ ጉም ነው፤ ገዳይ ወጥመድም ነው።*+

 7 ክፉዎች ፍትሕን ማስፈን ስለማይፈልጉ

የሚፈጽሙት ግፍ ጠራርጎ ይወስዳቸዋል።+

 8 የበደለኛ ሰው መንገድ ጠማማ ነው፤

የንጹሕ ሰው ሥራ ግን ቀና ነው።+

 9 ከጨቅጫቃ* ሚስት ጋር በአንድ ቤት ከመኖር

በጣሪያ ማዕዘን ላይ መኖር ይሻላል።+

10 ክፉ ሰው* መጥፎ ነገር ይመኛል፤+

ለባልንጀራው ሞገስ አያሳይም።+

11 ፌዘኛ ሲቀጣ ተሞክሮ የሌለው ሰው ይበልጥ ጥበበኛ ይሆናል፤

ጥበበኛ ሰው ጥልቅ ማስተዋል ሲያገኝም እውቀት ይቀስማል።*+

12 ጻድቅ የሆነው አምላክ፣ የክፉውን ቤት ልብ ብሎ ይመለከታል፤

ክፉዎችንም ይጠፉ ዘንድ ይገለብጣቸዋል።+

13 ችግረኛው የሚያሰማውን ጩኸት ላለመስማት ጆሮውን የሚደፍን ሁሉ፣

እሱ ራሱ ይጮኻል፤ መልስም አያገኝም።+

14 በድብቅ የተሰጠ ስጦታ ቁጣን ያበርዳል፤+

በስውር የተሰጠ ጉቦም* ኃይለኛ ቁጣ እንዲከስም ያደርጋል።

15 ጻድቅ ፍትሐዊ ነገር ማድረግ ያስደስተዋል፤+

ክፉ ድርጊት ለሚፈጽሙ ግን አስከፊ ነገር ነው።

16 ከማስተዋል መንገድ ወጥቶ የሚባዝን ሰው፣

በሞት ከተረቱት ጋር ያርፋል።+

17 ፈንጠዝያ* የሚወድ ሰው ይደኸያል፤+

የወይን ጠጅና ዘይት የሚወድ ባለጸጋ አይሆንም።

18 ክፉ ሰው ለጻድቅ ቤዛ ነው፤

ከዳተኛ የሆነ ሰውም በቅን ሰው ፋንታ ይወሰዳል።+

19 ጨቅጫቃና* ቁጡ ከሆነች ሚስት ጋር ከመኖር

በምድረ በዳ መኖር ይሻላል።+

20 ውድ ሀብትና ምርጥ ዘይት በጥበበኛ ሰው ቤት ይገኛል፤+

ሞኝ ሰው ግን ያለውን ያባክናል።*+

21 ጽድቅንና ታማኝ ፍቅርን የሚከታተል ሰው ሁሉ

ሕይወትን፣ ጽድቅንና ክብርን ያገኛል።+

22 ጥበበኛ ሰው የኃያላን ሰዎች ከተማ ላይ ይወጣል፤*

የሚታመኑበትንም ብርታት ያዳክማል።+

23 አፉንና ምላሱን የሚጠብቅ፣

ራሱን ከችግር ይጠብቃል።*+

24 በእብሪት የመሰለውን የሚያደርግ ሰው

እብሪተኛና ጉረኛ ይባላል።+

25 ሰነፍ ሰው ምኞቱ ይገድለዋል፤

እጆቹ መሥራት አይፈልጉምና።+

26 ቀኑን ሙሉ በስግብግብነት ሲመኝ ይውላል፤

ጻድቅ ግን ምንም ሳይሰስት ይሰጣል።+

27 የክፉ ሰው መሥዋዕት አስጸያፊ ነው።+

በክፉ ዓላማ ተነሳስቶ* ሲያቀርብማ ምንኛ የከፋ ይሆናል!

28 ውሸታም ምሥክር ይጠፋል፤+

በጥሞና የሚያዳምጥ ሰው ግን የምሥክርነት ቃሉ ተቀባይነት ያገኛል።*

29 ክፉ ሰው ኀፍረት የሚባል ነገር አያውቅም፤+

የቅን ሰው አካሄድ ግን አስተማማኝ ነው።*+

30 ይሖዋን የሚጻረር ጥበብ፣ ማስተዋልም ሆነ ምክር ከንቱ ነው።+

31 ፈረስ ለጦርነት ቀን ይዘጋጃል፤+

መዳን ግን ከይሖዋ ዘንድ ነው።+

22 መልካም ስም* ከብዙ ሀብት ይመረጣል፤+

መከበር* ከብርና ከወርቅ ይሻላል።

 2 ሀብታምንና ድሃን የሚያመሳስላቸው ነገር አለ፦*

ሁለቱንም የፈጠረው ይሖዋ ነው።+

 3 ብልህ ሰው አደጋ ሲያይ ይሸሸጋል፤

ተሞክሮ የሌለው ግን ዝም ብሎ ይሄዳል፤ መዘዙንም* ይቀበላል።

 4 ትሕትናና ይሖዋን መፍራት

ሀብት፣ ክብርና ሕይወት ያስገኛል።+

 5 በጠማማ ሰው መንገድ ላይ እሾህና ወጥመድ አለ፤

ለሕይወቱ* ትልቅ ግምት የሚሰጥ ሁሉ ግን ከእነዚህ ይርቃል።+

 6 ልጅን* ሊሄድበት በሚገባው መንገድ አሠልጥነው፤+

በሚያረጅበት ጊዜም እንኳ ከዚያ ፈቀቅ አይልም።+

 7 ሀብታም ድሃን ይገዛል፤

ተበዳሪም የአበዳሪው ባሪያ ነው።+

 8 ክፋትን የሚዘራ ሁሉ ጥፋትን ያጭዳል፤+

የቁጣውም በትር ያከትማል።+

 9 ለጋስ ሰው* ይባረካል፤

ምግቡን ለድሃ ያካፍላልና።+

10 ንቀት የሚያሳይን ሰው አባረው፤

ጭቅጭቅም ይቀራል፤

ጥልና* ስድብ ያከትማል።

11 ንጹሕ ልብ የሚወድና ንግግሩ ለዛ ያለው ሰው፣

የንጉሥ ወዳጅ ይሆናል።+

12 የይሖዋ ዓይኖች እውቀትን ይጠብቃሉ፤

የከዳተኛን ቃል ግን ይሽራል።+

13 ሰነፍ “ውጭ አንበሳ አለ!

አደባባይ ላይ እገደላለሁ!” ይላል።+

14 የጋጠወጥ* ሴት አፍ ጥልቅ ጉድጓድ ነው።+

ይሖዋ ያወገዘው ሰው እዚያ ውስጥ ይወድቃል።

15 ሞኝነት በልጅ* ልብ ውስጥ ታስሯል፤+

የተግሣጽ በትር ግን ከእሱ ያርቀዋል።+

16 ሀብቱን ለመጨመር ድሃውን የሚያጭበረብር+

እንዲሁም ለባለጸጋ ስጦታ የሚሰጥ ሰው

የኋላ ኋላ ይደኸያል።

17 እውቀቴን በሙሉ ልብ እንድትቀበል+

ጆሮህን አዘንብል፤ የጥበበኞችንም ቃል አዳምጥ፤+

18 ምንጊዜም ይህ ቃል ሙሉ በሙሉ በከንፈሮችህ ላይ እንዲሆን+

ቃሉን በውስጥህ መያዝህ መልካም ነውና።+

19 በይሖዋ እንድትተማመን፣

ዛሬ እውቀት እሰጥሃለሁ።

20 ከዚህ ቀደም ምክርና

እውቀት የያዙ ሐሳቦች አልጻፍኩልህም?

21 ይህን ያደረግኩት ለላከህ ትክክለኛ ወሬ ይዘህ እንድትመለስ፣

እውነት የሆነውንና እምነት የሚጣልበትን ቃል ላስተምርህ አይደለም?

22 ድሃውን ድሃ ስለሆነ ብቻ አትዝረፈው፤+

ችግረኛውንም በከተማው በር ላይ ግፍ አትፈጽምበት፤+

23 ይሖዋ ራሱ ይሟገትላቸዋልና፤+

የሚያጭበረብሯቸውንም ሰዎች ሕይወት ያጠፋል።*

24 ከግልፍተኛ ሰው ጋር አትግጠም፤

በቀላሉ ቱግ ከሚል ሰውም ጋር አትቀራረብ፤

25 አለዚያ መንገዱን ትማራለህ፤

ለራስህም* ወጥመድ ይሆናል።+

26 ዋስ ለመሆን እጅ እንደሚመቱ፣*

ለብድር ተያዥ እንደሚሆኑ ሰዎች አትሁን።+

27 የምትከፍለው ካጣህ

የተኛህበት አልጋ ከሥርህ ይወሰድብሃል!

28 አባቶችህ ያደረጉትን

የጥንቱን የወሰን ምልክት ከቦታው አታንቀሳቅስ።+

29 በሥራው የተካነን ሰው አይተሃል?

በነገሥታት ፊት ይቆማል፤+

ተራ በሆኑ ሰዎች ፊት አይቆምም።

23 ከንጉሥ ጋር ለመመገብ ስትቀመጥ፣

በፊትህ ያለውን በሚገባ አስተውል፤

 2 ለመብላት ብትቋምጥ* እንኳ

በጉሮሮህ ላይ ቢላ አስቀምጥ።*

 3 የእሱ ጣፋጭ ምግብ አያስጎምጅህ፤

ምግቡ አታላይ ነውና።

 4 ሀብት ለማግኘት አትልፋ።+

ይህን ትተህ በማስተዋል ተመላለስ።*

 5 ዓይንህን ስትጥልበት በዚያ አታገኘውም፤+

የንስር ዓይነት ክንፎች አውጥቶ ወደ ሰማይ ይበርራልና።+

 6 የስስታምን* ምግብ አትብላ፤

ጣፋጭ ምግቡ አያስጎምጅህ፤

 7 እሱ ሒሳብ እንደሚይዝ* ሰው ነውና።

“ብላ፣ ጠጣ” ይልሃል፤ የሚናገረው ግን ከልቡ አይደለም።*

 8 የበላሃትን ቁራሽ ምግብ ታስመልሳለህ፤

የተናገርካቸው የምስጋና ቃላትም ከንቱ ይሆናሉ።

 9 የምትናገራቸውን ጥበብ ያዘሉ ቃላት ስለሚንቅ+

ለሞኝ ሰው ምንም አትናገር።+

10 የጥንቱን የወሰን ምልክት ከቦታው አታንቀሳቅስ፤+

ደግሞም አባት የሌላቸውን ልጆች መሬት አትያዝ።

11 የሚከራከርላቸው* ብርቱ ነውና፤

እሱ ራሱ ከአንተ ጋር ይሟገትላቸዋል።+

12 ልብህን ለተግሣጽ፣

ጆሮህንም ለእውቀት ቃል ስጥ።

13 ልጅን* ከመገሠጽ ወደኋላ አትበል።+

በበትር ብትመታው አይሞትም።

14 ከመቃብር* ታድነው ዘንድ*

በበትር ምታው።

15 ልጄ ሆይ፣ ልብህ ጥበበኛ ቢሆን፣

የእኔ ልብ ሐሴት ያደርጋል።+

16 ከንፈሮችህ ትክክል የሆነውን ሲናገሩ

ውስጤ ደስ ይለዋል።*

17 ልብህ በኃጢአተኞች አይቅና፤+

ከዚህ ይልቅ ቀኑን ሙሉ ይሖዋን በመፍራት ተመላለስ፤+

18 እንዲህ ብታደርግ የወደፊት ሕይወትህ የተሳካ ይሆናል፤+

ተስፋህም ከንቱ አይሆንም።

19 ልጄ ሆይ፣ አዳምጥ፤ ጥበበኛም ሁን፤

ልብህንም በትክክለኛው መንገድ ምራ።

20 ብዙ የወይን ጠጅ እንደሚጠጡ፣+

ሥጋም ያለልክ እንደሚሰለቅጡ ሰዎች አትሁን፤*+

21 ሰካራምና ሆዳም ይደኸያሉና፤+

ድብታ ሰውን የተቦጫጨቀ ልብስ ያስለብሰዋል።

22 የወለደህን አባትህን ስማ፤

እናትህንም ስላረጀች አትናቃት።+

23 እውነትን ግዛ፤* ፈጽሞም አትሽጣት፤+

ጥበብን፣ ተግሣጽንና ማስተዋልን ገንዘብህ አድርግ።+

24 የጻድቅ አባት ደስ ይለዋል፤

ጥበበኛ ልጅ የወለደ ሁሉ በልጁ ሐሴት ያደርጋል።

25 አባትህና እናትህ ሐሴት ያደርጋሉ፤

አንተን የወለደችም ደስ ይላታል።

26 ልጄ ሆይ፣ ልብህን ስጠኝ፤

ዓይኖችህም መንገዴን ይውደዱ።+

27 ዝሙት አዳሪ ጥልቅ ጉድጓድ፣

ባለጌ* ሴትም ጠባብ ጉድጓድ ናትና።+

28 እንደ ዘራፊ ታደባለች፤+

ታማኝ ያልሆኑ ወንዶችን ቁጥር ታበዛለች።

29 ዋይታ የማን ነው? ጭንቀት የማን ነው?

ጠብ የማን ነው? እሮሮ የማን ነው?

ያለምክንያት መቁሰል የማን ነው? የዓይን ቅላት* የማን ነው?

30 ይህ ሁሉ የሚደርሰው የወይን ጠጅ በመጠጣት ረጅም ጊዜ በሚያሳልፉ፣+

የተደባለቀም ወይን ጠጅ ፍለጋ በሚዞሩ* ሰዎች ላይ ነው።

31 በብርጭቆ ውስጥ ሲያንጸባርቅ፣

እየጣፈጠም ሲወርድ በወይን ጠጅ ቅላት ዓይንህ አይማረክ፤

32 በመጨረሻ እንደ እባብ ይናደፋልና፤

እንደ እፉኝትም መርዙን ይረጫል።

33 ዓይኖችህ እንግዳ ነገር ያያሉ፤

ልብህም ጠማማ ነገር ይናገራል።+

34 በባሕር መካከል እንደተኛ፣

በመርከብ ምሰሶም ጫፍ ላይ እንደተጋደመ ሰው ትሆናለህ።

35 እንዲህ ትላለህ፦ “መቱኝ፤ ሆኖም አልተሰማኝም።*

ደበደቡኝ፤ ሆኖም አልታወቀኝም።

ተጨማሪ መጠጥ እጠጣ ዘንድ*

የምነቃው መቼ ነው?”+

24 በክፉ ሰዎች አትቅና፤

ከእነሱም ጋር ለመሆን አትጓጓ፤+

 2 ልባቸው ዓመፅን ያውጠነጥናልና፤

ከንፈራቸውም ተንኮልን ያወራል።

 3 ቤት በጥበብ ይገነባል፤*+

በማስተዋልም ይጸናል።

 4 በእውቀት አማካኝነት ክፍሎቹ

በተለያዩ ውድ የሆኑና ያማሩ ነገሮች ተሞልተዋል።+

 5 ጥበበኛ ሰው ኃያል ነው፤+

ሰውም በእውቀት ኃይሉን ይጨምራል።

 6 ጥበብ ያለበት አመራር ተቀብለህ ለውጊያ ትወጣለህ፤+

በብዙ አማካሪዎችም ድል* ይገኛል።+

 7 ለሞኝ ሰው እውነተኛ ጥበብ ሊገኝ የማይችል ነገር ነው፤+

በከተማው በር ላይ አንዳች የሚናገረው ነገር የለውም።

 8 መጥፎ ነገር ለማድረግ የሚያሴር ሁሉ

ሴራ በመጠንሰስ የተካነ ተብሎ ይጠራል።+

 9 በሞኝነት የሚጠነሰስ ሴራ* ኃጢአት ነው፤

ሰዎችም ፌዘኛን ይጸየፋሉ።+

10 በመከራ ቀን* ተስፋ የምትቆርጥ ከሆነ

ጉልበትህ እጅግ ይዳከማል።

11 ወደ ሞት እየተወሰዱ ያሉትን ታደግ፤

ለእርድ እየተውተረተሩ የሚሄዱትንም አስጥል።+

12 “እኛ ግን ስለዚህ ጉዳይ ምንም አናውቅም” ብትል፣

ልብን* የሚመረምረው እሱ ይህን አያስተውልም?+

አዎ፣ አንተን* የሚመለከተው አምላክ ያውቃል፤

ለእያንዳንዱም ሰው እንደ ሥራው ይከፍለዋል።+

13 ልጄ ሆይ፣ መልካም ስለሆነ ማር ብላ፤

ከማር እንጀራ የሚገኝ ማር ጣፋጭ ጣዕም አለው።

14 በተመሳሳይም ጥበብ ለአንተ መልካም* እንደሆነ እወቅ።+

ጥበብን ብታገኝ የወደፊት ሕይወትህ የተሳካ ይሆናል፤

ተስፋህም ከንቱ አይሆንም።+

15 በጻድቁ ቤት ላይ በክፋት አትሸምቅ፤

ማረፊያ ቦታውንም አታፍርስበት።

16 ጻድቅ ሰባት ጊዜ ቢወድቅ እንኳ መልሶ ይነሳልና፤+

ክፉ ሰው ግን በሚደርስበት መከራ ይሰናከላል።+

17 ጠላትህ ሲወድቅ ሐሴት አታድርግ፤

ሲሰናከልም ልብህ ደስ አይበለው፤+

18 አለዚያ ይሖዋ ይህን አይቶ ያዝናል፤

ቁጣውንም ከእሱ* ይመልሳል።+

19 መጥፎ በሆኑ ሰዎች አትበሳጭ፤

በክፉዎች አትቅና፤

20 መጥፎ ሰው ሁሉ ምንም ተስፋ የለውምና፤+

የክፉዎች መብራት ይጠፋል።+

21 ልጄ ሆይ፣ ይሖዋንና ንጉሥን ፍራ።+

ከተቃዋሚዎች* ጋር አትተባበር፤+

22 ጥፋታቸው ድንገት ይመጣልና።+

ሁለቱም* በእነሱ ላይ የሚያመጡትን ጥፋት ማን ያውቃል?+

23 እነዚህም አባባሎች የጥበበኞች ናቸው፦

በፍርድ ማዳላት ጥሩ አይደለም።+

24 ክፉውን “አንተ ጻድቅ ነህ”+ የሚለውን ሰው ሁሉ

ሕዝቦች ይረግሙታል፤ ብሔራትም ያወግዙታል።

25 እሱን የሚወቅሱት ግን መልካም ይሆንላቸዋል፤+

በመልካም ነገሮችም ይባረካሉ።+

26 ሰዎች በሐቀኝነት መልስ የሚሰጥን ሰው ከንፈር ይስማሉ።*+

27 በደጅ ያለህን ሥራ አሰናዳ፤ በእርሻም ላይ አስፈላጊ የሆኑትን ነገሮች ሁሉ አዘጋጅ፤

ከዚያ በኋላ ቤትህን ሥራ።*

28 ምንም መሠረት ሳይኖርህ በባልንጀራህ ላይ አትመሥክር።+

በከንፈሮችህ ሌሎችን አታታል።+

29 “እሱ እንዳደረገብኝ እንዲሁ አደርግበታለሁ፤

እንደ ሥራው እከፍለዋለሁ”* አትበል።+

30 በሰነፍ ሰው እርሻ፣+

ማስተዋል* በጎደለው ሰው የወይን ቦታ አለፍኩ።

31 እርሻው አረም ወርሶት አየሁ፤

መሬቱን ሳማ ሸፍኖት፣

የድንጋዩም አጥር ፈራርሶ ነበር።+

32 ይህን ተመልክቼ በጥሞና አሰብኩበት፤

ካየሁትም ነገር ይህን ትምህርት አገኘሁ፦*

33 ቆይ ትንሽ ልተኛ፣ ቆይ ትንሽ ላንቀላፋ፣

እጄንም አጣጥፌ እስቲ ትንሽ ጋደም ልበል ካልክ፣

34 ድህነት እንደ ወንበዴ፣

ችጋርም መሣሪያ እንደታጠቀ ሰው ይመጣብሃል።+

25 እነዚህም የይሁዳ ንጉሥ የሕዝቅያስ+ ሰዎች የጻፏቸው* የሰለሞን ምሳሌዎች ናቸው፦+

 2 አንድን ጉዳይ መሰወር ለአምላክ ክብሩ ነው፤+

ጉዳይን በሚገባ መመርመር ደግሞ ለነገሥታት ክብራቸው ነው።

 3 ሰማያት ከፍ ያሉ እንደሆኑ፣ ምድርም ጥልቅ እንደሆነች ሁሉ

የንጉሥም ልብ አይመረመርም።

 4 የብርን ቆሻሻ አስወግድ፤

ሙሉ በሙሉም የጠራ ይሆናል።+

 5 ክፉን ሰው ከንጉሥ ፊት አስወግድ፤

ዙፋኑም በጽድቅ ይጸናል።+

 6 በንጉሥ ፊት ራስህን ከፍ ከፍ አታድርግ፤+

ታላላቅ ሰዎችም ባሉበት ስፍራ አትቀመጥ፤+

 7 በተከበረ ሰው ፊት ከሚያዋርድህ

እሱ ራሱ “ወደዚህ ከፍ በል” ቢልህ ይሻላልና።+

 8 ክስ ለመመሥረት አትቸኩል፤

የኋላ ኋላ ባልንጀራህ ቢያዋርድህ ምን ይውጥሃል?+

 9 ከባልንጀራህ ጋር ስለ ራስህ ጉዳይ ተሟገት፤+

ሆኖም በሚስጥር የተነገረህን ጉዳይ* አትግለጥ፤+

10 አለዚያ የሚሰማህ ሰው ያዋርድሃል፤

ያናፈስከውንም መጥፎ ወሬ* መመለስ አትችልም።

11 በተገቢው ጊዜ የተነገረ ቃል

ከብር በተሠራ ዕቃ ላይ* እንዳለ የወርቅ ፖም ነው።+

12 በጥበብ ወቀሳ የሚሰጥ ሰው፣ የሚሰማ ጆሮ ላለው

እንደ ወርቅ ጉትቻና ከጥሩ ወርቅ እንደተሠራ ጌጥ ነው።+

13 ታማኝ መልእክተኛ ለላኩት ሰዎች

በመከር ወቅት እንደሚገኝ የበረዶ ቅዝቃዜ ነው፤

የጌታውን መንፈስ* ያድሳልና።+

14 የማይሰጠውን ስጦታ* እሰጣለሁ እያለ ጉራውን የሚነዛ ሰው

ዝናብ እንደማያመጣ ደመናና ነፋስ ነው።+

15 በትዕግሥት አዛዥን ማሸነፍ ይቻላል፤

ለስላሳም አንደበት* አጥንትን ይሰብራል።+

16 ማር ካገኘህ የሚበቃህን ያህል ብቻ ብላ፤

ከልክ በላይ ከበላህ ሊያስመልስህ ይችላልና።+

17 እንዳይሰለችህና እንዳይጠላህ

ወደ ባልንጀራህ ቤት እግር አታብዛ።

18 በባልንጀራው ላይ በሐሰት የሚመሠክር

እንደ ቆመጥ፣ እንደ ሰይፍና እንደ ሹል ፍላጻ ነው።+

19 በችግር ወቅት እምነት በማይጣልበት* ሰው መተማመን፣

እንደተሰበረ ጥርስና እንደሰለለ እግር ነው።

20 ላዘነ ልብ የሚዘምር ሰው፣

በብርድ ቀን ልብሱን እንደሚያወልቅ፣

በሶዳም ላይ እንደተጨመረ ኮምጣጤ ነው።+

21 ጠላትህ* ቢራብ ምግብ ስጠው፤

ቢጠማ ውኃ ስጠው፤+

22 ይህን ብታደርግ በራሱ ላይ ፍም ትከምራለህና፤*+

ይሖዋም ወሮታ ይከፍልሃል።

23 የሰሜን ነፋስ ኃይለኛ ዝናብ ያመጣል፤

ሐሜተኛ ምላስም የሰውን ፊት ያስቆጣል።+

24 ከጨቅጫቃ* ሚስት ጋር በአንድ ቤት ከመኖር

በጣሪያ ማዕዘን ላይ መኖር ይሻላል።+

25 ቀዝቃዛ ውኃ የዛለችን ነፍስ* እንደሚያረካ ሁሉ

ከሩቅ አገር የመጣ መልካም ወሬም እንዲሁ ነው።+

26 ለክፉ ሰው የሚንበረከክ* ጻድቅ፣

እንደጨቀየ ምንጭና እንደተበከለ የውኃ ጉድጓድ ነው።

27 ብዙ ማር መብላት ጥሩ አይደለም፤+

የራስንም ክብር መሻት አያስከብርም።+

28 ስሜቱን መቆጣጠር የማይችል ሰው*

ቅጥር እንደሌላት የፈረሰች ከተማ ነው።+

26 በረዶ በበጋ፣ ዝናብም በመከር እንደማያስፈልግ ሁሉ

ክብርም ለሞኝ ሰው አይገባውም።+

 2 ወፍ ቱር የምትልበት፣ ወንጭፊትም የምትበርበት ምክንያት እንዳላት ሁሉ

እርግማንም ያለበቂ ምክንያት አይመጣም።*

 3 አለንጋ ለፈረስ፣ ልጓም ለአህያ፣+

በትርም ለሞኞች ጀርባ ነው።+

 4 ለሞኝ እንደ ሞኝነቱ አትመልስለት፤

አለዚያ አንተም የእሱ ቢጤ ትሆናለህ።*

 5 ጥበበኛ የሆነ እንዳይመስለው

ለሞኝ እንደ ሞኝነቱ መልስለት።+

 6 አንድን ጉዳይ ለሞኝ በአደራ የሚሰጥ

እግሩን ከሚያሽመደምድና ራሱን ከሚጎዳ* ሰው ተለይቶ አይታይም።

 7 በሞኞች አፍ የሚነገር ምሳሌ፣

እንደ አንካሳ ሰው እግር* ነው።+

 8 ለሞኝ ክብር መስጠት፣

በወንጭፍ ላይ ድንጋይ እንደ ማሰር ነው።+

 9 በሞኞች አፍ የሚነገር ምሳሌ

በሰካራም እጅ እንዳለ እሾህ ነው።

10 ሞኝን ወይም አላፊ አግዳሚውን የሚቀጥር፣

በነሲብ ያገኘውን ሁሉ* እንደሚያቆስል ቀስተኛ ነው።

11 ውሻ ወደ ትፋቱ እንደሚመለስ፣

ሞኝ ሰውም ሞኝነቱን ይደጋግማል።+

12 ጥበበኛ ነኝ ብሎ የሚያስብ ሰው አይተህ ታውቃለህ?+

ከእሱ ይልቅ ሞኝ የተሻለ ተስፋ አለው።

13 ሰነፍ “በመንገድ ላይ ደቦል አንበሳ፣

በአደባባይም አንበሳ አለ!” ይላል።+

14 በር በማጠፊያው* ላይ እንደሚዞር፣

ሰነፍም በአልጋው ላይ ይገላበጣል።+

15 ሰነፍ እጁን ወደ ሳህን ያጠልቃል፤

ወደ አፉ ለመመለስ ግን እጅግ ይታክታል።+

16 ሰነፍ ሰው በማስተዋል መልስ ከሚሰጡ ሰባት ሰዎች ይበልጥ

ጥበበኛ የሆነ ይመስለዋል።

17 በሌሎች ጠብ የሚቆጣ* መንገደኛ

የውሻ ጆሮ እንደሚይዝ ሰው ነው።+

18 የሚንበለበሉ ተወንጫፊ መሣሪያዎችን፣ ፍላጻዎችንና ሞትን* እንደሚወረውር እብድ፣

19 ባልንጀራውን አታሎ ሲያበቃ “ቀልዴን እኮ ነው!” የሚል ሰውም እንዲሁ ነው።+

20 እንጨት ከሌለ እሳት ይጠፋል፤

ስም አጥፊ ከሌለ ደግሞ ጭቅጭቅ ይበርዳል።+

21 ከሰል ፍምን፣ እንጨትም እሳትን እንደሚያቀጣጥል

ጨቅጫቃ ሰውም ጠብ ይጭራል።+

22 ስም አጥፊ የሚናገረው ቃል ጣፋጭ እንደሆነ ቁራሽ ምግብ ነው፤*

በፍጥነት ተውጦ በቀጥታ ወደ ሆድ ይገባል።+

23 ከክፉ ልብ የሚወጡ የፍቅር ቃላት፣*

በቀለጠ ብር እንደተለበጠ የሸክላ ዕቃ ስባሪ ናቸው።+

24 ሌሎችን የሚጠላ ሰው ጥላቻውን በከንፈሩ ይደብቃል፤

በውስጡ ግን ተንኮል ይቋጥራል።

25 አነጋገሩን ቢያሳምርም እንኳ አትመነው፤

በልቡ ውስጥ ሰባት አስጸያፊ ነገሮች አሉና።*

26 ጥላቻው በተንኮል ቢሸፈንም

ክፋቱ በጉባኤ መካከል ይገለጣል።

27 ጉድጓድ የሚቆፍር እሱ ራሱ እዚያ ውስጥ ይወድቃል፤

ድንጋይ የሚያንከባልልም ወደ እሱ ተመልሶ ይመጣበታል።+

28 ውሸታም ምላስ የጎዳቻቸውን ሰዎች ትጠላለች፤

የሚሸነግል አንደበትም ጥፋት ያስከትላል።+

27 ነገ በሚሆነው ነገር አትመካ፤

ቀን የሚያመጣውን* አታውቅምና።+

 2 የገዛ አፍህ ሳይሆን ሌላ ሰው ያመስግንህ፤*

የገዛ ከንፈርህ ሳይሆን ሌሎች* ያወድሱህ።+

 3 ድንጋይ ከባድ ነው፤ አሸዋም ሸክም ነው፤

የሞኝ ሰው ትንኮሳ ግን ከሁለቱም ይከብዳል።+

 4 ንዴት ጨካኝ ነው፤ ቁጣም ጎርፍ ነው፤

ይሁንና ቅናትን ማን ሊቋቋም ይችላል?+

 5 ከተሰወረ ፍቅር ይልቅ የተገለጠ ወቀሳ ይሻላል።+

 6 የወዳጅ ማቁሰል ከታማኝነት የሚመነጭ ነው፤+

የጠላት መሳም ግን የበዛ* ነው።

 7 የጠገበ ሰው* ከማር እንጀራ የሚገኝን ማር አይፈልግም፤*

የተራበ* ግን የሚመር ነገር እንኳ ይጣፍጠዋል።

 8 ከቤቱ ወጥቶ የሚባዝን* ሰው

ከጎጆዋ ወጥታ እንደምትባዝን ወፍ ነው።

 9 ዘይትና ዕጣን ልብን ደስ ያሰኛሉ፤

በቀና ምክር ላይ* የተመሠረተ ጥሩ ወዳጅነትም እንዲሁ ነው።+

10 መከራ ባጋጠመህ ቀን የራስህንም ሆነ የአባትህን ወዳጅ ትተህ

ወደ ገዛ ወንድምህ ቤት አትግባ፤

ሩቅ ቦታ ካለ ወንድም ይልቅ በቅርብ ያለ ጎረቤት ይሻላል።+

11 ልጄ ሆይ፣ ለሚነቅፈኝ መልስ መስጠት እችል ዘንድ

ጥበበኛ ሁን፤+ ልቤንም ደስ አሰኘው።+

12 ብልህ ሰው አደጋ አይቶ ይሸሸጋል፤+

ተሞክሮ የሌለው ሰው ግን ዝም ብሎ ይሄዳል፤ መዘዙንም ይቀበላል።*

13 አንድ ሰው ለማያውቀው ሰው ዋስ ከሆነ ልብሱን ውሰድበት፤

ይህን ያደረገው ለባዕድ ሴት* ብሎ ከሆነ መያዣውን ውሰድ።+

14 ሰው በማለዳ ድምፁን ከፍ አድርጎ ባልንጀራውን ቢባርክ

እንደ እርግማን ይቆጠርበታል።

15 ጨቅጫቃ* ሚስት በዝናባማ ቀን ያለማቋረጥ እንደሚያንጠባጥብ ጣሪያ ናት።+

16 እሷን መግታት የሚችል ሁሉ ነፋስን መግታት፣

ዘይትንም በቀኝ እጁ መጨበጥ ይችላል።

17 ብረት ብረትን እንደሚስል ሁሉ

ሰውም ጓደኛውን ይስለዋል።*+

18 የበለስን ዛፍ የሚንከባከብ ፍሬዋን ይበላል፤+

ጌታውንም የሚንከባከብ ክብር ይጎናጸፋል።+

19 ውኃ የሰውን ፊት እንደሚያንጸባርቅ ሁሉ፣

የሰውም ልብ የሌላ ሰው ልብ ነጸብራቅ ነው።

20 መቃብርና የጥፋት ቦታ* አይጠግቡም፤+

ልክ እንደዚሁም የሰው ዓይን ፈጽሞ አይጠግብም።

21 ማቅለጫ ለብር፣ ምድጃ ለወርቅ ነው፤+

ሰውም በሚቀበለው ውዳሴ ይፈተናል።*

22 ሞኝን ሙቀጫ ውስጥ ከተህ በዘነዘና ብትወቅጠውና

እንደ እህል ብታደቀው እንኳ

ሞኝነቱ ከእሱ አይወገድም።

23 የመንጋህን ሁኔታ በሚገባ እወቅ።

በጎችህን በደንብ ተንከባከብ፤*+

24 ሀብት ለዘላለም አይኖርምና፤+

አክሊልም* ከትውልድ እስከ ትውልድ ጸንቶ አይኖርም።

25 ሣሩ በቦታው የለም፤ አዲስ ሣርም በቅሏል፤

በተራሮች ላይ ያለው ተክልም ተሰብስቧል።

26 የበግ ጠቦቶች ለልብስ፣

አውራ ፍየሎችም ለመሬት መግዣ ይሆኑልሃል።

27 ደግሞም አንተንና ቤተሰብህን ለመመገብ፣

ልጃገረዶችህንም በሕይወት ለማኖር የሚያስችል በቂ የፍየል ወተት ይኖርሃል።

28 ክፉዎች ማንም ሳያሳድዳቸው ይሸሻሉ፤

ጻድቃን ግን እንደ አንበሳ ልበ ሙሉ ናቸው።+

 2 በአንድ አገር ውስጥ ሕግ ተላላፊነት* ሲነግሥ ብዙ ገዢዎች ይፈራረቁበታል፤+

ይሁንና ጥልቅ ግንዛቤና እውቀት ያለው ሰው በሚያበረክተው እርዳታ ገዢ* ለረጅም ዘመን ይቆያል።+

 3 ችግረኞችን የሚበዘብዝ ድሃ፣+

እህሉን ሁሉ ጠራርጎ እንደሚወስድ ዝናብ ነው።

 4 ሕግን የሚተዉ ሰዎች ክፉዎችን ያወድሳሉ፤

ሕግን የሚጠብቁ ሰዎች ግን በእነሱ ላይ ይቆጣሉ።+

 5 ክፉዎች ፍትሕን መረዳት አይችሉም፤

ይሖዋን የሚፈልጉ ግን ሁሉን ነገር መረዳት ይችላሉ።+

 6 መንገዱ ብልሹ ከሆነ ሀብታም ይልቅ

ንጹሕ አቋም* ይዞ የሚመላለስ ድሃ ይሻላል።+

 7 አስተዋይ ልጅ ሕግን ይጠብቃል፤

ከሆዳሞች ጋር የሚወዳጅ ግን አባቱን ያዋርዳል።+

 8 ወለድና+ አራጣ በማስከፈል ሀብት የሚያካብት፣

ለድሆች ሞገስ ለሚያሳይ ሰው ያከማችለታል።+

 9 ሕግን ለመስማት አሻፈረኝ የሚል ሰው፣

ጸሎቱ እንኳ አስጸያፊ ነው።+

10 ቅኖችን አሳስቶ ወደ መጥፎ መንገድ የሚመራ፣ እሱ ራሱ በቆፈረው ጉድጓድ ይገባል፤+

ነቀፋ የሌለባቸው ሰዎች ግን መልካም ነገርን ይወርሳሉ።+

11 ሀብታም ሰው በገዛ ዓይኖቹ ፊት ጥበበኛ ነው፤+

ጥልቅ ግንዛቤ ያለው ድሃ ግን ማንነቱን ይደርስበታል።+

12 ጻድቃን ድል ሲያደርጉ ታላቅ ክብር ይሆናል፤

ክፉዎች ሥልጣን ሲይዙ ግን ሰዎች ይሸሸጋሉ።+

13 የሠራውን በደል የሚሸፋፍን አይሳካለትም፤+

የሚናዘዝና የሚተወው ሁሉ ግን ምሕረት ያገኛል።+

14 ምንጊዜም ተጠንቅቆ የሚኖር* ሰው ደስተኛ ነው፤

ልቡን የሚያደነድን ሁሉ ግን ለጥፋት ይዳረጋል።+

15 ምስኪን በሆነ ሕዝብ ላይ የተሾመ ክፉ ገዢ፣

እንደሚያገሳ አንበሳና ተንደርድሮ እንደሚመጣ ድብ ነው።+

16 ጥልቅ ግንዛቤ የሌለው መሪ ሥልጣኑን አላግባብ ይጠቀማል፤+

በማጭበርበር የሚገኝን ትርፍ የሚጠላ ግን ዕድሜውን ያራዝማል።+

17 የሰው ሕይወት በማጥፋቱ የደም* ባለ ዕዳ የሆነ ሰው መቃብር* እስኪገባ ድረስ ሲሸሽ ይኖራል።+

እንዲህ ያለውን ሰው ማንም አይርዳው።

18 እንከን የለሽ በሆነ መንገድ የሚመላለስ ሰው ይድናል፤+

መንገዱ ጠማማ የሆነ ግን ድንገት ይወድቃል።+

19 መሬቱን የሚያርስ ሰው የተትረፈረፈ ምግብ ያገኛል፤

ከንቱ የሆኑ ነገሮችን የሚያሳድድ ግን እጅግ ይደኸያል።+

20 ታማኝ ሰው ብዙ በረከት ያገኛል፤+

ሀብት ለማግኘት የሚጣደፍ ግን ንጽሕናውን ማጉደፉ አይቀርም።+

21 አድልዎ ማድረግ መልካም አይደለም፤+

ሆኖም ሰው ለቁራሽ ዳቦ ብሎ ስህተት ሊፈጽም ይችላል።

22 ቀናተኛ* ሰው ሀብት ለማግኘት ይጓጓል፤

ድህነት ላይ እንደሚወድቅ አያውቅም።

23 በምላሱ ከሚሸነግል ይልቅ

ሰውን የሚወቅስ+ የኋላ ኋላ ይበልጥ ሞገስ ያገኛል።+

24 አባቱንና እናቱን እየዘረፈ “ምንም ጥፋት የለበትም” የሚል ሁሉ+

የአጥፊ ተባባሪ ነው።+

25 ስግብግብ ሰው* ጠብ ያነሳሳል፤

በይሖዋ የሚታመን ግን ይበለጽጋል።*+

26 በገዛ ልቡ የሚታመን ሁሉ ሞኝ ነው፤+

በጥበብ የሚመላለስ ግን ክፉ አያገኘውም።+

27 ለድሃ የሚሰጥ ሁሉ አይቸገርም፤+

እነሱን ላለማየት ዓይኖቹን የሚከድን ግን ብዙ እርግማን ይደርስበታል።

28 ክፉዎች ሥልጣን ሲይዙ ሰው ራሱን ይሸሽጋል፤

ክፉዎች ሲጠፉ ግን ጻድቃን ይበዛሉ።+

29 ብዙ ጊዜ ተወቅሶ አንገቱን ያደነደነ* ሰው፣+

ሊፈወስ በማይችል ሁኔታ በድንገት ይሰበራል።+

 2 ጻድቃን ሲበዙ ሕዝብ ሐሴት ያደርጋል፤

ክፉ ሰው ሲገዛ ግን ሕዝብ ይቃትታል።+

 3 ጥበብን የሚወድ ሰው አባቱን ደስ ያሰኛል፤+

ከዝሙት አዳሪዎች ጋር የሚወዳጅ ግን ሀብቱን ያባክናል።+

 4 ንጉሥ ፍትሕ በማስፈን አገርን ያረጋጋል፤+

ጉቦ የሚፈልግ ሰው ግን ያወድማታል።

 5 ባልንጀራውን የሚሸነግል ሰው፣

ለእግሩ ወጥመድ ይዘረጋበታል።+

 6 መጥፎ ሰው በደሉ ወጥመድ ይሆንበታል፤+

ጻድቅ ግን እልል ይላል፤ ሐሴትም ያደርጋል።+

 7 ጻድቅ ለድሆች መብት ይቆረቆራል፤+

ክፉ ሰው ግን ለእንዲህ ዓይነት ጉዳይ ደንታ የለውም።+

 8 ጉራ የሚነዙ ሰዎች ከተማን ያቃጥላሉ፤+

ጥበበኞች ግን ቁጣን ያበርዳሉ።+

 9 ጥበበኛ ሰው ከሞኝ ጋር ቢሟገት፣

ሁከትና ፌዝ ይነግሣል፤ ደስታ ግን አይኖርም።+

10 ደም የተጠሙ ሰዎች ንጹሕ የሆነን* ሰው ሁሉ ይጠላሉ፤+

ቅን የሆነውን ሰው ሕይወት* ለማጥፋት ይሻሉ።*

11 ሞኝ ስሜቱን* ሁሉ እንዳሻው ይገልጻል፤+

ጥበበኛ ግን ስሜቱን ይቆጣጠራል።+

12 ገዢ የሐሰት ወሬ የሚሰማ ከሆነ፣

አገልጋዮቹ ሁሉ ክፉዎች ይሆናሉ።+

13 ድሃንና ጨቋኝን የሚያመሳስላቸው* ነገር አለ፦

ይሖዋ ለሁለቱም የዓይን ብርሃን ይሰጣል።*

14 ንጉሥ ለድሆች በትክክል ሲፈርድ፣+

ዙፋኑ ምንጊዜም ጸንቶ ይኖራል።+

15 በትርና* ወቀሳ ጥበብ ያስገኛሉ፤+

መረን የተለቀቀ ልጅ ግን እናቱን ያሳፍራል።

16 ክፉዎች ሲበዙ ክፋት ይበዛል፤

ጻድቃን ግን የእነሱን ውድቀት ያያሉ።+

17 ልጅህን ገሥጸው፤ ሰላም ይሰጥሃል፤

ደግሞም እጅግ ደስ ያሰኝሃል።*+

18 ራእይ* ከሌለ ሕዝብ እንዳሻው ይሆናል፤+

ሕግን የሚጠብቁ ግን ደስተኞች ናቸው።+

19 አገልጋይ በቃል ብቻ ለመታረም ፈቃደኛ አይሆንም፤

የሚነገረውን ነገር ቢረዳውም እንኳ እሺ ብሎ አይታዘዝምና።+

20 ለመናገር የሚቸኩል ሰው አይተህ ታውቃለህ?+

ከእሱ ይልቅ ሞኝ የተሻለ ተስፋ አለው።+

21 አገልጋይ ከልጅነቱ ጀምሮ ከተሞላቀቀ፣

የኋላ ኋላ ምስጋና ቢስ ይሆናል።

22 በቀላሉ የሚቆጣ ሰው ጠብ ያስነሳል፤+

ግልፍተኛ የሆነም ብዙ በደል ይፈጽማል።+

23 ሰውን ትዕቢቱ ያዋርደዋል፤+

ትሑት መንፈስ ያለው ግን ክብር ይጎናጸፋል።+

24 የሌባ ግብረ አበር ራሱን* ይጠላል።

እንዲመሠክር የቀረበለትን ጥሪ* ቢሰማም ምንም አይናገርም።+

25 ሰውን መፍራት* ወጥመድ ነው፤+

በይሖዋ የሚታመን ግን ጥበቃ ያገኛል።+

26 ብዙዎች ከገዢ ጋር ተገናኝተው መነጋገር* ይሻሉ፤

ሰው ግን ፍትሕ የሚያገኘው ከይሖዋ ነው።+

27 ጻድቅ ፍትሐዊ ያልሆነን ሰው ይጸየፋል፤+

ክፉ ሰው ግን በቀና መንገድ የሚሄደውን ይጸየፋል።+

30 የያቄ ልጅ አጉር ለኢቲኤል፣ ለኢቲኤልና ለዑካል የተናገራቸው ከፍተኛ ቁም ነገር ያዘሉ ቃላት።

 2 እኔ ከማንም የባሰ አላዋቂ ነኝ፤+

ሰው ሊኖረው የሚገባው ማስተዋልም የለኝም።

 3 ጥበብን አልተማርኩም፤

እጅግ ቅዱስ የሆነው አምላክ እውቀትም የለኝም።

 4 ወደ ሰማይ የወጣ፣ ከዚያም የወረደ ማን ነው?+

ነፋስን በእፍኙ ሰብስቦ የያዘ ማን ነው?

ውኃን በልብሱ የጠቀለለ ማን ነው?+

የምድርን ዳርቻዎች ሁሉ የወሰነ* ማን ነው?+

ስሙ ማን ነው? የልጁስ ስም ማን ነው? ታውቅ እንደሆነ ንገረኝ።

 5 የአምላክ ቃል ሁሉ የነጠረ ነው።+

እሱ፣ መጠጊያቸው ለሚያደርጉት ሁሉ ጋሻ ነው።+

 6 በቃሉ ላይ ምንም አትጨምር፤+

አለዚያ ይወቅስሃል፤

ሐሰተኛም ሆነህ ትገኛለህ።

 7 ሁለት ነገር እንድታደርግልኝ እለምንሃለሁ።

እነሱንም ከመሞቴ በፊት አትንፈገኝ።

 8 ውሸትንና ሐሰትን ከእኔ አርቅ።+

ድሃም ሆነ ባለጸጋ አታድርገኝ።

ብቻ የሚያስፈልገኝን ቀለብ አታሳጣኝ፤+

 9 አለዚያ እጠግብና እክድሃለሁ፤ ከዚያም “ይሖዋ ማን ነው?” እላለሁ፤+

ደግሞም ድሃ ሆኜ እንድሰርቅና የአምላኬን ስም እንዳሰድብ* አትፍቀድ።

10 እንዳይረግምህና በደለኛ ሆነህ እንዳትገኝ

በጌታው ፊት የአገልጋዩን ስም አታጥፋ።+

11 አባቱን የሚረግም፣

እናቱንም የማይባርክ ትውልድ አለ።+

12 በገዛ ዓይኑ ፊት ንጹሕ የሆነ፣+

ሆኖም ከቆሻሻው* ያልነጻ ትውልድ አለ።

13 እጅግ ትዕቢተኛ ዓይን ያለው ትውልድ አለ፤

ዓይኖቹም በታላቅ እብሪት ይመለከታሉ!+

14 ጥርሱ ሰይፍ፣

መንገጭላው ደግሞ ቢላ የሆነ ትውልድ አለ፤

በምድር ላይ ያሉ ምስኪኖችን፣

በሰው ዘር መካከል ያሉ ድሆችንም ይውጣል።+

15 አልቅቶች “ስጡን! ስጡን!” እያሉ የሚጮኹ ሁለት ሴቶች ልጆች አሏቸው።

ፈጽሞ የማይጠግቡ ሦስት ነገሮች አሉ፤

ደግሞም “በቃኝ!” የማያውቁ አራት ነገሮች አሉ።

16 እነሱም መቃብር፣*+ መሃን የሆነ ማህፀን፣

ውኃ የተጠማ መሬት

እንዲሁም “በቃኝ!” የማይል እሳት ናቸው።

17 በአባቷ ላይ የምታፌዝን፣ የእናቷንም ትእዛዝ የምትንቅን+ ዓይን

የሸለቆ* ቁራዎች ይጎጠጉጧታል፤

የንስር ጫጩቶችም ይበሏታል።+

18 ከመረዳት አቅሜ በላይ የሆኑ* ሦስት ነገሮች አሉ፤

የማልገነዘባቸውም አራት ነገሮች አሉ፦

19 ንስር በሰማያት የሚበርበት መንገድ፣

እባብ በዓለት ላይ የሚሄድበት መንገድ፣

መርከብ በባሕር ላይ የሚጓዝበት መንገድ፣

ሰውም ከሴት ልጅ ጋር የሚሄድበት መንገድ ናቸው።

20 የአመንዝራ ሴት መንገድ ይህ ነው፦

በልታ አፏን ከጠራረገች በኋላ

“ምንም የሠራሁት ጥፋት የለም” ትላለች።+

21 ምድርን የሚያናውጡ ሦስት ነገሮች አሉ፤

መታገሥ የማትችላቸውም አራት ነገሮች አሉ፦

22 ባሪያ ንጉሥ ሆኖ ሲገዛ፣+

ሞኝ በልቶ ሲጠግብ፣

23 የተጠላች* ሴት ባል ስታገኝ፣

ሴት አገልጋይም የእመቤቷን ቦታ ስትወስድ* የሚከሰቱ ሁኔታዎች ናቸው።+

24 በምድር ላይ በጣም ትናንሽ የሆኑ አራት ፍጥረታት አሉ፤

ሆኖም በደመ ነፍስ ጥበበኞች* ናቸው፦+

25 ጉንዳኖች ኃይል የሌላቸው ፍጥረታት* ናቸው፤

ይሁንና ምግባቸውን በበጋ ያዘጋጃሉ።+

26 ሽኮኮዎች+ ኃያላን ፍጥረታት* አይደሉም፤

ነገር ግን መኖሪያቸውን በቋጥኞች ውስጥ ያደርጋሉ።+

27 አንበጦች+ ንጉሥ የላቸውም፤

ሆኖም ሁሉም በሰልፍ ወደ ፊት* ይጓዛሉ።+

28 እንሽላሊት*+ በእግሮቿ ቆንጥጣ ትይዛለች፤

ወደ ንጉሥ ቤተ መንግሥትም ትገባለች።

29 ግርማ የተላበሰ አረማመድ ያላቸው ሦስት ፍጥረታት አሉ፤

አዎ፣ እየተጎማለሉ የሚሄዱ አራት ፍጥረታት አሉ፦

30 ከአራዊት ሁሉ ኃያል የሆነውና

ማንንም አይቶ ወደ ኋላ የማይመለሰው አንበሳ፣+

31 አዳኝ ውሻ፣ አውራ ፍየል፣

እንዲሁም በሠራዊቱ የታጀበ ንጉሥ ናቸው።

32 በሞኝነት ራስህን ከፍ ከፍ ካደረግክ፣+

ወይም እንዲህ ለማድረግ ካሰብክ

እጅህን በአፍህ ላይ አድርግ።+

33 ወተት ሲናጥ ቅቤ እንደሚወጣው፣

አፍንጫም ሲጨመቅ እንደሚደማ ሁሉ

ቁጣን ማነሳሳትም ጠብ ያስከትላል።+

31 የንጉሥ ልሙኤል ቃል፤ እናቱ እሱን ለማስተማር የተናገረችው ከፍተኛ ቁም ነገር ያዘለ መልእክት፦+

 2 ልጄ ሆይ፣ ምን ልበልህ?

የማህፀኔ ልጅ ሆይ፣ ምን ልበልህ?

የስእለቴ ልጅ ሆይ፣ ምን ልበልህ?+

 3 ጉልበትህን ለሴቶች አትስጥ፤+

ነገሥታትንም ለጥፋት የሚዳርግ መንገድ አትከተል።+

 4 ልሙኤል ሆይ፣ ነገሥታት የወይን ጠጅ መጠጣት የለባቸውም፤

አዎ፣ ነገሥታት ይህን ማድረግ አይገባቸውም፤

ገዢዎችም “መጠጤ የት አለ?” ሊሉ አይገባም።+

 5 አለዚያ ጠጥተው የተደነገገውን ሕግ ይረሳሉ፤

የችግረኞችንም መብት ይጥሳሉ።

 6 ሊጠፉ ለተቃረቡ ሰዎች መጠጥ፣+

ከባድ ጭንቀት ለደረሰባቸውም* የወይን ጠጅ ስጧቸው።+

 7 ጠጥተው ድህነታቸውን ይርሱ፤

ችግራቸውንም ዳግመኛ አያስታውሱ።

 8 ስለ ራሳቸው መናገር ለማይችሉት አንተ ተናገርላቸው፤

ሊጠፉ ለተቃረቡት ሰዎች ሁሉ መብት ተሟገት።+

 9 ተናገር፤ በጽድቅም ፍረድ፤

ለችግረኛውና ለድሃው መብት ጥብቅና ቁም።*+

א [አሌፍ]

10 ባለሙያ ሚስትን* ማን ሊያገኛት ይችላል?+

ዋጋዋ ከዛጎል* እጅግ ይበልጣል።

ב [ቤት]

11 ባሏ ከልቡ ይታመንባታል፤

አንዳችም ጠቃሚ ነገር አይጎድልበትም።

ג [ጊሜል]

12 በሕይወቷ ዘመን ሁሉ

መልካም ነገር ታደርግለታለች እንጂ ክፉ ነገር አታደርግበትም።

ד [ዳሌት]

13 ሱፍና በፍታ ታመጣለች፤

በእጆቿ መሥራት ያስደስታታል።+

ה [ሄ]

14 እሷ እንደ ነጋዴ መርከብ ናት፤+

ምግቧን ከሩቅ ቦታ ታመጣለች።

ו [ዋው]

15 ገና ሳይነጋም ትነሳለች፤

ለቤተሰቦቿም ምግባቸውን፣

ለሴት አገልጋዮቿም ድርሻቸውን ትሰጣለች።+

ז [ዛየን]

16 በጥሞና ካሰበችበት በኋላ መሬት ትገዛለች፤

በራሷ ጥረት* ወይን ትተክላለች።

ח [ኼት]

17 ወገቧን ታጥቃ ለሥራ ትነሳለች፤*+

ክንዶቿንም ታበረታለች።

ט [ቴት]

18 ንግዷ ትርፋማ እንደሆነ ታስተውላለች፤

መብራቷ በሌሊት አይጠፋም።

י [ዮድ]

19 እጆቿ አመልማሎ የያዘ ዘንግ ይጨብጣሉ፤

ጣቶቿም እንዝርት ይይዛሉ።*+

כ [ካፍ]

20 እጆቿን ለተቸገረ ሰው ትዘረጋለች፤

ለድሃውም እጇን ትከፍታለች።+

ל [ላሜድ]

21 ቤተሰቦቿ ሁሉ የሚያሞቅ* ልብስ ስለሚለብሱ

በበረዶ ወቅት እንኳ አትሰጋም።

מ [ሜም]

22 ለራሷ የአልጋ ልብስ ትሠራለች።

ልብሷ ከበፍታና ከሐምራዊ ሱፍ የተሠራ ነው።

נ [ኑን]

23 ባሏ ከአገሩ ሽማግሌዎች ጋር በሚቀመጥበት በከተማዋ በሮች+

በሰዎች ዘንድ በሰፊው የታወቀ ነው።

ס [ሳሜኽ]

24 የበፍታ ልብሶች እየሠራች* ትሸጣለች፤

ለነጋዴዎችም ቀበቶ ታስረክባለች።

ע [አይን]

25 ብርታትንና ግርማን ትጎናጸፋለች፤

የወደፊቱንም ጊዜ በልበ ሙሉነት ትጠባበቃለች።*

פ [ፔ]

26 አፏን በጥበብ ትከፍታለች፤+

የደግነት ሕግም* በአንደበቷ አለ።

צ [ጻዴ]

27 የቤተሰቧን እንቅስቃሴ በደንብ ትከታተላለች፤

የስንፍናንም ምግብ አትበላም።+

ק [ኮፍ]

28 ልጆቿ ተነስተው ደስተኛ ይሏታል፤

ባሏ ተነስቶ ያወድሳታል።

ר [ረሽ]

29 ባለሙያ* የሆኑ ብዙ ሴቶች አሉ፤

አንቺ ግን፣ አዎ አንቺ ከሁሉም ትበልጫለሽ።

ש [ሺን]

30 ውበት ሐሰት፣ ቁንጅናም አላፊ* ነው፤+

ይሖዋን የምትፈራ ሴት ግን ትመሰገናለች።+

ת [ታው]

31 ላከናወነችው ነገር ሽልማት ስጧት፤*+

ሥራዎቿም በከተማዋ በሮች ያስመስግኗት።+

ቃል በቃል “ለማወቅ።”

ወይም “ፍትሕና።”

ወይም “ሚዛናዊነት።”

ወይም “በጥልቅ ማክበር።”

ወይም “ሕግ፤ ትምህርት።”

ወይም “ሲኦል።” የሰው ልጆችን ሁሉ መቃብር ያመለክታል። የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ወይም “ከእኛ ጋር ዕጣህን ጣል።”

ወይም “አንድ የጋራ ከረጢት (ቦርሳ) ይኖረናል።”

ወይም “ነፍስ።”

ወይም “ነፍስ።”

ቃል በቃል “ራስ።”

ወይም “ስወቅሳችሁ ተመለሱ።”

ቃል በቃል “የመንገዳቸውን ፍሬ ይበላሉ።”

ወይም “ውጥን፤ ዕቅድ።”

ወይም “ማስተዋል የታከለበት ጥበብን።”

እዚህ ላይ የገባው የዕብራይስጥ ቃል የሥነ ምግባር ንጽሕናን፣ ሁለት ልብ አለመሆንንና እንከን የለሽ መሆንን ያመለክታል።

የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ቃል በቃል “እንግዳ።” ከምትከተለው የሥነ ምግባር አቋም የተነሳ ከአምላክ ጋር የተቆራረጠችን ሴት የሚያመለክት ሳይሆን አይቀርም።

ቃል በቃል “ባዕድ።” ከምትከተለው የሥነ ምግባር አቋም የተነሳ ከአምላክ የራቀችን ሴት የሚያመለክት ሳይሆን አይቀርም።

ወይም “የሚያማልል።”

ወይም “ባሏን።”

ቃል በቃል “መንገዷም።”

ቃል በቃል “ወደ እሷ የሚገቡ።”

ወይም “ንጹሕ አቋማቸውን የሚጠብቁ።”

ወይም “ሕጌን።”

ወይም “እውነት።”

ቃል በቃል “በገዛ ራስህ ማስተዋል አትደገፍ።”

ቃል በቃል “ለእምብርትህ።”

ወይም “ከገቢህ።”

ወይም “ምርጥ በሆነው ነገር።”

የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ከላይ በሚገኙት ቁጥሮች ላይ የተጠቀሱትን የአምላክ ባሕርያት የሚያመለክት ሳይሆን አይቀርም።

ወይም “ማስተዋል የታከለበትን ጥበብና።”

ወይም “ለነፍስህ ሕይወት ያስገኙላታል።”

ወይም “ከምንም ነገር ጋር አይጋጭም።”

ወይም “ማድረግ እስከቻልክ ድረስ።”

ወይም “ሕጌን።”

ወይም “ዓይነተኛ።”

ቃል በቃል “ጆሮህን ወደ ንግግሬ አዘንብል።”

ቃል በቃል “ለሥጋቸውም ሁሉ።”

ወይም “ብሩህ ዓይኖችህ ፊት ለፊት ይመልከቱ።”

“ልብ ብለህ አጢን” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ቃል በቃል “ወደ ማስተዋሌ ጆሮህን አዘንብል።”

ቃል በቃል “የእንግዳ።” ምሳሌ 2:16ን ተመልከት።

ወይም “ሲኦል።” የሰው ልጆችን ሁሉ መቃብር ያመለክታል። የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ወይም “ኃይልህን።”

ቃል በቃል “በማኅበርና በጉባኤ መካከል።”

ወይም “የምንጭህን ንጹሕ ውኃ ጠጣ።”

ወይም “ዋልያ።”

ወይም “ያስክሩህ።”

ቃል በቃል “እንግዳ።” ምሳሌ 2:16ን ተመልከት።

ቃል በቃል “ባዕድ።” ምሳሌ 2:16ን ተመልከት።

ቃል በቃል “ተያዥ።”

ወይም “ብትጨብጥ።” ቃል መግባትን ያመለክታል።

ወይም “ነፍሱ የምትጸየፋቸው።”

ወይም “ሕግ፤ ትምህርት።”

ወይም “ያስተምርሃል።”

ቃል በቃል “ከባዕድ።” ምሳሌ 2:16ን ተመልከት።

ቃል በቃል “አንድ ሰው ያለውን ሁሉ አጥቶ አንድ ዳቦ ብቻ ይቀረዋል።”

ወይም “ነፍስ።”

ወይም “ነፍሱን።”

ቃል በቃል “ልብ።”

ወይም “በነፍሱ።”

ወይም “ቤዛ።”

ወይም “ሕጌን፤ ትምህርቴን።”

ቃል በቃል “እንግዳና።” ምሳሌ 2:16ን ተመልከት።

ቃል በቃል “ባዕድ።” ምሳሌ 2:16ን ተመልከት።

ወይም “የሚያማልል።”

ወይም “ተሞክሮ የሌላቸውን።”

ቃል በቃል “ልብ።”

ወይም “የዝሙት አዳሪ ልብስ።”

ቃል በቃል “እግሮቿ ቤት አይቀመጡም።”

በመጽሐፍ ቅዱስ ዘመን ሽቶ ለመሥራት የሚያገለግል ጥሩ መዓዛ ያለው ንጥረ ነገር የሚገኝበትን ዛፍ ያመለክታል።

ወይም “በእግር ብረት።”

ወይም “ነፍሱን።”

ወይም “ሲኦል።” የሰው ልጆችን ሁሉ መቃብር ያመለክታል። የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ቃል በቃል “ወደ ሞት ውስጠኛ ክፍሎችም።”

ቃል በቃል “ለሰው ወንዶች ልጆች።”

የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ወይም “በውርስ የተገኙ ውድ ነገሮችና።”

ወይም “በውል ከማይታወቁ ዘመናት በፊት።”

ወይም “በምጥ ተወለድኩ።”

ቃል በቃል “ክበብን።”

ቃል በቃል “ባጸና።”

ወይም “በደነገገ።”

ወይም “በየዕለቱ በራፌ ላይ ነቅቶ በመጠበቅ።”

ወይም “ነፍሱን።”

ቃል በቃል “እርዷን አረደች።”

ቃል በቃል “ልብ።”

ወይም “ተሞክሮ ከሌላቸው ሰዎች ራቁ።”

ቃል በቃል “ልብ።”

ወይም “በሲኦል።” የሰው ልጆችን ሁሉ መቃብር ያመለክታል። የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ወይም “የጻድቁ ነፍስ እንድትራብ።”

ወይም “ጻድቅ ሰው ያተረፈው ስም።”

ቃል በቃል “ይበሰብሳል።”

ቃል በቃል “ትእዛዛትን።”

ምሳሌ 2:7 ላይ የሚገኘውን የግርጌ ማስታወሻ ተመልከት።

ቃል በቃል “ልብ።”

ወይም “ውድ ንብረት።”

“ወደ ሕይወት በሚወስድ መንገድ ላይ ነው” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ወይም “አሉባልታ።”

ወይም “ይመራሉ።”

ወይም “ሐዘንን፤ መከራን።”

ወይም “ለአሠሪው።”

ወይም “የጥበብን ፍሬ ያፈራል።”

ወይም “የማታለያ።”

ወይም “የተሟላ የድንጋይ መለኪያ።”

ምሳሌ 2:7 ላይ የሚገኘውን የግርጌ ማስታወሻ ተመልከት።

ወይም “ውድ ነገሮች ፋይዳ አይኖራቸውም።”

ወይም “አምላክ የለሽ ሰው።”

ቃል በቃል “ልብ።”

ወይም “ባልንጀራውን ያቃልላል።”

ቃል በቃል “በመንፈሱ የታመነ ሰው።”

ቃል በቃል “ነገርን ይሰውራል።”

ወይም “መዳን።”

ወይም “ተያዥ የሚሆን።”

ወይም “በመጨበጥ።”

ቃል በቃል “(ቃል መግባት) የሚጠላ።”

ወይም “የምትወደድ።”

ወይም “ታማኝ ፍቅር የሚያሳይ ሰው ነፍሱን ይጠቅማል።”

ወይም “ውርደት።”

ቃል በቃል “አንዱ ይበትናል።”

ወይም “ለጋስ ነፍስ።”

ቃል በቃል “ይሰባል።”

ቃል በቃል “እንደ ልብ የሚያጠጣም።”

ወይም “ውርደት።”

የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ወይም “ማስተዋል።”

ወይም “አሳፋሪ ድርጊት የምትፈጽም።”

ቃል በቃል “ደም ለማፍሰስ ያደባል።”

ቃል በቃል “ዳቦ።”

ወይም “የቤት እንስሳቱን ነፍስ።”

ቃል በቃል “ልብ።”

ወይም “በዚያው ቀን።”

ቃል በቃል “ይሸፍናል።”

ቃል በቃል “ጽድቅ የሆነውን።”

ቃል በቃል “የሰላም አማካሪ የሆኑ።”

ወይም “የመንፈስ ጭንቀት ያስከትልበታል።”

ወይም “እርማትን።”

ወይም “የከዳተኞች ነፍስ።”

ወይም “ተጠንቅቆ የሚናገር ነፍሱን ይጠብቃል።”

ወይም “ነፍሱ ምንም አታገኝም።”

ወይም “ነፍስ።”

ቃል በቃል “ትሰባለች።”

ወይም “ለነፍሱ።”

ቃል በቃል “ሐሴት ያደርጋል።”

ወይም “እርስ በርስ በሚመካከሩ።”

ወይም “ከምንም ተነስቶ የተገኘ ሀብት።”

ቃል በቃል “በእጁ የሚሰበስብ።”

ወይም “ቃልን የሚንቅ።”

ወይም “ሕግ።”

ወይም “ወቀሳን የሚቀበል።”

ወይም “ነፍስ።”

ወይም “እሱ ይጠፋል።”

ወይም “ልጁን ከመገሠጽ፤ ልጁን ከመቅጣት።”

“ወዲያው” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ወይም “ነፍሱንም።”

ወይም “ጠማማ።”

“ሞኞች ግን ሌሎችን ያታልላሉ” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ወይም “በበደል ካሳ።”

ወይም “በቅኖች መካከል ግን በጎ ፈቃድ አለ።”

ወይም “የነፍሱን።”

ወይም “ተሞክሮ የሌለው።”

ወይም “ይቆጣል።”

ወይም “የማመዛዘን ችሎታ ያለው ሰው።”

ወይም “ተሞክሮ የሌላቸው።”

ወይም “ነፍስን።”

ወይም “ጤና።”

ምሳሌ 2:7 ላይ የሚገኘውን የግርጌ ማስታወሻ ተመልከት።

ወይም “ደግነት የተሞላበት።”

ወይም “የሚያቆስል።”

ወይም “ፈዋሽ ምላስ።”

ቃል በቃል “መንፈስን ያደቃል።”

ወይም “ገቢ።”

ወይም “ከባድ።”

ወይም “ሲኦልና።” የሰው ልጆችን ሁሉ መቃብር ያመለክታል። የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ወይም “አባዶን።”

ወይም “የሚወቅሰውን።”

ወይም “ይከታተላል።”

ወይም “ጥሩ።”

ወይም “ከሽብር።”

ቃል በቃል “በግርግም የተቀለበ።”

ቃል በቃል “ልብ።”

ወይም “ልብ ለልብ መነጋገር።”

ቃል በቃል “በአፉ መልስ።”

ወይም “ሲኦል።” የሰው ልጆችን ሁሉ መቃብር ያመለክታል። የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ወይም “ውርደት።”

ወይም “ምን ብሎ እንደሚመልስ በጥሞና ያስባል፤ ከመናገሩ በፊት ያስባል።”

ወይም “በፈገግታ የተሞላ ፊት።”

ቃል በቃል “ያሰባል።”

ወይም “ነፍሱን።”

ቃል በቃል “ልብ።”

ቃል በቃል “ልብን ማዘጋጀት የሰው ድርሻ ነው።”

ወይም “ትክክለኛው መልስ።” ቃል በቃል “የምላስ መልስ።”

ቃል በቃል “ንጹሕ።”

ቃል በቃል “መንፈስን።”

ቃል በቃል “ሥራህን ለይሖዋ አስተላልፍ።”

ወይም “መለኮታዊ ውሳኔ።”

ወይም “ያስወግደዋል።”

ወይም “ነፍሱን ይጠብቃል።”

ቃል በቃል “የተዋረደ መንፈስ።”

ቃል በቃል “ጥሩ ነገር ያገኛል።”

ወይም “በሚማርክ መንገድ የሚናገርም።” ቃል በቃል “ከንፈሩ ጣፋጭ የሆነም።”

ወይም “ለአፍ።” የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ወይም “ነፍሱ።”

ቃል በቃል “አፉ።”

ወይም “ሴረኛ።”

ወይም “የክብር።”

ቃል በቃል “መንፈሱን የሚገዛም።”

ቃል በቃል “መሥዋዕቶች ከሞሉበት።”

ወይም “ጸጥታ።”

ቃል በቃል “ወንዶች የልጅ ልጆች።”

ወይም “ወላጆችም።”

ወይም “ለልጆቻቸው።”

ወይም “መልካም።”

ወይም “ለተከበረ ሰው።”

ወይም “ሞገስ የሚያስገኝ ድንጋይ።”

ቃል በቃል “የሚሸፍን።”

ቃል በቃል “ውኃን ከመልቀቅ።”

ወይም “ማስተዋል።”

ወይም “ተያዥ።”

ቃል በቃል “መልካም ነገር አያገኝም።”

ወይም “ፈውስ ያስገኛል።”

ወይም “አጥንትን ያደርቃል።”

ቃል በቃል “ከሰው ጉያ።”

ወይም “መቀጫ ማስከፈል።”

ቃል በቃል “መንፈሱ ቀዝቃዛ ነው።”

ወይም “ማስተዋል የታከለበትንም ጥበብ።”

ወይም “ይንቃል።”

ወይም “ለነፍሱ።”

ወይም “ተስገብግበው እንደሚውጡት ነገር ነው።”

ቃል በቃል “ከፍ ይላል።” ግለሰቡ እንደማይደረስበትና ከአደጋ እንደሚጠበቅ ያመለክታል።

ወይም “ከባድ የተስፋ መቁረጥ ስሜትን።”

ወይም “በጎ ፈቃድ።”

ምሳሌ 2:7 ላይ የሚገኘውን የግርጌ ማስታወሻ ተመልከት።

ወይም “ነፍስ።”

ቃል በቃል “በእግሩ የሚጣደፍ።”

ወይም “ለጋስ በሆነ ሰው።”

ቃል በቃል “ልብ።”

ወይም “ነፍሱን።”

ቃል በቃል “መልካም ነገር ያገኛል።”

ቃል በቃል “በደልንም ማለፉ።”

ወይም “ደቦል አንበሳ።”

ወይም “ነዝናዛ ሚስትም።”

ወይም “ታካች ነፍስም ትራባለች።”

ወይም “ነፍሱን።”

ወይም “ወሮታ።”

ወይም “የእሱንም ሞት አትመኝ።” ቃል በቃል “ለእሱ ሞት ነፍስህን አታንሳ።”

ወይም “ዓላማ።”

ወይም “የንጉሥ አስፈሪነት።”

ወይም “ደቦል አንበሳ።”

“በመከር ወራት ይፈልጋል፤ ግን አያገኝም” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ወይም “ዕቅድ።” ቃል በቃል “ምክር።”

ምሳሌ 2:7 ላይ የሚገኘውን የግርጌ ማስታወሻ ተመልከት።

ወይም “ሁለት ዓይነት የድንጋይ ሚዛንና ሁለት ዓይነት መስፈሪያ።”

የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ወይም “ለባዕድ።”

ወይም “ምክር።”

ወይም “ይጸናል።”

ወይም “በከንፈሮቹ ከሚያባብል ሰው።”

ወይም “ሁለት ዓይነት የድንጋይ ሚዛን።”

ወይም “የሚሄድበትን መንገድ።”

ተሽከርካሪ እግር።

ወይም “ያነጻል።”

ወይም “ውስጣዊ ዓላማን ይመረምራል።”

ወይም “ጥቅም ያስገኝለታል።”

“ሞትን ለሚሹ ወዲያው እንደሚጠፋ ጉም ነው” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ወይም “ከነዝናዛ።”

ወይም “የክፉ ሰው ነፍስ።”

ወይም “ምን ማድረግ እንዳለበት ያውቃል።”

ቃል በቃል “በጉያ የተሸጎጠ ጉቦም።”

ወይም “ደስታ።”

ወይም “ነዝናዛና።”

ቃል በቃል “ያለውን ይውጣል።”

ወይም “ከተማን ድል ያደርጋል።”

ወይም “ነፍሱን ከችግር ይጠብቃል።”

ወይም “አሳፋሪ ምግባር እያለው።”

ቃል በቃል “ለዘላለም ይናገራል።”

ወይም “ቅን ሰው ግን መንገዱን አስተማማኝ ያደርጋል።”

ወይም “ዝና።” ቃል በቃል “ስም።”

ቃል በቃል “ሞገስ።”

ቃል በቃል “ተገናኙ።”

ወይም “ቅጣቱንም።”

ወይም “ለነፍሱ።”

ወይም “ሕፃንን፤ ወጣትን።”

ቃል በቃል “ጥሩ ዓይን ያለው ሰው።”

ወይም “ክስና።”

ቃል በቃል “የእንግዳ።” ምሳሌ 2:16ን ተመልከት።

ወይም “በሕፃን፤ በወጣት።”

ወይም “ነፍስ ይቀማል።”

ወይም “ለነፍስህም።”

ወይም “እንደሚጨብጡ።”

ወይም “በምኞት የተሞላች ነፍስ ብትኖርህ።”

ወይም “ራስህን ተቆጣጠር።”

“በገዛ ራስህ ማስተዋል አትመራ” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ወይም “ክፉ ዓይን ያለው ሰው የሚያቀርበውን።”

ወይም “በነፍሱ እንደሚያሰላ።”

ቃል በቃል “ልቡ ግን ከአንተ ጋር አይደለም።”

ቃል በቃል “የሚዋጃቸው።”

ወይም “ሕፃንን፤ ወጣትን።”

ወይም “ከሲኦል።” የሰው ልጆችን ሁሉ መቃብር ያመለክታል። የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ወይም “ነፍሱን ከመቃብር ታድናት ዘንድ።”

ቃል በቃል “ኩላሊቶቼ ደስ ይላቸዋል።”

ወይም “ብዙ የወይን ጠጅ ከሚጠጡ፣ ሥጋም ያለልክ ከሚሰለቅጡ ሰዎች ጋር አትወዳጅ።”

ወይም “አግኝ።”

ቃል በቃል “ባዕድ።” ምሳሌ 2:16ን ተመልከት።

ወይም “መፍዘዝ።”

ወይም “ለመቀማመስ በሚሰባሰቡ።”

ወይም “አላመመኝም።”

ወይም “መጠጡን ደግሜ እሻዋለሁ።”

ወይም “ቤተሰብ በጥበብ ይገነባል።”

ወይም “ስኬት፤ መዳን።”

ወይም “የሞኝ ሴራ።”

ወይም “በችግር ጊዜ።”

ወይም “ውስጣዊ ዓላማን።”

ወይም “ነፍስህን።”

ወይም “ለነፍስህ ጣፋጭ።”

ጠላትን ያመለክታል።

ወይም “ለውጥ ለማካሄድ ከተነሱ ሰዎች።”

ይሖዋንና ንጉሡን ያመለክታል።

“በቀጥታ መልስ መስጠት እንደ መሳም ይቆጠራል” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ወይም “ቤተሰብህን ገንባ።”

ወይም “አጸፋውን እመልሳለሁ።”

ቃል በቃል “ልብ።”

ቃል በቃል “ተግሣጽ ተቀበልኩ፦”

ወይም “የገለበጧቸውና ያጠናቀሯቸው።”

ወይም “የሌሎችን ሚስጥር።”

ወይም “ተንኮል ያዘለ አሉባልታ።”

ወይም “በብር መደብ ላይ።”

ወይም “ነፍስ።”

ቃል በቃል “የውሸት ስጦታ።”

ወይም “የለዘበም አንደበት።”

“በከዳተኛ” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ቃል በቃል “የሚጠላህ ሰው።”

የሰውየውን ልብ ለማለስለስና ግትር አቋሙን ለማለዘብ የሚደረግን ጥረት ያመለክታል።

ወይም “ከነዝናዛ።”

የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ወይም “በክፉ ሰው ፊት አቋሙን የሚያላላ።” ቃል በቃል “በክፉ ሰው ፊት የሚንገዳገድ።”

ወይም “መንፈሱን የማይገታ ሰው።”

“ተገቢ ያልሆነ እርግማንም በሰው ላይ አይደርስም” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ወይም “አለዚያ አንተም እኩያው ትሆናለህ።”

ቃል በቃል “ዓመፅን ከሚጋት።”

ወይም “እንደ ሽባ ሰው የተንጠለጠለ እግር።”

ወይም “ሰውን ሁሉ።”

ወይም “በመሽከርከሪያው።”

“ጣልቃ የሚገባ” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ወይም “ገዳይ ፍላጻዎችን።”

ወይም “ተስገብግበው እንደሚውጡት ነገር ነው።”

ቃል በቃል “ኃይለኛ ስሜትን የሚገልጽ ከንፈር።”

ወይም “ልቡ ሙሉ በሙሉ አስጸያፊ ነውና።”

ቃል በቃል “የሚወልደውን።”

ቃል በቃል “እንግዳ ያመስግንህ።”

ቃል በቃል “የባዕድ አገር ሰዎች።”

“የውሸት፤ የግድ” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ወይም “ነፍስ።”

ቃል በቃል “ይረግጣል።”

ወይም “የተራበች ነፍስ።”

ወይም “የሚሰደድ።”

ወይም “በነፍስ ምክር ላይ።”

ወይም “ይቀጣልም።”

ወይም “ለባዕድ።”

ወይም “ነዝናዛ።”

ቃል በቃል “የጓደኛውን ፊት ይስላል።”

ወይም “ሲኦልና አባዶን።”

ወይም “ሰውም በሚያገኘው ውዳሴ መሠረት ነው።”

ወይም “ልብህን በበጎችህ ላይ አኑር፤ ለበጎችህ ትኩረት ስጥ።”

ወይም “ዘውድም።”

ወይም “ዓመፅ።”

ቃል በቃል “እሱ።”

ምሳሌ 2:7 ላይ የሚገኘውን የግርጌ ማስታወሻ ተመልከት።

ወይም “ፍርሃት ተለይቶት የማያውቅ።”

ወይም “የነፍስ ደም።”

ወይም “ጉድጓድ።”

ወይም “ስግብግብ።”

“እብሪተኛ ነፍስ” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ቃል በቃል “ይሰባል።”

ወይም “ግትር የሆነ።”

ወይም “ነቀፋ የሌለበትን።”

ወይም “ነፍስ።”

“ቅን የሆነ ሰው ግን ሕይወቱን ለመጠበቅ ይሻል” ማለትም ሊሆን ይችላል።

ቃል በቃል “መንፈሱን።”

ቃል በቃል “የሚያገናኛቸው።”

ሕይወት እንደሚሰጣቸው ያመለክታል።

ወይም “ተግሣጽና፤ ቅጣትና።”

ወይም “ነፍስህን እጅግ ደስ ያሰኛታል።”

ወይም “ትንቢታዊ ራእይ።”

ወይም “የገዛ ነፍሱን።”

ወይም “እርግማን የሚያስከትለውን መሐላ።”

ወይም “በሰው ፊት መንቀጥቀጥ።”

“የገዢን ሞገስ ማግኘት” ማለትም ሊሆን ይችላል። ቃል በቃል “የገዢን ፊት።”

ቃል በቃል “ያቆመ።”

ወይም “እንዳስነቅፍ።”

ቃል በቃል “ከእዳሪው።”

ወይም “ሲኦል።” የሰው ልጆችን ሁሉ መቃብር ያመለክታል። የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ወይም “የደረቅ ወንዝ።”

ወይም “እጅግ የሚያስደንቁኝ።”

ወይም “የማትወደድ።”

ወይም “ስትቀማ።”

ወይም “እጅግ ጥበበኞች።”

ቃል በቃል “ጥንካሬ የሌለው ሕዝብ።”

ቃል በቃል “ሕዝብ።”

ወይም “በቡድን ተከፋፍለው።”

ጌኮ የተባለችውን እንሽላሊት ያመለክታል።

ወይም “በነፍሳቸው ለተመረሩትም።”

ወይም “ጉዳይ ተሟገት።”

ወይም “እጅግ ጥሩ የሆነችን ሚስት።”

የቃላት መፍቻውን ተመልከት።

ወይም “በምታገኘው ገቢ።” ቃል በቃል “ከእጆቿ ፍሬ።”

ቃል በቃል “ዳሌዋን በኃይል ትታጠቃለች።”

የአመልማሎ ዘንግና እንዝርት፣ ድርና ማግ ለማጠንጠን ወይም ለመሥራት የሚያገለግሉ ቀጫጭን እንጨቶች ናቸው።

ቃል በቃል “ድርብ።”

ወይም “የውስጥ ልብሶች እየሠራች።”

ወይም “በመጪው ጊዜ ላይ ትስቃለች።”

ወይም “ፍቅራዊ መመሪያም፤ የታማኝ ፍቅር ሕግም።”

ወይም “እጅግ ጥሩ።”

ወይም “ከንቱ።”

ቃል በቃል “ከእጆቿ ፍሬ ስጧት።”

    የኢትዮጵያ ምልክት ቋንቋ ጽሑፎች (2011-2025)
    ውጣ
    ግባ
    • የኢትዮጵያ ምልክት ቋንቋ
    • አጋራ
    • የግል ምርጫዎች
    • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
    • የአጠቃቀም ውል
    • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
    • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
    • JW.ORG
    • ግባ
    አጋራ